1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ተስፋ የማይቆርጠው ርዋንዳዊ ነጋዴ

ረቡዕ፣ ነሐሴ 13 2007

ሰርጅ ንደክቬ ፤ የ18 ዓመት ወጣት ሳለ ፤ የታክሲ ሹፌር ሆኖ ሰርቷል፤ ከአንድ ዓመት በኋላ ደግሞ የጭነት መኪና ሾፍሯል። ተስፋ የማይቆርጠው ሩዋንዳዊ ወጣት ቀጥሎ ደግሞ ስልክ፣ መኪና፣ የመሳሰሉትን አሻሽጧል። የራሱ የሆነ ንግድ ከመጀመሩ በፊት ማለት ነው።

https://p.dw.com/p/1GHpc
Serge Ndekwe Unternehmer Ruanda
ምስል DW

[No title]


የሰርጅ ንደክቬ ስራ አያልቅም። ዛሬ የ35 ዓመቱ ጎልማሳ የከፈተው የጣሊያን ምግብ ቤት በረንዳ ላይ ቆሞ ታች ያለውን አረንዴ ሳር ይመለከታል። በብዙ ሺ የሚቆጠር ዩሮ ያፈሰሰበት ምግብ ቤት ውስጡ መጠጥ ቤት እና ጭፈራ ቤትም አለው። የምግብ ቤቱ እንግዶች የርዋንዳ መዲና ኪጋሊን ውበት ከፎቅ ላይ ሆነው ያደንቃሉ። ነገር ግን ሰርጅ ዛሬ የደረሰበት ቦታ እስኪደርስ ብዙ ፈተናዎችን ማለፍ ነበረበት፤
« ከጋሳቦ ቀበሌ በግል የእገዳ ደብዳቤ ደረሰን። ያኔ እጅግ ሀሳብ ይገባኻል ምክንያቱም ስኬታማ ትሁን አትሁን አታውቀውም፤ እዛ ላይ እንደዚህ አይነት ንግድ ስትጀምር፤ ቦታው ይስራ አይስራ እንኳን አታውቅም።»
ለደንበኞች በቂ መኪና ማቆሚያ የለም በዛ ላይ ድምፅ አካባቢውን እየረበሸ ነው በሚል ነበር ንግዱ ገና ከመጀመሩ የአካባቢው መስተዳደር የሰርጅን ምግብ ቤት የዘጋው። ሰርጅ ይህንን ለማስተካከል ሌላ ተጨማሪ ገንዘብ ማውጣት ነበረበት። በመጨረሻም ለችግሩ መፍትሄ አገኘ፤
« መስኮቱ ሁለት መስታወቶች አሉት ። ስንጀምር አንድ ብቻ ነበር። ያለ ምንም ችግር ሁለት ለማድረግ ተስማማን። አሁን እንደምታየው ሁለት ነው። ቢያንስ አሁን አዚጋ ሰዎች ቢኖሩ እና ከውስጥ ሙዚቃ ቢጫወት ጎረቤቱን አይረብሽም።»
ትንሽ ቆየት ብሎ ሰርጅ ንደክቬ የወተት ፋብሪካውን ይጎበኛል። ይህንንም ቢሆን ባለስልጣናት ፅዳት ይጎድለዋል በሚል ሁለት ጊዜ ለወራት ዘግተውት ነበር። ፋብሪካው የመንግሥት የሆነውን የወተት ፋብሪካ ክፉኛ በመፎካከሩ ነው የተዘጋው የሚል ጭምጭምታም ነበር። አሁን የሰርጄ የወተት ምርቶች በመላው ሩዋንዳ የመደብሮችን መደርደሪያ ተቆጣጥረዋል። ነጭ ጋውን ለብሶ እና አፉን የቀዶ ህክምና ባለሙያዎች በሚያስሩበት አይነት ጨርቅ አፍኖ ፤ አሁን ተስፋ መቁረጫ ሰዓት አይደለም ይላል።
« የተወሰነ ዝና አግኝተናል። ታድያ አሁን መዝጋቱ ጥሩ አይደለም ፤ ምክንያቱም እዚህ ለመድረስ ስምንት ዓመት ፈጅቶብናል። ከሌላ የተወሰነ ዓመታት በኋላ ይህ ፋብሪካ መካከለኛው ደረጃ ላይ የሚገኝ ፋብሪካ ይሆናል።»
ሰርጅ ፋብሪካውን ማስፋፋት እና ዘመናዊ ማድረግ ይፈልጋል። ፋብሪካው በደርዘን የሚቆጠር ሰራተኞች አሉት ሰርጅ ግን ይህንን ቁጥር በእጥፍ ማሳደግ ይፈልጋል። ፋብሪካው በቀን ከ1000 ሊትር በላይ ወተት ይመረታል፤ ከወተት በተጨማሪ እርጎ እና አይብ። ሰርጅ ቀጣይ አላማው ከኪጋሊ ወጣ ብሎ የስፓርት እና የእረፍት ጊዜ መዝናኛ መክፈት ነው። ከገጠሙት ውጣ ውረዶች በኋላ ምናልባት አሁን ይበቃው ይሆን?
« በርግጥ ይጎዳል። ነገር ግን በሌላ በኩል ከፍተኛ ድጋፍ ከመንግሥት አገኛለሁ። እንደ አንድ ወጣት ኩባንያ እንድንሰራ ይገፋፋናል።»
እንደዚህ ነው በራሱ የሚተማመነውን ርዋንዳዊ ጎልማሳ በስራው እንዲቀጥል፣ ለሌሎች ሰዎች የስራ እድል እንዲፈጥር እና ሩዋንዳን በማበልፀጉ ረገድ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ የሚገኘው።
አቡባክር ጃሎህ
ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ

Joghurt Fabrikation von Serge Ndekwe
የሰርጅ እርጎ ፋብሪካምስል DW