1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመሠረቱት ክስ

ማክሰኞ፣ ጥር 6 2006

ከ7 ሳምንት በፊት ነበር ሶስት ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የቤልጄምን ጦር ኃይል በፍርድ ቤት የከሰሱት። ይህም እኢአ በ2011 መጋቢት ወር ከሊቢያ ትሪፖሊ 72 ሰዎችን አሳፍራ ወደ ላምፔዱዛ ስትጓዝ የነበረች አንዲት ጀልባ የማዕበል አደጋ ከደረሰባት በኋላ በአካባቢዉ ከነበሩ ኃይሎች ርዳታ ባለማግኘታቸዉ ነው።

https://p.dw.com/p/1Apsa
EU-Grenzüberwachungssystem Eurosur
ምስል picture-alliance/dpa

ወቅቱ የሊቢያ አብዮት ነበር። ሰዎች ከቤታቸው መውጣት የሚፈሩበት እና በየጎዳናው ቀን እና ሌሊት የጥይት ድምፅ የሚሰማበት። በዚህ ወቅትም በርካታ ሊቢያውያን እና በሀገሪቱ ይኖሩ የነበሩ የውጭ ሀገር ዜጎች ተሰደዋል። አቶ አቡ ከሌሎች እሳቸው እንደሚሉት 47 ኢትዮጵያውያን ፣ በርካታ ኤርትራዊያን እና ሌሎች አፍሪቃውያን ጋር ገንዘብ ከፍለው በጀልባ የሸሹት ወደ ላምፔዱዛ ኢጣሊያ ነበር። ይሁንና የፈለጉበት ሳይደርሱ ባህር ላይ የጠበቃቸው የ15 ቀን ሰቆቃ ነበር። ጉዞዋቸው ለምን እንደስተጓጓለ እና ጉዳያቸው ለምን በፍርድ ቤት እንዲታይ እንደወሰኑ በዚህ መርከብ ተሳፍረው የተረፉ እና ከከሳሶቹ አንዱ የሆኑት ኢትዮጵያዊ አቶ አቡ ገጠመኛቸውን መለስ ብለው ያስታውሱናል።

Libyen Hafen von Tripolis
የትሪፖሊ ወደብምስል picture-alliance/dpa

አቶ አቡ እንደሚሉት የገጠማቸው ማዕበል አደገኛ ስለነበር በስልክ የርዳታ ጥሪ ካደረጉ በኋላ አንድ ሄሊኮብተር መጥታ ውሃ እና ብስኩት ከሰጠቻቸው በኋላ ሄሊኮፕተሯ እንደሚመለስ ምልዕክት ሰጥቶዋቸው ተመልሳለች። ይሁንና ውሃ የአቀበላቻቸውም ሄሊኮፕተር ትሁን በጎናቸው የሚያልፉ መርከቦች ከዛን ሰዓት በኋላ አልደረሱላቸውም። ከዚህም በተጨማሪ የጀልባቸው ነጂ በመደናገጥ አቅጣጫ መምሪያውን ውሃ ውስጥ በመጣሉ እና አቶ አቡ እንደሚሉት ጀልባዋ ነዳጅ በመጨረሷ ቀጥለው ለመንዳት አልቻሉም። በወቅቱ ያላቸው ብቸኛ አማራጭ፤ ባሉበት መቆየት ብቻ ነበር። የዛኑ ሌሊትም 3 ስደተኞች በማዕበሉ ተወስደው ባህር ሰምጠው ቀሩ። ይህ ብቻ አይደለም፤ 63ቱ ሲሞቱ በህይወት የተረፉት 9ኙ ብቻ ናቸው።

Italien Küstenwache
የጣሊያን የባህር ኃይልምስል Getty Images

አቶ አቡ እና ሌሎቹ 2 ከሳሾች ጉዳይን የሚከታተሉት ለስደተኞች የሚሟገተዉ አጀንሲያ ሃበሻ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አባ ሙሴ ዘርዓይ በቤልጄም ጦር ኃይል ላይ የቀረበውን ክስ አብራርተውልናል።

አባ ሙሴ እንዳሉትም በህይወት የተረፉት ስደተኞች ካሳ እንዲያገኙ ከመጠየቅ ባሻገር፤ ዳግም እንደዚህ ዓይነት ስህተት እንዳይፈጠር እና የሰብዓዊ መብቶች እንዳይጣሱ እንዲሁም እንደዚህ ዓይነት አጋጣሚዎች ሲከሰቱ ኃላፊነት የሚወስድ ተጠያቂ አካል በአውሮፓ ህብረት ደረጃ ተደንግጎ እንዲወጣ እንደሚጥሩ ገልፀውልናል።

ልደት አበበ

ነጋሽ መሀመድ