1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢሶህዴፓ የመጀመርያ ጉባዔ

ሰኞ፣ መጋቢት 23 2011

የኢትዮጵያ ሶማሌ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ/ኢሶህዴፓ በፓርቲውና በክልሉ ከጀመረው ለውጥ በኃላ የመጀመርያ ጉባዔ ዛሬ ጀመረ። ለሦስት ቀናት የሚቆየው የፓርቲው ጉባዔ በፓርቲው ያለፈ የስራ አፈፃፀም ላይ ከመወያየትና ቀጣይ አቅጣጫ ከማስቀመጥ በተጨማሪ ለቀጣይ የሚያገለግሉ የማዕከላዊ ኮሚቴዎችንና ስራ አስፈፀሚዎችን ይመርጣል ተብሎ ይጠበቃል ።

https://p.dw.com/p/3G2xk
Äthiopien Somali-Region-Partei & gegenerische Parteien in Jigjiga
ምስል DW/M. Teklu

ፓርቲዉ ማዕከላዊ ኮሚቴዎችንና ስራ አስፈፀሚዎችን ይመርጣል

የቀደሙ አመራሮቹ በክልሉ ህዝብ ላይ ፈፀሙት በተባለው የተለያየ ዓይነት ችግር ከፊሎቹን በህግ እንዲጠየቁ ከፊሎችንም ከሀላፊነት እንዲነሱ ያደረገው የኢትዮጵያ ሶማሌ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ/ኢሶህዴፓ በፓርቲውና በክልሉ ከጀመረው ለውጥ በኃላ የመጀመርያ የሆነውን ድርጅታዊ ጉባዔ ዛሬ በጅግጅጋ ከተማ ማካሄድ ጀምሯል ። የኢትዮጵያ ሶማሌ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ/ኢሶህዴፓ ሊቀመንበር የሆኑት አቶ አህመድ ሽዴ ዛሬ በተጀመረው 10ኛ ድርጅታዊ ጉባዔ ላይ እንደተገለፁት ባለፉት ወራት በክልሉ ሰላምንና የህግ የበላነትን ለማረጋገጥ እና በፓርቲው የተፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት በርካታ ጥረቶች ተደርገዋል በተለይም በህዝቡ ላይ አስከፊ ጉዳት ያደረሱ አካለት በህግ እንዲጠየቁ መደረጉን ተናግረዋል ።“ ፓርቲው ላለፉት አመታት የመጣበትን መንገድ በመገምገም የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች የፓረቲውን ውስጠ ደምብ እና አሰራር በተጣረሰ መልኩ የሰሩት ስራ በፓርቲው ላይ ከፍተኛ የፖለቲካ ክስረት እንዲያጋጥም አድርጓል ።ለዘህም መፍትሄ ለመስጠት በየደረጃው በተካሄደ ግምገማ ለውጦች ተደርገዋል ለዚህ ዋንኘ ማሳያ በፓርቲው ከፍተና አመራር ላይ የተደረገ ለውጥ ነው “ ነባሩ አመራር በክልሉ የፈጠረው ችግር በህዝቡ ዘንድ ከፍተኛ መጠራጠርና አመኔታ ማሳጣቱን የገለፁት አቶ አህመድ ጉባዔተኛው በፓርቲው የተጀመረውን ለውጥ እና በህዝብ ዘንድ የተሸረሸረውን አመኔታ መለወጥ የሚችሉ የፓርቲ አመራሮችን በመምረጥ ሀላፊነቱን እንዲወጣም ጠይቀዋል ።“ተስፋ አደርጋለሁ ጉባዔተኞች የፓርቲው ውስጠ ደንብ በሰጣቸው ነፃነት ተጠቅመው ጠንካራና ለህዝብ ጥያቄዎች ፖለቲካዊ ምላሽ መስጠት የሚችል ፓርቲ የመገንባት ፍላጎት እውን እንዲሆን ፣ ከወገንተኝነትና ከሙስና የጸዱ አመራሮችን በመምረጥ የበኩላቸውን እንደሚወጡ እምነቴ ነው”  በፓርቲው  10ኛ ድርጅታዊ ጉባዔ ላይ የተገኙት የኢህአዴግ ፅቤት ሀላፊ አቶ ብናልፍ አንዷለም በበኩላቸው ግንባሩ በአጋርነት ለአመታት አብረውት ሲሰሩ የቆዩ ድርጅቶችን ያካተተ ህብረ ብሄራዊ ድርጅት ለመፍጠር የጀመረው እንቅስቃሴ በመፋጠን ላይ ነው ብለዋል ።ይህም ሁሉም ዜጎች በሀገራቸው እኩል የሚሳተፉበት ዕድል ይፈጥራል ብለዋል ።አቶ ብናልፍ ቀደም ሲል በሶማሌ ክልል በነበሩ አመራሮች በህዝብ ላይ ያደረሱትን ጉዳት በወል በተገነዘቡ የኢሶህዴፓ የለውጥ ሀይሎች የድርጅቱን ችግሮች ለማረም ያደረጉት ጥረት በርካታ ፍሬዎች ማፍራቱንና ለክልሉ ህዝብ አዲስ ምዕራፍ መክፈቱን ተናግረዋል ።በጉባዔው ላይ የተገኙ የኢህአዴግ እህት ድርጅቶችና የአጋር ፓርቲ ተወካዮች ፓርቲው ለጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ የበኩላቸውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል ።ለሶስት ቀናት የሚቆየው የፓርቲው ጉባዔ በፓርቲው ያለፈ የስራ አፈፃፀም ላይ ከመወያየትና ቀጣይ አቅጣቻ ከማስቀመጥ በተጨማሪ ለቀጣይ የሚያገለግሉ የማዕከላዊ ኮሚቴዎችንና ስራ አስፈፀሚዎችን ይመርጣል ተብሎ ይጠበቃል።

Äthiopien Somali-Region-Partei & gegenerische Parteien in Jigjiga
ምስል DW/M. Teklu

መሳይ ተክሉ 


አዜብ ታደሰ 
ሸዋዬ ለገሠ