ኢስታንቡል-በጥቃቱ የተገደሉት በሙሉ ጀርመናዊ ናቸዉ
ረቡዕ፣ ጥር 4 2008
የቱርክ ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት በሐገር ጎብኚዎች የሚዘወተረዉን የኢስታንቡል ታሪካዊ ሥፍራ ያሸበረዉ አጥፍቶ ጠፊ እራሱን የኢራቅና የሶሪያ እስላማዊ መንግሥት (ISIS) ብሎ የሚጠራዉ አሸባሪ ቡድን ባልደረበ ነዉ።አጥፍቶ ጠፊዉ ሶሪያ ዉስጥ ለረጅም ጊዜ የኖረና እና በቅርቡ ወደ ቱርክ የተሻገረ የ27 ዓመት ሳዑዲ አረቢያዊ ወጣት ነዉ።ጥቃቱ ሆን ብሎ የጀርመን ዜጎችን ለመግደል ያለመ-ሥለመሆን አለመሆኑ ግን የሁለቱም ሐገራት ባለሥልጣናት ያሉት ነገር የለም።ይሁንና የጀርመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር ቱርክ የሚኖሩም ሆነ ለጉብኝ የተጓዙ እና የሚጓዙ ጀርመናዊያን ከተመሳሳይ ጥቃት እንዲጠነቀቁ መክረዋል።
«በጀርመን ዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር የፌደራዊዉ የአስቸኳይ ጉዳይ ቡድን አደጋዉን እንደተሰማ ወዲያዉ ጉዳዩን መከታተል ጀምሯል።ቡድኑ የጥቃቱን ሠለቦች ለመርዳትና የአደጋዉን ትክክለኛ ዓለማ ለማወቅ ኢስታንቡል ከሚገኘዉ የጀርመን ቆስላ እና አንካራ ካለዉ ኤምባሲያችን ጋር በቅርብ እየሠራ ነዉ።ከቱርክ ባለሥልጣናት ጋርም የቅርብ ግንኙነት አለን።ቱርክ በተለይም ኢስታንቡል የምትገኙ ጀርመናዉያን በሙሉ የዉጪ ጉዳይ ሚንስቴርን የጉዞና የደሕንነት መመሪያዎች በትትክል እንድትከታተሉ እጠይቃለሁ።መመሪያዎቹ በዉጪ ጉዳይ ሚንስቴር አምደ-መረቦች ይገኛሉ፤ በየጊዜዉ ይሻሻላሉም።»
ዛሬ ኢስታንቡል የገቡት የጀርመን የሐገር ግዛት ሚንስትር ቶማስ ደ ሚዚዘየር በበኩላቸዉ ጥቃቱ የተጣለበትን አካባቢ ጎብኝተዋል።ጀርመናዊያን ጉዳተኞችን አነጋግረዋልም።ደ ሚዚየር እንዳሉት የትናንቱ ጥቃት ጀርመናዉያንኑን ነጥሎ ለመጉዳት ያለመ ለመሆኑ ምንም ማረጋገጪያ የለም። የቱርክ ፀጥታ አስከባሪዎች ከትናንቱ አጥፍቶ ጠፊ ጋር በአባሪ ተባባሪነት የጠረጠሩትን አንድ ሰዉ ይዘዋል።ሌሎች ሰዎስት የሩሲያ ዜጎችም በአሸባሪነት ተጠርጥረዉ መያዛቸዉን ቱርክ አስታዉቃለች።