1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቻድ በበኮሃራም ላይ የከፈቸው ዘመቻ

ሐሙስ፣ ጥር 28 2007

ቦኮሃራም የተባለው ደፈጣ ተዋጊ ቡድን በናይጀሪያና በአጎራባቾቿ የሚያካሂደው ጥቃት ቀጥሏል ። ቡድኑ ናይጀሪያ ድንበር አቅራቢያ ካሜሩን ውስጥ በሚገኝ መንደር ትናንት ባደረሰው ጥቃት በርካታ ሰዎችን መግደሉ ተዘግቧል ። የካሜሩን መከላከያ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እንዳስታወቁት ግድያው የተፈፀመው በመስጊዶች በየጎዳናውና በመኖሪያ ቤቶች ውስጥ ነው ።

https://p.dw.com/p/1EWEe
Soldaten aus dem Tschad Archiv 2014
ምስል AFP/Getty Images/M. Medina

አሸባሪው ቡድን ቦኮሃራም ጥቃቱን የፈጸመው በቡድኑ ላይ ዘመቻ የከፈቱት የቻድ ወታደሮች በርካታ የቦኮሃራም ቡድን አባላትን መግደላቸው እንደተሰማ ነበር ። በአሁኑ ጊዜ ቻድ በጎረቤት ናይጀሪያ በበኮሃራም ላይ የከፈተችው ዘመቻ የናይጀሪያውያንን ድጋፍ አግኝቷል ። በጎረቤት ናይጀሪያ በአሸባሪዎቹ በቦኮሃራም ደፈጣ ተዋጊዎች ላይ ዘመቻ የጀመረችው ቻድ በአሁኑ ጊዜ በቡድኑ ላይ ጥቃቷን አጠናቅራ ቀጥላለች ። ባለፈው ቅዳሜ የአፍሪቃ ህብረት ቦኮሃራምን ለመውጋት 7500 ወታደሮችን ለመላክ ከተስማማ በኋላ ቻድ ከናይጀሪያ በሚያዋስናት ድንበር ላይ 2ሺህ ወታደሮቿን አስፍራለች ። ከዚህ ሳምንት ሰኞ አንስቶ የናይጀሪያና የቻድ የጦር አውሮፕላኖች የቦኮሃራም ምሽጎችን እየደበደቡ ነው ። ቻድ ቦኮ ሃራምን ከድንበር አካባቢ በማባረር የኤኮኖሚ ጥቅምዋን ማስጠበቅ ትፈልጋለች ። ይህ የቻድ እርምጃ የበርካታ ናይጀሪያውያንን ድጋፍ አግኝቷል ።ከመካከላቸው አንዱ ይህ የሌጎስ ነዋሪ ነው ።
«የቻድ ወታደሮች ናይጀሪያ መግባታቸው መጥፎ ሃሳብ አይመስለኝም ። ምክንያቱም ዓለምዓቀፋዊ ይዘት ያለውን አሸባሪነትን በጋራ ለመዋጋት የምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት የተነጋገሩበት ጉዳይ ነውና ።በአፍሪቃ ሰላምን መልሶ ለማስፈን እስከሆነ ድረስ መጥፎ ሃሳብ አይደለም ።ችግሩ የናይጀሪያ ብቻ ሳይሆን በቻድ በኒዠር በካሜሩን እና በሌሎችም ሃገራት እየተባባሰ በመሄድ ላይ ነው።»
የቻድ ወታደሮች ትናንት በሰሜን ምስራቅ ናይጀሪያዋ ከተማ ጋምባሩ ባደረሱት ጥቃት ቢያንስ 200 የቦኮሃራም ተዋጊዎችን መግደላቸው ተነግሯል ። የቻድ ወታደሮች የቦኮሃራም ሚሊሽያዎችን ቦርኖ ግዛት ውስጥ ወደሚገኙት ጋምቦሩና ናጋላ በተባሉት ከተሞች ወደሚገኙት ምሽጎቻቸው እንዲያፈገፍጉ ማድረጋቸውም ተሰምቷል ። ከአንድ ቀን በፊት ደግሞ የቻድ ወታደሮች ከካሜሩን ኃይሎች ጋር ከጋምባሩ 500 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው በካሜሩንዋ የድንበር ከተማ ፎቶኮል ከቦኮሃራም ጋር ከባድ ውጊያ ገጥመው ነበር ። ቻድ በአሁኑ ጊዜ ይህን አሸባሪ ቡድን ከግዛትዋ ጠራርጎ ማስወጣት ብቻ ሳይሆን ከዚያም የላቀ ዓላማ አላት ። የአፍሪቃ ጉዳዮች አጥኚና የአካባቢው ጉዳዮችን የሚከታተሉት ፕሮፌሰር ኖርቤርት ሳይፈር እንደሚሉት የቦኮሃራም ጥቃት ለቻድም አደጋ ነው ።
«ቻድ በአመዛኙ ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች አቅርቦት ላይ ጥገኛ ናት ። እቃዎቹ በብዛት በናይጀሪያ እና በከፊልም በካሜሩን ወደቦች በኩል ሲሆን ፣ ወደነዚ የሚያመሩት መሥመሮች የሚያልፉት ሰሜን ምሥራቅ ናይጀሪያ በሚገኘው በቦርኖ ግዛቱ በማይዱጉሪ በኩል ነው። ከዚያም ወደ ናይጀሪያው ድንበር ወደ ምዕራቡ ወደ ጋምባሩ እና በካሜሩኑ በፎቶኮል ነው የሚሸጋገሩት ። ጥቃቱ ለቻድ አቅርቦት አደጋ ነው ። እንደሚመስለኝ ቻድ እነዚህ መሥመሮች ተጠብቀው እንዲቆዩ የማድረግ ከፍተኛ ፍላጎት አላት ። »

Anschlag in Gombe, NIgeria 02.02.2015
ምስል Reuters/Afolabi Sotunde


ሳይፈር ቻድ ቦኮሃራምን የምትወጋበት ሌላም ዋነኛ ምክንያት በቻድ ሐይቅ የሚገኘውን የተፈጥሮ ሃብት ከቦኮሃራም ጥቃት ለመከላከል ነው ይላሉ ።በሐይቁ ዙሪያ በሚገኘው አካባቢ በርካታ የካኑሪ ጎሳ አባላት ይኖራሉ ። የዚህ ጎሳ አባላት ቁጥር በናይጀሪያ ከ4 እስከ 5 ሚሊዮን ሲገመት ቻድ የሚኖሩት ደግሞ አንድ ሚሊዮን ይደርሳሉ ።ከቦኮ ሃራም አባላት አብዛኛዎቹ የዚህ ጎሳ አባላት እንደሆኑ ይገመታል ።ቦኮሃራም ብዙው ጊዜ ዓላማውን የማይከተሉ ሆኖም በገንዘብ የሚገዙ ቅጥረኛ ነፍሰ ገዳዮችንም ያሰማራል እንደ ሳይፈር ። ሌላው የዩኒቨርስቲ መምህር ሉስየን ፓምቡ እንደሚሉት ቻድ ቦኮሃራምን የምትወጋበት ሌሎች ሁለት ምክንያቶች አሏት ።
«በመጀመሪያ ቦኮሃራም በተለያዩ ሃገራት እስላማዊ ከሊፋ መመስረት በመፈለጉ ነው ። በሁለተኛ ደረጃ የቻድ ፕሬዝዳንት ኢድሪስ ዴቢ ፣ቻድ በሳህል ቀጣና ለሚገኙና ለማዕከላዊ አፍሪቃ ሃገራት ፀጥታ አስፈላጊ የሆነች ሃገር መሆኗን ለማሳየት ስለሚፈልጉ ነው ,።»
በሃገር ውስጥ ትችት የሚሰነዘርባቸው ዴቢ ካሜሩንንም መርዳታቸው ዝናቸው ከፍ እንዲል ገፅታቸውም እንዲሻሻል ያደርጋል ይላሉ ፓምቡ።

Tschad Präsident Idriss Deby 3.4.2014
ምስል Thierry Charlier/AFP/Getty Images

ኂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ