1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዳጊ አትሌቶቹ ወደ ፖላንድ

ዓርብ፣ ሐምሌ 8 2008

እድሜያቸው ከ20 ዓመት በታች የኾኑ ኢትዮጵያውያን አዳጊ አትሌቶች ፖላንድ ውስጥ በሚኪያሄደው ዓለም አቀፍ ውድድር ለመሳተፍ ነገ ወደ ፖላንድ ይበራሉ። አብዛኛዎቹ አትሌቶች በውጭ ሃገር በተለይ በአውሮጳ ሲወዳደሩ የፖላንዱ ፉክክር የመጀመሪያቸው ይኾናል።

https://p.dw.com/p/1JP3x
Symbolbild Leichtathletik Laufen
ምስል picture-alliance/dpa/B. Thissen

አዳጊ አትሌቶች ወደ ፖላንድ

እድሜያቸው ከ20 ዓመት በታች የኾኑ አዳጊ አትሌቶች የሚሳተፉበት የዓለም አትሌቲክስ ስፖርት ፉክክር በፖላንድ ቢድጎሲሽች ማክሰኞ፤ ሐምሌ 12 ቀን፣ 2008 ዓ.ም ይጀመራል። በተለያዩ የአትሌቲክስ ስፖርት ዘርፎች ለመወዳደርም ኢትዮጵያውያን አዳጊ አትሌቶችን ያቀፈው ቡድን ነገ ወደ ቢድጎሲሽች እንደሚያቀና ተገልጧል። በረዥም ርቀት፤ በመካከለኛ እና አጭር ርቀት የሩጫ ፊፉክክር እንዲሁም በመሰናክል ሩጫ የሚሳተፉት አዳጊ ወጣቶች ቁጥራቸው 23 ሲሆን፤ በተጨማሪም የርምጃ ተፎካካሪዎዎችም በቡድኑ ታቅፈዋል። ውድድሩ ከብራዚሉ የኦሎምፒክ ፉክክር 17 ቀናት ቀደም ብሎ የሚከናወን ነው። በስልክ ያነጋገርናቸው አዳጊ ወጣት አትሌቶች በውድድሩ አሸናፊ ለመሆን ተገቢውን ዝግጅት እንዳከናወኑ ገልጠዋል።

የ16 ዓመቷ ታዳጊ አትሌት ዝናሽ ተስፋዬ ፖላንድ ውስጥ ኢትዮጵያን ወክላ የምትወዳደረው በ400 ሜትር ርቀት ነው። ከኢትዮጵያ ውጪ ተወዳድራ አታውቅም፤ ኾኖም ግን በውድድሩ አንደኛ ለመውጣት ጥሩ ልምምድ እንዳደረገች ገልጣለች።

የሴቶች 400 ሜትትር የሩጫ ሽቅድምድም ግማሽ ፍጻሜ በፖላንድ የሚከናወነው ውድድሩ በተጀመረ በሁለተኛው ቀን ረቡዕ ነው። ፍጻሜው ደግሞ ሐሙስ ማታ ይከናወናል።

Fahne IAAF Symbolbild
ምስል picture-alliance/dpa/A. Filippov

አትሌት ትዕግስት ከተማ እንደ አትሌት ዝናሽ የ16 ዓመት አዳጊ አትሌት ናት። የምትወዳደረው በመካከለኛ ርቀት፤ ማለትም በ800 ሜትር የሩጫ ዘርፍ ነው። ትዕግስት ከዝናሽ ጋር በዕድሜ ቢመሳሰሉም ውጪ ሃገር ወጥቶ በመወዳደር ግን ይለያያሉ። ትዕግስት ከዚህ ቀደም ሁለት የአፍሪቃ ሃገራት ሄዳ የመወዳደር ዕድል አግኝታለች።

ቀደም ሲል ለደን እና ዱር አራዊት ቡድን ተሰልፋ ትወዳደር የነበረችው ትዕግስት አሁን በዓለም አቀፍ ውድድር ኢትዮጵያን ወክለው ከሚሳተፉ አዳጊ ወጣት አትሌቶች አንዷ መሆን ችላለች። ከበፊት አንስቶ በግሏም ከፍተኛ ጥረት እንደምታደርግ የጠቀሰችው የሴቶች የ800 ሜትር የሩጫ ፍክክር በውድድሩ መክፈቻ ቀን ማክሰኞ ረፋዱ ላይ ይከናወናል። ግማሽ ፍጻሜ ውድድሩ በበነጋታው ረቡዕ አመሻሹ ላይ ይደረግና የፍጻሜው ፍልሚያ ሐሙስ ማታ ይኾናል።

የ17 ዓመት አዳጊ አትሌት ጌትነት ዋለ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፉ ውድድር የሚወክለው በ3000 ሜትር የመሰናክል የሩጫ ውድድር ነው። ወጣት ጌትነት ከሀገር ውጪ ተወዳድሮ አያውቅም። ኾኖም አሰላ ውስጥ በተከናወነው የወጣቶች ፉክክር እና በኢትዮጵያ የአሸናፊዎች ውድድር ብቃቱን አስመስክሯል።

ከወጣት አትሌት ጌትነት ጋር ቃለ መጠይቁን ያደረግነው ትናንት ነበር። ጌትነት ኢትዮጵያን ወክሎ ለመወዳደር በቡድኑ ከመታቀፉ በፊት በትምህርት ቤት ውድድሮች ጠንካራ ተፎካካሪ መኾኑን ያወቁት የስፖርት መምህሩ ናቸው።

አትሌት በየኑ ደገፋ ደግሞ የ17 ዓመት አዳጊ ወጣት ናት። የምትወዳደረው በ3000 ሜትር የሩጫ ፉክክር ነው። ከኢትዮጵያ ውጪ ስትወዳደር የፖላንዱ ፉክክር የመጀመሪያዋ ይኾናል። ሀገር ውስጥ ግን በአሰላ ውድድር ዘንድሮ አንደኛ መውጣት ችላለች። የፖላንዱ ዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ውድድር ማክሰኞ፤ ሐምሌ 12 ቀን፣ 2008 ዓ.ም ጀምሮ በስድስተኛ ቀኑ እሁድ ይጠናቀቃል።

Symbolbild Hürde
ምስል picture-alliance/Lehtikuva

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ