1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አልቃይዳ በማግሬብ

ረቡዕ፣ ጳጉሜን 2 2003

ራሳቸውን " ጂሃዲስት፣ የቅዱስ ጦርነት ተዋጊዎች ብለው ይጠራሉ። ታማኝና ቁርጠኛ ስለመሆናቸውም ለመሪዎቻቸው ቃል ይገባሉ።

https://p.dw.com/p/RkRF
የመግሪብ አገራትምስል Wikipedia

በአካባቢያቸው የሚገኙ አገዛዞችን በቦምቦችና በአጥፍቶ ጠፊ ጥቃቶች ማስወገድ ይፈልጋሉ። ዓላማቸው አምስት የሰሜን አፍሪቃ አገራትን ማለትም ሞሮኮን፣ አልጀሪያን፣ ቱኒዝያን፣ ሊቢያን እንዲሁም ሞሪታኒያን ባካተተው በማግሬብ አካባቢ በሸሪአ ህግ የሚተዳደሩ መንግሥታትን መመሥረት ነው፤ የሽብርተኛው 'አልቄይዳ በማግሬብ ቡድን አሸባሪዎች። ስለ ቡድኑ አመሠራረት እና ማንነት የዶቼቬለዋ ቻምሴላሲል አያሪ ያዘጋጀችውን ዘገባ ሂሩት መለሰ አጠናቅራዋለች።

በአልጀሪያዋ መዲና በአልጀርስ ቀኑ እየመሸ ነው ። ፀሀይ ስትጠልቅ ሙአዚኑ አዛን ያደርጋል ።

Alltag in der Maurice Audin Straße in Algier
አልጀርስምስል DW

መንገዶቹ በድንገት ጭር፣ ፀጥ እረጭ አሉ። የቀኑ ፆም የሚያበቃበት የማፍጠሪያ ሰዓት ነው። እንደ ሌላው የሙስሊም ዓለም በአልጀሪያም የፆሙ ወር ሮመዳን ገብቷል። በመሠረቱ ሮመዳን የሙስሊሞች እምነት የሚንፀባረቅበት ወር ነው። እ.ጎ.አ በ 1990 ዎቹ የርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ላለፉ ለበርካታ አልጀሪያውያን ግን ወሩ የፍርሃት ወር ነው። ከእርስ በርሱ ጦርነት በኋላም እጎአ ከ1992 እስከ 2000 በሙስሊሞች የፆም ወራት ደም የፈሰሰባቸው የሽብር ጥቃቶች ደርሰዋል። ጥቃቶቹን የሚያቀነባበረውም "አልቄይዳ በማግሬብ" በምህፃሩ AQIM የሚባለው የአካባቢው የአልቄይዳ የሽብር መረብ አካል ነው። AQIM ለአብዛኛዎቹ ጥቃቶች ሃላፊነቱን የወሰደ ሲሆን የጥቃት አድራሾቹን ማንነትም በኢንተርኔት ይፋ ያደርጋል። AQIM እ.ጎ.አ በ2007 መጨረሻ ከትልቁ የአልጀሪያ አሸባሪ ድርጅት ሳላፊስት የጥሪና የውጊያ ቡድን በፈረንሳይኛው ምህፃሩ GSPC የተፈጠረ ቡድን ነው።

እጎአ በ 1990 ዎቹ ማለቂያ ላይ ይኽው ቡድን በውስጡ ከነበረው ከታጠቀው እስላማዊ ጦር GIA አፈንግጦ ወጣ። GIA በአልጀሪያው የርስ በርስ ጦርነት ወቅት ለተጨፈጨፉት በሺህዎች ለሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰዎች ተጠያቂ ነው ይባላል። የአካባቢው የፖለቲካ አጥኚና ተንታኝ ሞሮኳዊው ሞሀመድ ዳሪፍ የተለያዩ በማግሬብ አገሮች የሚኖሩ ጂሃዲስቶችን ከአልቄይዳ ጋር ህብረት በመፍጠር በ GSPC አባላት የበላይ አመራር ለማቀናጀት ሃሳብ ነበር።

«በአልቃይዳ ዘንድ ርዕዮት መሰረታዊ ሚና አለው። ይህም በማይለወጥ ድርጅታዊ እምነት የተመሠረተ ሲሆን የርዕዮቱ ዋና መመሪያም ኢአማንያን በሚባሉና ከራሱም እምነት ባፈነገጡት ላይ የኃይል እርምጃ መውሰድ ነው።»

ርዕዮታዊ አንድነት ቢኖርም በድርጅታዊ አመራርና አያያዝ ረገድ አፍጋኒስታን የሚገኙትና ፓኪስታን ውስጥ እና አካባቢው ያሉት ይለያሉ። ዳሪፍ በአረቦቹ የማግሬብ ሃገራት እያደገ የሄደውን ጅሃዳዊነት እ.ጎ.አ ከ 1979 እስከ 1989 የዘለቀውን የሶቭየት ህብረት የአፍጋኒስታን ወረራ በመቃወም ከአፍጋኖች ጎን ለመዋጋት ወደ አፍጋኒስታን ከዘመቱ በጎ ፈቃደኞች መመለስ ጋር ያያዙታል። እጎአ በ1989 የሶቭየት ጦር ወታደሮቹን ከአፍጋኒስታን ሲያስወጣ የቅዱስ ጦርነት ተዋጊዎች የሚባሉት ሙጅሃዲኖች ወደ የሀገራቸው ተመለሱ።

«የአፍጋኒስታኑ ጦርነት እንዳበቃ የአፍጋኒስታንና እና የፓኪስታን መንግሥታት ቅዱስ ጦረኞቹን ወደሀገራቸው ለመላክ ተገደዱ። ብዙዎቹ ወደ የሃገራቸው ተመለሱ። ከነዚህም አብዛኛዎቹም የአልጀሪያ ተዋጊዎች ነበሩ።»

በአሁኑ ሰዓት የ AQIM ተዋጊዎች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ ትክክለኛ መረጃ የለም። የአልጀሪያ ባለሥልጣናት የታጣቂ ሚሊሽያዎቹን ቁጥር ከሶስት መቶ እስከ ስምንት መቶ ይገምታሉ። አላማቸውም ተንታኙ ሞሀመድ ዳሪፍ እንደሚሉት አገዛዙን በማስወገድ ሃይማኖትን መመሪያዉ ያደረገ መንግሥት መመሥረት ነው። አላማቸውን ከግብ ማድረሻ መንገዳቸውም አመፅ ነው። የ AQIM ዋነኛ የገቢ ምንጭም ወደ አካባቢው የሚመጡ ቱሪስቶችንና የልማት እርዳታ ሠራተኞችን በማገት የሚያገኙት ገንዘብ ነው።

በዚህ ዓመት አልቄይዳን ጨምሮ ሁሉንም ያስገረመ የቱኒዝያና የግብፅ ህዝባዊ አመፅ ሁለት አምባገነን መሪዎችን ከሥልጣን አውርዷል። ሁለቱም ሃገራት ለውጥ በሰላማዊ መንገድ ሊመጣ እንደሚችል አሳይተዋል። ይህም እንደ ዳሪፍ አባባል የአልቄይዳን ርዕዮተ ዓላማዊ መርሆዎች አናግቷል።

ቻምሴላሲል አያሪ

ሂሩት መለሰ

ሸዋዮ ለገሰ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ