1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ትኩረት በአፍሪቃ

ቅዳሜ፣ ታኅሣሥ 13 2005

ትኩረት በአፍሪቃ ሶስት አበይት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ አጠንጥኖዋል። የአፍሪቃና የጀርመን አጠቃላይ ግንኙነት ቀዳሚው ርዕስ ነው። የማሊ ፖለቲካና የጀርመን ተሳትፎ የተሰኘው ርዕስ ይከተለዋል። በደቡብ አፍሪቃ በሴቶችና ልጆች ላይ የሚፈፀመው ፆታዊ ጥቃቶችን የሚመለከተው ርዕሰጉዳይ ያሰልሰዋል። የጋዜጦች አምድም ተካቶበታል

https://p.dw.com/p/1784X
Parteitag des ANC Südafrika Jacob Zuma
ምስል Stephane de Sakutin/AFP/Getty Images
Eindrücke aus Bamako und Mopti
ምስል Katrin Gänsler
Eindrücke aus Bamako und Mopti
ምስል Katrin Gänsler
Mali Frauen in Nord-Mali
ምስል Bonnie Allen

ጀርመን ከአፍሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት በንግድ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን በፖሊቲካውም መስክ ማጠናከር እንደምትፈልግ ይነገራል። በቅርቡ በተፈጠረው የፖሊቲካ ቀውስ ምክንያት በሁለት የተከፈለችውን ማሊ መልሶ የማረጋጋት ጥረት ውስጥ ጀርመን እየተሳተፈች ነው። በናሚቢያ የጀርመን አምባሳደር ኤጎን ኮሃንኬ፣ በዚኛው የጎርጎሮሳውያን ዓመት የሐምሌ ወር ነው በጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪቃ ተጠሪ ሆነው የተሾሙት። አምባሳደሩ ከተሾሙ ወዲህ በአፍሪቃ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ቀውሶች ታይተዋል። ሆኖም ግን በአህጉሪቷና በጀርመን መካከል ባለው ግንኙነት አዎንታዊ እድገቶች ይታያሉ ይላሉ አምባሳደሩ፣
«አዎንታዊ ገጽታ ላለቸው ጉዳዮች አሁንም ጊዜ እንዳለን ይሰማኛል። በተለይም በኢኮኖሚው በኩል ያለውን ገጽታ ስናይ አበረታች ነው። ለምሳሌ ባሳለፍነው መስከረም ወር መጨረሻ ላይ የጀርመን የውጭ ንግድ ምክር ቤት በናይሮቢ አንድ ጽሕፈት ቤት መክፈቱ አስደሳች ነው። ይህ የሚያሳየው አፍሪቃ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ የጀርመን ምርቶች የሚፈለጉበት ሰፊ ገበያ መሆኑ ነው። ብዙ ያልተሟሉ ቅድመ ሁኔታዎች ቢታዩም ጀርመን በአፍሪቃ ገበያ ውስጥ የበለጠ ለመንቀሳቀስ ያላትን ፍላጎት ለማጠናከር ያስችለናል።»
በጀርመንና አፍሪቃ ግንኙነት ውስጥ በርግጥም ኢኮኖሚያው ግንኙነት ትልቅ ትኩረት የሚሰጠው ነው። ከዚህ ጋር በተያያዘ የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለይም ከጀርመን የምጣኔ ሐብት ልማትና ትብብር ሥራ ሚኒስቴር ጋር ተቀራርቦ ይሰራል። ከዚህም በተጨማሪ ጀርመን ከአፍሪቃ ጋር በፖሊቲካውም ዘርፍ በትብብር ትሰራለች። በተለይም ከአፍሪካ ህብረት፣ ከምዕራብ አፍሪቃ በየነ መንግስታት የኢኮኖሚ ማህበረሰብ፤ ከደቡባዊ አፍሪቃ የልማት ማህበረሰብ ሀገራትና ከሌሎች ጋር በቅርበት መስራትና እንቅስቃሴያቸውን መደገፍ ትሻለች።
በቅርቡ ጊዜ አማጺያን ሰሜናዊ ማሊን ከተቆጣጠሩ ወዲህ ማሊ ውስጥ የተፈጠረውን ፖሊቲካዊ ቀውስ ለመፍታት ጀርመን አንድ ግብረ ኃይል አቋቁማለች። ይህ የማሊ ግብረ ኃይል ከጀርመን የመከላከያ እንዲሁም የልማትና ትብብር ሚኒስቴሮች እና ከሌሎች ተቀራራቢ መሥሪያ ቤቶች የተወጣጡ ባለሙያዎችን የያዜ ሲሆን ባለሙያዎቹ በየጊዜው እየተገናጋገሩ የመረጃ ልውውጥ ያደርጋሉ፣ አምባሳደር ኮናንኬም ይህን ግብረ ኃይል ይመራሉ ፤
«ባለፈው ሳምንት ምን ተፈጠረ ብለን እንጠያየቃለን። ይህ፣ መረጃ የሚገኝበትንም አሰራር ያጠቃልላል። በሌላም መንገድ ምን ዓይነት የእርዳታ እርማጃ ሊወሰድ እንደሚገባ እንመረምራለን። በዚያው መጠን የጀርመን መንግስት ምን ዓይነት እርምጃ መውሰድ እንዳለበት እንመክራለን። »
እክራር የእስላም አማጺያን ሰሜናዊ ማሊን ከተቆጣዘሩ ወዲህ የማሊ አስተዳደር ስንኩል ሆኗል። ጀርመን የሀገሪቷን የሰላም ጥረት ለመደገፍ ከመጀመሪያውኑ ለማሊ የሽግግር መንግስት እውቅና በመስጠት ጀምራለች። አሁን ለሚታየው የማሊ ችግርም የፖሊቲካ መፍትሔ እንዲገኝ እየሰራች ነው ይላሉ አምባሳደር ኮናንኬ፤
«ማሊን በፖሊቲካ መንገድ ለማረጋጋት አሁንም እድል አለ። ከሌሎች የአውሮፓ አጋሮቻችንና ከተባበሩት መንግስታት ጋር በመሆን ማሊ የፖሊቲካ ድርድር መንገድን እንድትከተል ጥረት ማድረጋችንን እንቀጥላለን።»
ሌላው አስፈላጊው ጉዳይ በማሊ ህገ-መንግስታዊ ሥርዓት መመለሱ ነው። ይህ ለጀርመን የትብብር ሥራ መቀጠል ዓብይ መስፈርት ነው። ከዚህም በተጨማሪ ጀርመን የሰብዓዊ እርዳታን ለማሊ ታደርጋለች። በሰሜናዊ ማሊ የሚታዩ ሰብዓዊ ቀውስና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች አሳሳቢ መሆናቸው ይነገራል። ከዚህ ጋር በተያያዘ ጀርመን ለሰብዓዊ እርዳታ የሚውል 52 ሚሊዮን ዩሮ ለመስጠትም ቃል መግባቷ ተገልጿል።

ከሰብዓዊ እርዳታው ጎን ለጎን ጀርመን የጦር ኃይልን ወደ ማሊ ለማዝመት የተያዘውን እቅድ ከሌሎች የአውሮፓ አጋሮቿ ጋር በወታደራዊ ስልጠና ረገድ መደገፍ እንደምትፈልግ ተነግሯል። እንደ አምባሳደር ኮናንኬ ግን ለዚህ ውሳኔ መወሰድ በቅድሚያ በማሊ ውስጥ የሚታዩ ክስተቶች ወሳኝ ናቸው ፣
«ግልጽ የሆነ እይታ እንዲኖረን ማሊ ውስጥ የሚከሰተውን በንቃት መመልከት ይኖርብናል። አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታዎች ግልጽ በሆነ መንገድ ከተቀመጡ፣ የጀርመን መንግስት ወታደሮችን የማሰልጠን ተልዕኮ ላይ ይሳተፋል። የዚህ የአውሮፓ ተልዕኮና የጀርመን ተሳትፎ ግን ጦርን ማዝመት እንዳልሆነ ግልጽ ማድረግ እፈልጋለሁ። ቅድሚያ ማግኘት ይገባል የምንለው ለማሊ የፖሊቲካ መፍትሔ መፈለግ ነው። ይህ ደግሞ የእኛ ብቻ ሳይሆን የማሊና የአፍሪቃም ኃላፊነት ጭምር መሆን አለበት።»
ደቡብ አፍሪቃ ወንጀልን ከመቀነስ አኳያ ጥሩ እምርታ አሳይታለች። አሁን በሰላም ወጥተው መግባቱ ከበፊቱ በተሻለ ሁኔታ እውን ሆኗል። የፖሊስ መረጃ እንደሚያሳይ ከሆነ፣ በደቡብ አፍሪቃ በየቀኑ 42 ሰዎች ይገደላሉ። ከጥቂት ዓመታት በፊት ቁጥሩ ከዚህ የከፋ ነበር። በአማካይ 50 የሚሆኑ ይገደሉ ነበር። ዛሬ የዘረፋና ጠለፋ ወንጀሎችም እንዲሁ ቀንሰዋል። ነገር ግን ሴቶችና ልጆችን ከወንጀል ከመከላከል አንጻር የተለወጠ ነገር አለመኖሩ አስደንጋጭ ሆኗል።
ሉንግስዋ መሜላ አንድ «በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃት» የተሰኘው ማህበራዊ ቡድን አባል ናቸው። መሜላ ጠቅሰው የተናገሩት አንድ ጥናት እንደሚያሳየው በደቡብ አፍሪቃ በየስድስት ሰዓት አንድ ሴት ትገደላለች።

«በቤት ውስጥ የሚደርሰው ጥቃት ትልቅ ችግር ነው፤ ምክንያቱም በጓዳ በድብቅ የሚፈጸም ነውና። ከቤትም ውጪም ቢሆን ከመደፈር ጋር በተያያዘ ትልቅ ችግር እያጋጠመን ነው። ደቡብ አፍሪቃ በርግጥ ተራማጅ ህጎች ያላት ሀገር ናት። ሆኖም ህጎቹ ሥራ ላይ አይውሉም። በወረቀት ላይ የቀሩ ናቸው።»
እነኚህ ህጎች ውጭ መንገድ ላይ የሚጓዙትን ወንዶች የሚመለከትም አይመስልም። እንደ ማሜላ ከሆነ ፖሊሶች፣ ህጉ ሴቶችን የሚከላከል መሆኑን አያውቁም ወይ ደግሞ ጭራሹኑ ደንታ አይሰጣቸውም። እንዲህ ነው፣ ሴቶች ሊከላከላቸው የቆመውን የህግ ከለላ ሳያገኙ የሚቀሩት። ወንጀሉ እንዲጣራ ፖሊሶችን የማሳወቅ እድልንም አያገኙም። ለዚህ ተጠያቂው ህብረተሰቡ ነው ይላሉ ወይዘሮ መሜላ። ህብረተሰቡ ያያውን እንዳላየ አልፎ ወንዶች ሚስቶችና ልጆቻቸውን እንዲደበድቡ ይፈቅድላቸዋል። ከዚህ የሴቶች ጥቃት ልማድ አንጻር የጾታ መብት ተከራካሪው ፓትሪክ ጎዳና የሚሉት ነገር አለ፣

«ከልጅነቴ ጀምሬ ችግሮችን በቡጢ እንዲፈታና ማግኘት የሚሻውን ለማግኘት ጉልበት መጠቀም እንዳለብኝ እየተነገረኝ ነው ያደግኩት። በህጻንነቴ እያለቀስኩ ወደ ቤት እመጣ እንደሆነ፣ የመታኝን ተመልሼ በቡጢ እንድለው እገደድ ነበር። ጉጉሌቱ በምትባል ከኬፕታውን አቅራቢያ በሚትገኘው ከተማ የአባቶችና ልጆች ቀን እየተከበረ ነው። በባህር ላይ በተገነባው አንድ ቤት ውስጥ 2 ወንዶች 20 በሚሆኑ ህጻናት ዙሪያ ይንጎራደዳሉ። ይጨፍራሉ፣ ህጻናቱንም የተለያዩ አዝናኝ ትርዕቶችን ያሳዩዋቸዋል። ይህ የአባቶችና ህጻናት ቀን «ሶንኬ ሶሻል ጃስቲስ ኔትዎርክ» የተባለ ቡድን የሚያዘጋጀው «አንድ ወንድ ይችላል» የተሰኘ ዘመቻ አካል ነው። ሚዛሜ ሴዴሎ እንደሚሉት በዚህ ዘመቻ መሠረት ሴቶች ላይ የሚደርሰው የኃይል ጥቃት እንዲያበቃ ወንዶች ወንዶችን ያስተምራሉ።
«የሶንኬ ተግባር በችግሮቻቸው ላይ እንዲወያዩ ለወንዶች መንገድና ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው። እንዲሁም በቤተሰብ አስተዳደር የወንዶች ሚና ምን ያክል እንደሆነ ማሳወቅ ነው። ወንዶች ልጆቻቸውን ማሳደግና በልጆቻቸው ህይወት ውስጥም ድርሻ ሊኖራቸው ይገባቸዋል። ስለትዳር ጓደኞቻቸው አዎንታዊ አመለካከት እንዲኖራቸውም ለማስቻል ነው። እኒኚህ እዚህ ከምንነጋገርባቸው ጉዳዮች ውስጥ ዋናዎቹ ናቸው ናቸው።»
ሳኔሌ ንኩዌኔ የአባቶችና ልጆች ቀን ላይ ከተሳተፉ 17 የልጅ አባቶች ውስጥ አንዱ ናቸው። ሶስት ልጃገረድ ሴቶች ሲኖራቸው፣ አባቶች ልጆቻውን የማሳደግ ሂደት ውስጥ የበለጠ ኃላፊነት መሸከም አለባቸው የሚል አስተያየት አላቸው፣
«ብዙን ጊዜ ልጆቹን የምትንከባከበው ባለቤቴ ብቻ ናት። ነገር ግን እኛ ወንዶች ሚስቶቻችንን መርዳት አለብን። ይቻላል። ልጆቼን ለማሳደግና ለመንከባከብ ምንም ቢሆን ጊዜ አለኝ።» «አንድ ወንድ ይችላል» የተሰኘው ይህ ዘመቻ በደቡብ አፍሪቃ ከተጀመረ አምስት ዓመታት ሆኖታል። ይህ እንቅስቃሴ በቡሩንዲ በኬኒያ በሞዛምቢክና በናሚቢያ እየተስፋፋ ነው። ይህ አበረታች ለውጥ ነው ይላሉ የሶንኬ ቡድን አባል ፓትሪክ ጎዳና። ምናልባት በጣም ፈጣኝ የሆነ ለውጥ እንዲመጣ መጠበቅም ስህተት ነው። በሴቶችና ልጆች ላይ የሚደርስ ጥቃት ማስወገድ ረዥም ጊዜ የሚወስድ ነው ባይ ናቸው ሚስተር ጎዳና፣«የማህበራዊ እድገት ሂደት ነው እንጂ የአንድ ቀን ክስተት አይደለም። ከተወሰኑ ወንዶች ጋር እሰራለሁ። ራሴንም ለማሻሻል እሰራለሁ። ከዚህ በፊት ማድ ቤት ገብቼ ምግብን ስለማብሰልና ከልጆች ጋር የቤት ሥራን ስለመስራት ማሰብ እንኳ ይከብደኝ ነበር። ዛሬ ግን ይህን ማድረግ ያስደስተኛል።

አፍሪቃ
አፍሪቃምስል shirophoto/Fotolia.com

ገመቹ በቀለ

ተክሌ የኋላ


ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ