1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አፍሪቃ እና የአደንዛዥ እፅ ዝዉዉር

ረቡዕ፣ ጥቅምት 6 2006

ዚምባቡዌ ላይ የአደንዛዥ እፅ ዝዉዉርና አጠቃቀምን አስመልክቶ የሚካሄደዉ ጉባኤ፤ መሪዎቹ ወሳኝ ርምጃ ካልወሰዱ የአህጉሩን መረጋጋት ሊጎዳ እንደሚችል አመለከተ። የምዕራብ አፍሪቃ የኤኮኖሚ ማኅበረሰብና በተመድ የእፅ ተከታታይ ጽ/ቤት አፍሪቃ ዉስጥ ሕገ ወጥ የአደንዛዥ እፅ ዝዉዉርን ለመግታት የሚያስችል አዲስ ርምጃ ላይ እየመከሩ ነዉ።

https://p.dw.com/p/1A1CS
ምስል Erika Santelices/AFP/Getty Images

የአፍሪቃ ኅብረት የማኅበራዊ ጉዳይ ኃላፊ ዶክተር ኦላዋሌ ማየጉን እንደሚሉት አፍሪቃ በአህጉር ደረጃ የHIV ቫይረስ ስርጭትን ለመግታት ባደረገችዉ ጥረት ዉጤት እንዳስመዘገበች ሁሉ፤ ቀጣይ ዘመቻዋን ሕገ ወጥ የአደንዛዥ እፅ ዝዉዉርንና አጠቃቀምን መግታት መሆን ይኖርበታል፤

«የበሽታዉ ስርጭት በአዲስ መልክ ይነሳል የሚል ፍራት ከኖረ ሊሆን የሚችለዉ የአደንዛዥ እፅ ተጠቃሚዎችን በመርፌ በመዉጋት ነዉ የሚሆነዉ። ከሕገ ወጥ የእጽ ዝዉዉርና ከተደራጀ ወንጀል የሚገኘዉን በርካታ ገንዘብ ዴሞክራሲና መልካም አስተዳደርን ለማደናቀፍና ምርጫዎችን ለማወክ እያዋሉት ነዉ። በድፍረት ዴሞክራሲን ለማደናቀፍና ወደኤኮኖሚያችን ገብቶ የሚፈጥረዉን ዝብርቅርቅ ለማስወገድና ም በተደራጀ ወንጀል የሚገኝ ገንዘብን አንድ ነገር ማድረግ ይኖርብናል። በማሊና ጊኒ ባሳዉ የተፈጠረዉን ትርምስ መዉሰድ ይቻላል።»

Drogenkonsum Dänemark
ዴንማርክ፤ የአደንዛዥ እፅ ተጠቃሚምስል Laerke Sodring Nielsen

ይህን መሰሉን ሕገ ወጥ የአደንዛዥ እፅ ዝዉዉርና አጠቃቀም ለመግታትም አፍሪቃ እና የተመድ በጋራ ጥረት ጀምረዋል። ዶክተር ማይየጉን በኬንያ ዋና ከተማ በቅርቡ በአንድ የገበያ አዳራሽ ዉስጥ የተፈጸመዉ ጥቃት የተደራጀ ወንጀል አፍሪቃን መረጋጋት ስጋት ላይ የሚጥል ታላቅ ፈተና የመሆኑ ማረጋገጫ ነዉ። ናይጀሪያዊዉ ማይየጉን የአፍሪቃ ኅብረት የአደገኛ እፅ ቁጥጥር እና ወንጀል መከላከል የተግባር እቅድ አስፈጻሚ የሆነዉ የኅብረቱ ኮሚሽን አባል ናቸዉ። ዶክተሩ ወንጀለኞች የአፍሪቃ ሃገራትን ክፍት ድንበሮችና ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰዉን ድህነት ይጠቀማሉ ባይ ናቸዉ። ወደአዉሮጳና ምዕራብ ሃገራት የሚጓዘዉ አደንዛዥ እፅ መሸጋገሪያም አፍሪቃ መሆኗን ያመለክታሉ።

«ከደቡብ አሜሪካ የሚመጣዉ ኮኬይን በአብዛኛዉ በምዕራብ አፍሪቃና ጥቂቱ ደግሞ በደቡብ አፍሪቃ በኩል ነዉ የሚያልፈዉ። ከአፍጋኒስታን የሚመጣዉን ሄሮይን ብንወስድ ደግሞ የሚያልፈዉ በምስራቅ አፍሪቃ በኩል ነዉ። አፍሪቃ ዉስጥ ከግጭት ወጥተዉ ያልተጠናከሩ በርካት ሃገራት መሸጋገሪያ እየሆኑ ነዉ። አንዳንድ አደንዛዥ እፆችም እዚያዉ ይቀራሉ። ስለዚህ በአህጉሪቱ የሚታየዉ የአደንዛዥ እፅ አጠቃቀምም በእነዚህ በሚቀሩት ላይ የሚመሠረት ነዉ።»

Koka Anbau in Bolivien Archiv 2006
የቦሊቪያ የኮካ ተክልምስል Mauro Mariani/Europeaid/Delegation Bolivia

በጉባኤዉ የተገኙት የተመድ የአደንዛዥ እፅ ክትትል ቢሮ ኃላፊ ሻብ ሳላህ ለተሰብሳቢዎቹ ያመለከቱት ጽሕፈት ቤታቸዉ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ሕገወጥ የአደንዛዥ ዝዉዉርና አጠቃቀምን በመዋጋት ሂደት ያካበተዉን ልምድ አፍሪቃ ዉስጥም ለማዋል እንደሚሻ ነዉ።

«የተመድ የአደንዛዥ እፅ ቁጥጥር ጽህፈት ቤት፤ አፍሪቃ ለልማት ማለትም በመላ አህጉሪቱ የትምህርት፣ የኤኮኖሚ እድገት እና የጤና ችግሮች ዋነኛ እንቅፋት የሆነባትን ችግር ይገነዘባል። አፍሪቃ ዉስጥ የአደንዛዥ እፅ መጠቀም በተለይም በወጣቶች ዘንድ በፍጥነት እየተስፋፋ በመሄድ ላይ ነዉ። የተመድ የአደንዛዥ እፅ ቁጥጥር ጽህፈት ቤት አባል ሃገራት የአደንዛዥ አጠቃቀም፤ ዝዉዉር፣ ሙስናና አሸባሪነትን የመታገል ጥረትና አቅማቸዉን እንዲያጠናክሩ የቴክኒክ ድጋፍ ያደርጋል።»

ከመላዉ አፍሪቃ የተለያዩ መንግስታትን ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች በመወከል በጉባኤዉ የተገኙ ባለሙያዎች፤ ወደአህጉሪቱ የሚዘልቀዉን የአደንዛዥ እፅ አቅርቦት ለመቀነስ የታየዉ ተነሳሽነት ተስፋ እዳሳደረባቸዉ እየገለጹ ነዉ።

ኮሎምበስ ማቩንጋ
ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ