1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አያሌዉ ሙዚቃ ቤት ጋ እንገናኝ

እሑድ፣ ሐምሌ 21 2011

«በ 50 ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ጋሽ ጥላሁንን፤ አለማየሁ እሸቴን እና ታምራት ሞላን የመሳሰሉ እንቁዎች ሰምቼ ከሙዚቃ ፍቅር ያዘኝ» ድምፃዊ የግጥምና ዜማ ደራሲ እንዲሁም የሙዚቃ አቀናባሪ አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን። ከሁሉ ከሁሉ የአዲስ አበቤ ፍቅረኛሞች ቀጠሮአቸዉ አያሌዉ መስፍን ሙዚቃ ቤት ጋር እንደነበር የሚያስታዉስ ያስታዉሰዋል።

https://p.dw.com/p/3Mqb4
Musiker Ayalew Mesfin
ምስል Privat

አያሌዉ ሙዚቃ ቤት ጋ እንገናኝ

ድምፃዊ የግጥምና ዜማ ደራሲ እንዲሁም የሙዚቃ አቀናባሪ ነው ፤ አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን። ወሎ የሙዚቃ ባለ ኃብቶችን የሙዚቃ ምሁራንን፤ ያፈራች ሃገር መሆንዋ አብዛኞች ይመሰክሩላታል። ወሎ ካፈራችዉ አያሌዉ መስፍን ከመሳሰሉ ከያኒዎች መካከል በባህል ሙዚቃ ገናና ስምን የተከለዉ የማሲንቆዉ ቀንድ፤ በማሞካሸት የጥበብ ጀማሪ አሰፍዬ አባተ ይባል የነበረዉ፤  አንጋፋዋ ድምፃዊ ማሪቱ ለገሰ፤ አለማየሁ እሸቴ፤ ኃብተሚካኤል ደምሴ ከአብዛኞቹ የጥበብ እንቁዎች እጅግ ጥቂቶቹ ናቸዉ። ወሎ ከያኒዎችን ብቻ ሳይሆን አራቱን የኢትዮጵያ የሙዚቃ ቅኝቶች ያፈራች እንደሆነችም ይነገርላታል። «በ 50 ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ጋሽ ጥላሁንን፤ አለማየሁ እሸቴን እና ታምራት ሞላን የመሳሰሉ እንቆዎች ሰምቼ ከሙዚቃ ፍቅር ያዘኝ» ያለን አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን፤ ስለአገር ፍቅር ስለፍትህ፤ ስለአንድነት ስለፍቅር አዚሞአል፤ ገጥሞአልም። በተለይ በሙዚቃዎቹ ከኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት ጋ በጋራ የሃገር ድንበርን ማስከበሩ ይነገርለታል። በደረሳቸዉ ግጥሞች በርካታ ከያንያን ተወዳጅ ዜማቸዉን ለአድማጭ ጆሮ አድርሰዉ ታዋቂ ሆነዋል። ከሁሉ ከሁሉ የአዲስ አበቤ ፍቅረኛሞች ቀጠሮአቸዉ አያሌዉ መስፍን ሙዚቃ ቤት ጋር እንደነበር የሚያስታዉስ ያስታዉሰዋል። ምን እሱ ብቻ እንዲህ እንዳሁኑ የእጀታ ስልክ ኖሮ፤ የኢንተርኔት አገልግሎት ከሞላ ጎደል ተስፋፍቶ «ሜሴጅ አድግ አድርጊልኝ» በማይባልበት በዝያ ዘመን ከክፍለሃገር የመጡ ኢትዮጵያዉያን አያሌዉ ሙዚቃ ቤት መገናኛቸዉ ነበር። የመዲናዋም ወጣቶች ቢሆኑ በአያሌዉ ሙዚቃ ቤት በራፍ ግራና ቀኝ ከቆመዉ ነጎድጓድ ድምፅን ከሚተፋዉ አምፕሊፋየር «አልያም የድምፅ ማጉያ » በተለይ አዲስ ሙዚቃ ተለቀቀ ከተባለ አካባቢዉ ላይ ቆመዉ ማድመጫቸዉ ነበር፤ የሆነ ሆነና አንጋፋዉ ሙዚቀኛ አያሌዉ መስፍን የት ይሆን? የሙዚቃዉን መድረክ ተዉዉ እንዴ?  

አዜብ ታደሰ

ተስፋለም ወልደየስ