1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲሱ የልማት እርዳታ መርኅ፧

ዓርብ፣ መጋቢት 12 2000

የጀርመን መንግሥት፧ በአሁኑ ጊዜ ከልማት እርዳታ አኳያ የሚከተለውን የአመራር ዘይቤ፧ በአዲስ መልክ ለማዋቀር ተናሳስቷል። በልማት ተራድኦ የተካተቱት አገሮች ቁጥር፧ ከአሥር ዓመት በፊት፧ ወደ 120 ይጠጋ እንደነበረ ቢታወቅም፧ አሁን አኀዙ፧ ከ 60 በታች ነው ዝቅ እንዲል የተደረገው።

https://p.dw.com/p/E0ZG
በጀርመን የልማት እርዳታ፧ ንፁህ የሚጠጣ ውሃ ለማግኘት፧ በኒዠር ጉድጓዶች ሲቆፈሩ፧
በጀርመን የልማት እርዳታ፧ ንፁህ የሚጠጣ ውሃ ለማግኘት፧ በኒዠር ጉድጓዶች ሲቆፈሩ፧ምስል picture-alliance / dpa/dpaweb
የልየልማት ተራድኦው ስልትም ተቀይሯል። የዶቸ ቨለ ባልደረባ፧ Johannes Himmelreich ያቀረበውን ጽሑፍ ተክሌ የኋላ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል።
የልማት እርዳታን በተመለከተ የወቅቱ መሪ ቃል የመርኀ-ግብር ስልት የተሰኘው ሆኗል። አሁን ለጋሽ መንግሥታት ሳይሆኑ፧ የአንድ ተረጂ አገር ነው በልማት ረገድ ምን ማድረግ እንደሚፈልግ መርኀ-ግብር የሚያወጣው። ይህ አዲስ የአሠራር ስልት፧ ከተጀመረ ረጅም ጊዜ የሆነውን፧ ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ የተፈጸመውን ተግባር የሚመለከት አይደለም። የጀርመን ልማት-ነክ ፖለቲካ፧ የልማት ተራድኦ እስካሁን የተመራበት ሂደት፧ በዛ ያሉ ፕሮጀርቶች የተጀመሩበት አሠራር፧ እንደሚገባውና እንደታሰበውም ያን ያህል አልሠመረም። የጀርመን የልማት ተራድኦ ሚንስቴር ባልደረባ Hildegard Hoven..................
«የልማት ፕሮጀክቶችን በመደገፍ ረገድ ችግሮች ያጋጠሙት፧ ለጋሽ መንግሥታት፧ ገንዘብ ወጪ የሚደረግባት አንድ ፕሮጀክት የሚያዋጣ፧ ዘላቂ ጠቀሜታ የሚሰጥ፧ መሆን-አለመሆኑን ሳያረጋግጡ፧ የተለያዩ ተግባሮችን በመወጠናቸው ነበር። ትምህርት ቤት መሥራት ብቻ ሳይሆን መምህራንም ያስፈልጋሉ። በጤና ጥበቃም ረገድ፧ መድኀኒት አብሮ ነው መቅረብ ያለበት። ያም ሆነ ይህ፧ በአንዳንድ ዘርፎች፧ የልማት ፕሮጀክቶች፧ በእርግጥ የሠመሩና ዘላቂነት ያላቸው አልነበሩም። የእኛም የተለያየ የፕሮጀክት ሥራ ውጥን፧ በጭፍኑ የተመራ ነበር።«
በውሃ ኃይል የሚሠራ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ አውታር ለመትከል፧ በሚወጣ ገንዘብ ሠራተኞችንም አብሮ ማሠልጠን ይቻላል። የራስን ሠራተኛ በሚፈለገው ሙያ ሳያሠለጥኑ ከሌላ አገር መዋስም ሆነ መቅጠር የማይበጅ በመሆኑ፧ ያ ዓይነቱ አሠራር ወደፊት እንዲቀጥል አይደረግም። ለሀገራቸው የልማት አቅድ የሚያወጡ መንግሥታት፧ ፕሮጀክቱን በተመለከተ፧ መመካከርና ማስተባበር ይጠበቅባቸዋል። ይህም ሲሆን፧ ፕሮጀርቶች፧ በተጠናከረ መልክ፧ ኀላፊነትም በሚሰማቸው ወገኖች ሊመሩ ችላሉ። ለምሳሌ ያህል፧ ገንዘብ ለጋሽ የሆነ መንግሥት፧ የበጀት ድጎማ ሲያደርግ ተቀባዩ መንግሥት ለተጨባጭ ጉዳይ ያውለዋል። የበጀት እርዳታ የሚባለው ይህ ዓይነቱ ነው። አሁንም ሂልደጋርድ ሆፈን፧.........
«የበጀት እርዳታ ሲባል፧ እንዲሁ ገንዘብ መስጠት፧ ተቀባዩም፧ እንዳሻው ለፈለገው ጉዳይ እንዲያውለው ማድረግ ማለት አይደለም። ተቀባዩ ለግንባታ የሚበጅ አመርቂ ሐሳብ ይዞ ነው፧ ወደ ለጋሹ መንግሥት መቅረብ የሚኖርበት። የበጀት እርዳታ፧ ጠንከር ያለ ክትትልና ቁጥጥር የሚደረግበት፧ ተቀራርቦ ሰፊ ውይይት በማካሄድም፧ ከተሳሳተ መንገድ መመለስ የሚቻልበት ነው።«
ከሞላ ጎደል ገሚሱ የልማት ተግባር በአሁኑ ጊዜ፧ በመርኀ-ግብር ነው የሚካተተው። ጀርመን በያመቱ ከ 300 ሚልዮን ዩውሮ በላይ ነው ለበጀት እርዳታ የምትሰጠው። ትኩረት የሚሰጠው ለአፍሪቃ ክፍለ-ዓለም፧ በዚሁም ክፍለ ዓለም ደግሞ፧ ታንዛንያን፧ ኢትዮጵያን፧ ዛምቢያንና ሞዛምቢክን ለመሳሰሉ አገሮች የተለየ አስተያይ ነው የሚደረገው። አዲሱ የልማት እርዳታ ነክ ፖለቲካ፧ ለሲቭሉ ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምን ትርጓሜ ይኖረው ይሆን? በጀርመን የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች ኮሚቴ ሊቀመንበር ወይዘሮ Claudia Warning..........
«ሲቭሉ ማህበረሰብ ትንሽ የንቁ ዘበኛ ያህል ሚና ነው ያለው። እዚህ ላይ ሲቭል ማኅበረሰብ ሲባል፧ በልማት ዘርፍ የሚገኙ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች ብቻ ማለት አይደለም። የኩባንያዎች ማኅበራት፧ የግብርና፧ የንግድና የኢንዱስትሪ ሠራተኞች ማኅበራት፧ ምሁራን፧ እነዚህና የመሳሰሉት፧ የሲቭል ማኅበረሰብ ሊባሉ ይችላሉ። በተግባር ለሚረጋገጥ ዴሞክራሲ፧ እነዚህ የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ተፈላጊዎች ናቸው።«
በአዲሱ ተራድኦ፧ የበጀት ድጋፍ በማቅረብ፧ እንዴት ሲቭሉን ማኅበረሰብ መርዳት ይቻላል? Hildegard Hoven........
«የበጀት እርዳታውን አጠቃቀም፧ ለሲቭሉ ማኅበረሰብ እንዲበጅ ማድረግ፧ የሀገሩ በጀት ግልጽ እንዲሆን ያግዛል። በመሠረቱ፧ ዓመታዊው በጀት፧ በአዲስ አቅድ እንዲያዝ፧ የሚወጣበትም ምክንያት አሳማኝ ሆኖ ድጋፍ እንዲሰጠው፧ ሲቭሉ ኅብረተሰብም፧ በጀቱን ተግባራዊ እንዲያደርገው የሚያስችል ይሆናል።«
ፓሪስ ውስጥ፧ እ ጎ አ በ 2005 ዓ ም፧ እርዳታ ለጋሽ መንግሥታት፧ የልማት እርዳታን ከልማት አቅድ ጋር እንዲተሣሠር መወሰናቸው አይዘነጋም። ያን መሰሉ ጉባዔ፧ በመጪው መስከረም ወር አክራ፧ ጋና ውስጥይካሄዳል። የሲቭሉ ማኅበረሰብም የወደፊት መጻዔ-ዕድልን በጋራ መወሰን ይቻል ዘንድ ችሎታውንና አቋሙን አጠናክሮ ይቀርባል። Hildegard Hoven...............
የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች እጅግ ተጠናክረው በሚንቀሳቀሱባቸው አካባቢዎች፧ የማስተባበር እክልም ያጋጥማል። አፍጋኒስታንን በተመለከተ ውይይት አካሂደን ነበር። በዚያ የተሠማሩ በዛ ያሉ የመንግሥት ያልሆኑ ድርጅቶች አሉ። ነገር ግን የአፍጋኒስታን ተቋማት፧ ሥራቸውን ለመመርመር፧ እነርሱም አስተዋጽዖ በማድረግ፧ ለውጥ ማሳየት የሚችሉበት ሁኔታ ፈጽሞ የለም።«
አቅድ ያለው የልማት መርኅና የሥራ ውጥን፧ ሲቭሉን ማኅበረሰብ ተጠናክሮ እንዲቀርብና የመንግሥትን ተግባር በጥሞና እንዲመረምር ያችለዋል። በፕሮጀክቶች ላይ ብቻ በመተባባር የሚወሰን አይሆንም። አሁንም Claudia Warning.........
«ይህ ማለት ምንድን ነው!? እኛ እንደ ሲቭል ማኅበረሰብ፧ መታገል ተግባራችን ነው። የአርሶ-አደሮችን ማኅበር በማደራጀት ብቻ፧ መወሰን በቂ አይደለም። በይበልጥ ተጠናክረን፧ ማኅበሮቻችንን በማስፋፋትና በማስተሣሠር፧ ላቅ ያለ ተግባር ማከናወን እንደምንችል ማሥመስከር ይኖርብናል። ይህ ደግሞ፧ ለጠቅላላው ኅብተሰብ የሚጠቅምና ለዴሞክራሲ ግንባታ የሚበጅ ነው የሚሆነው።«