1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አማራ ክልል በጦርነት 2 ሚሊዮን ኼክታር አልታረሰም

ረቡዕ፣ ጥር 11 2014

ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) አማራ ክልል ውስጥ ከ2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ የእርሻ መሬት እንዳይታረስና ሰብል እንዳይሰበሰብ ማድረጉ፤ 40 ሚሊዮን ኩንታል የሰብል ምርትም እንዳይለማ ማድረጉን የክልሉ ግብርና ጽ/ቤት ዐስታወቀ። መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ለክልሉ ግብርና እና ጤና ጽ/ቤቶች የምርጥ ዘርና የመድኃኒት ድጋፍ አድርገዋል፡፡

https://p.dw.com/p/45huO
Hilfslieferung für Krieg betroffene Region Amhara
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

ለክልሉ ግብርና እና ጤና ጽ/ቤቶች ድጋፍ ተሰጥቷል

ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) አማራ ክልል ውስጥ ከ2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ የእርሻ መሬት እንዳይታረስና ማሳ ላይ የነበረ ሰብል እንዳይሰበሰብ ማድረጉ ተገለጠ። በዚህም የተነሳ በክልሉ 40 ሚሊዮን ኩንታል የሰብል ምርት እንዳይለማ ማድረጉን የክልሉ ግብርና ጽ/ቤት ዐስታውቋል። መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ለክልሉ ግብርና እና ጤና ጽ/ቤቶች የምርጥ ዘርና የመድኃኒት ድጋፍ አድርገዋል።

Hilfslieferung für Krieg betroffene Region Amhara
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

የሕወሓት ኃይሎች በምስራቅ አማራ ወረራ በፈፀሙበት ወቅት ከ2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት እንዳይለማ በማድረጉ በክልሉ ከፍተኛ የምርት ቅናሽ መታየቱን የአማራ ክልል ግብርና ጽ/ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አበጀ ስንሻው ተናግረዋል። በግብርናውና በሌሎችም ዘርፎች የተፈጠረውን ውድመትና ዝርፊያ ለማሟላት መንግሥትና መንግሥታዊ ልሆኑ ተቋማት ሰፊ ርብርብ እያደረጉ ሲሆን፤ በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን አስተባባሪነት የመድኃኒት፣ የምርጥ ዘርና ለአካል ጉዳተኞች የሚያገለግሉ የተሸከርካሪ ወንበሮች (wheelchairs) ድጋፍ መደረጉን የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ጂማ ዲልቦ ተናግረዋል። በርዳታ የተሰጠው የስንዴ ምርጥ ዘር በሰሜን ወሎ ለሚገኙ አርሶ አደሮች ለመስኖ ልማት እንደሚውል የግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊው አቶ አበጀ አረጋግጠዋል። ርዳታውን ከሰጡት ድርጅቶች መካከል የኬር ኢትዮጵያ የአማራ ክልል አስተባባሪ ጎበዜ አያለው በግብርና ለተጎዱ አካባቢዎች የሚሆን 4 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ 695 ኩንታል ምርጥ የስንዴ ዘር ለክልሉ ግብርና ጽ/ቤት ማስረከባቸውን አአስረድተዋል።

Hilfslieferung für Krieg betroffene Region Amhara
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

በኢትዮጵያ የፋሮ ፋውንዴሽን ዳይሬክተር ዶ/ር ኤርሚያስ ሀብቴ ከ1 ሚሊዮን 400 ሺህ በላይ ዋጋ ያላቸው መድኃኒት መለገሳቸውንና በቀጣይም እገዛ እንደሚያደርጉ አመልክተዋል፡፡
የአዲስ ጉዞ የኢትዮጵያ ተወካይ አቶ ታምራት በላይ በበኩላቸው ከ70 በላይ የአካል ጉዳተኞች ተሸከርካሪ ወንበሮችን ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡
የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር መልካሙ አብቴ በጦርነቱ ምክንያት በክልሉ በ2ሺህ 350 የጤና ተቋማት ላይ ዝርፊያና ውድመት መድረሱን አስታውሰው፣ ዛሬ የተደረገው የመድኃኒትና የተሸከርካሪ ወንበሮች ድጋፍ ከፍተኛ እገዛ ይኖረዋል ብለዋል።

ዓለምነው መኮንን
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ