አዲስ አበባ፤ የአፍሪቃ እና የአዉሮጳ ኅብረት ትብብር ጉባኤ
ሐሙስ፣ መጋቢት 29 2008የአፍሪቃ እና የአዉሮጳ ኅብረት ከ9 ዓመታት በፊት ሊዝበን ላይ ባካሄዱት ጉባኤ ለትብብራቸዉ የጋራ ስልት ቀይሰዉ አጽደቀዋል። በየዓመቱ በሚያካሂዱት ስብሰባም በተለይ ከጎርጎሪዮሳዊዉ 2014 እስከ 2017 ዓ,ም የቀየሱትን ስልት በአምሥት ዘርፎች ማለትም በሰላም በጸጥታ፤ በዴሞክራሲ፤ እንዲሁም መልካም አስተዳደር እና ሰብዓዊ መብቶችን በተመለከተ በዉይይት እና ትብብር ተግባራዊ ለማድረግ አቅደዋል። በጉባኤዉ ላይ የተገኙት የአዉሮጳ ኅብረት የዉጭ ጉዳይ ኃላፊ ፌዴሪካ ሙገሪኒ የኅብረቱ እና የአፍሪቃ ትብብር እና ዉይይት ስደተኞችን ከመከላከል የዘለለ መሆኑን አመልክተዋል።
«የስደት ጉዳይ አንደኛዉና ቁልፍ የትብብራችን ዘርፍ ነዉ። ሆኖም ግን ብቸኛዉ እና እጅግ አስፈላጊዉ እንዳልሆነ ግን በግልፅ አፅንኦት መስጠት እፈልጋለሁ። ምክንያቱም በዛሬዉ ጉባኤ መጀመሪያ ላይ አብዛኞቻችን እንደገለጽነዉ የትብብራችን አቅጣጫ ብዙ እና ከኤኮኖሚዉ ጉዳይ እና ከሥራ መስክ ፈጠራዉ አንስቶ ሁሉም ጠቃሚዎች ናቸዉ።»
የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳዮችና የደህንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ ፌደሪካ ሞጎሮኒ ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት የአውሮጳ ህብረት ከ13 የአፍሪቃ ሃገሮች ጋር በስደተኞች ጉዳይ ላይ አብሮ ለመሥራት ስምምነት ላይ ደርሷል ።
የአፍሪቃ ኅብረትና የአውሮጳ ኅብረት በጋራ በሚሰሩባቸው የተለያዩ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ውይይት ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ አካሄዱ ። ዛሬ ከተነጋገሩባቸው ጉዳዮች መካከል ባለፈው ዓመት የተጀመረው ሁለቱ ወገኖች በሰደተኞች ጉዳይ ላይ በጋራ የሚያከናውኑት ተግባር ይገኝበታል ። የአውሮፓ ኅብረት የውጭ ጉዳዮችና የደህንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ ፌደሪካ ሞጎሮኒ ዛሬ አዲስ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገሩት የአውሮጳ ኅብረት ከ13 የአፍሪቃ ሃገሮች ጋር በስደተኞች ጉዳይ ላይ አብሮ ለመሥራት ስምምነት ላይ ደርሷል ። ጋዜጣዊ መግለጫውን የተከታተለው የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ ዝርዝሩን ልኮልናል ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ