የአዉሮጳ ኅብረት ሩስያ ያሰረቻቸዉን ሰላማዊ ሰልፈኞች እንድትፈታ ጠየቀ
ሰኞ፣ መጋቢት 18 2009በሩስያ አንድ የሀገሪቱ ፍርድ ቤት ትናንት በመዲናይቱ ሞስኮ ፀረ ሙስና ተቃውሞ ሰልፍ ያካሄዱትን የተቃዋሚ ቡድን መሪ አሌክሴይ ናቫልኒ በ15 ቀን እስራት እንዲቀጡ እና 20,000 ሩብል ወይም 350 ዩኤስ ዶላር እንዲከፍሉ በየነ። የፍርድ ቤቱ ዳኛ አሌስያ ኦርክሆቫ እጎአ በ2018 ዓም በሚደረገው ፕሬዚደንታዊ ምርጫ በፕሬዚደንት ቭላዲሚር ፑቲን አንፃር ለመፎካከሩ ያቀዱት ናቫልኒ ፈቃድ ሳያገኙ ከሰባት እስከ ስምንት ሺህ ሰው ተሳትፎበታል የተባለውን የትናንቱን ተቃውሞ በማዘጋጀታቸው ጥፋተኛ ብለዋቸዋል። ናቫልኒ ብይኑ ከተሰጠ በኋላ ፀረ ሙስና ትግላቸው ትክክለኛ መሆኑን ለጋዜጠኞች ገልጸዋል።
«የትናንቱ ተቃውሞ በሩስያ በሙስና አንፃር የሚታገል እጩ መርሃግብርን የሚደግፉ ብዙ መራጮች መኖራቸውን ያሳየ ይመስለኛል። እነዚህ መራጮች ፖለቲካዊ ውክልና ማግኘት ይፈልጋሉ። እና እኔ የእነዚህ ሰዎች ተወካይ ለመሆን እፈልጋለሁ፣ ለዚህም ነው ለሀገሪቱ ከፍተኛ ስልጣን የመፎካከር መብት አለኝ ብዬ የማስበው። »
እጎአ ከ2011 ዓም ወዲህ በሞስኮ በተካሄደው ትልቁ ፀረ ሙስና ተቃውሞ ወቅት ከናቫልኒ ጋር ትናንት ወደ አንድ ሺህ የሚገመቱ ተቃዋሚዎችም ታስረዋል። ዩኤስ አሜሪካ እና የአውሮጳ ኅብረት እስራቱ ፀረ ዴሞክራሲ ነው በሚል ሩስያ እስረኞቹን እንድትፈታ ቢጠይቁም፣ ሩስያ ጥያቄውን ውድቅ አድርጋዋለች።
አርያም ተክሌ
አዜብ ታደሰ