1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኤች አይ ቪ ኤድስ እና ወጣቱ

ዓርብ፣ ኅዳር 22 2004

ዓለም አቀፍ የኤድስ ቀን ሐሙስ ሕዳር 22፣ 2011 ዓ.ም. በመላው ዓለም ታስቦ ውሏል። ይህንኑ ልዩ ቀን አስመልክቶ ሁለት እንግዶችን ከአዲስ አበባ እና ከካናዳ አነጋግረናል። የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ስለ ኤች አይ ቪ ኤድስ ምን ያህል ንቃት አላቸው? አንዲት ወጣት የዩነቨርሲቲ ተማሪ የምትለን ይኖራታል።

https://p.dw.com/p/RztN

በውጭው ዓለም በስደት የሚገኘው ኢትዮጵያዊስ ይህንኑ አሳሳቢ ቫይረስ ምን ያህል እየታገለው ነው?የቶሮንቶው ወጣት ከካናዳ ልምዱን ያካፍለናል።

---

ኤች አይ ቪ ኤድስ ከሁለት አስርት ዓመታት ላላነሰ ጊዜያት ዓለማችንን ሲያስጨንቅና ሲያስጠብብ ዛሬ ላይ ደርሷል። ብዙ ተብሎለታል፣ በተደጋጋሚ ተመክሮበታል፣ ለዓመታትም ተዘክሮበታል። እንዲያም ሆኖ ግን በዓለማችን ዛሬም ከኤድስ አማጪው ቫይረስ ጋር የሚኖሩ ሰዎች ቁጥር 34 ሚሊዮንን ቢሻገር እንጂ አያንስም ሲል የተባበሩት መንግስታት የኤድስ ዘገባ ትናንት ይፋ አድርጓል። ያም በመሆኑ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት መላው ዓለም በያለበት በርብርብ ላይ ነው።

ወጣት ትዕግስት ደጉ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ክፍል የአራተኛ ዓመት ተማሪ ናት። በምትማርበት ዩኒቨርሲቲ ኤች አይ ቪ ኤድስን አስመልክቶ እየተደረገ ያለውን እንቅስቃሴ በዚህ መልኩ ትገልፃለች። ድምፅ፥ ትዕግስት ደጉ

በእርግጥም መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የኤች አይ ቪ ኤድስ ስርጭትን በመቀነሱ ረገድ ቀደም ሲል አመርቂ ውጤት ያስመዘገቡ አንዳንድ ሀገራት ውስጥ ስርጭቱ እንዳዲስ እያሻቀበ ነው። በተለይ ኡጋንዳ ቫይረሱ እንዳዲስ ያስጨንቃት ጀምሯል። ለዚያ ደግሞ በህብረተሰቡ ዘንድ ለቫይረሱ የሚሰጠው ትኩረት እየቀለለ መምጣቱ እንደ አቢይ ምክንያትነት ተጠቅሷል። በጥቅሉ ሲታይ ግን ኤች አይ ቪ ቫይረስ እንደ ተተኳሽ ሮኬት የተያያዘውን መምዘግዘግ ካለፉት ቅርብ ዓመታት ወዲህ ረገብ ያደረገው ይመስላል።

ትናንት ይፋ የሆነው የተባበሩት መንግስታት የኤድስ ዘገባ እንዳተተው ከሆነ፤ በበርካታ ሀገራት የታየው ውጤታማ የማስተማርና የማንቃት ዘመቻ እንዲሁም የመድሀኒት አቅርቦት መስፋፋቱ የስርጭቱን ፈጣን ግስጋሴ በመጠኑ አርግቦታል። ጄኔቫ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የኤድስ ፕሮግራም ውስጥ የመረጃና ንድፍ ክፍል ሃላፊው ዶክተር በርንሐርድ ሽዋርትሌንደርም ይህንኑ ይጋራሉ ። ድምፅ፥ በርንሐርድ ሽዋርትሌንደር

«በአሁኑ ወቅት በርካታ ሰዎች፤ ማለትም ዝቅተኛ እና መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት ውስጥ የሚኖሩ ከ6 ሚሊዮን በላይ የሚጠጉ ሰዎች መድሀኒት ተጠቃሚዎች ናቸው። እናም የመድሀኒት አቅርቦቱ የሰዎችን ህይወት ከመታደጉም ባሻገር ሰዎችን ማከሙ በራሱ ከአንዱ ወደ አንዱ የሚተላለፈውን የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት አስተዋፅዖ ያደርጋል» ድምፅ፥ ዮሐንስ አያሌው በዓለማችን የኤች አይ ቪ ኤድስ ስርጭትን ለመግታት መላ ህብረተሰቡን የማንቃቱ ሂደት በይበልጥ መጠናከር የሚገባውን ያህል፤ ወጣቱ ላይ የበለጠ ትኩረት ማድረግ ያስፈልጋል። ወጣቱ ለቫይረሱ ስርጭት የያዘው ድርሻ እንዲህ በቀላሉ የሚገመት አይደለምና።

የተባበሩት መንግስታት ዘገባ እንደሚያሳየው ከሆነ እድሜያቸው ከ15 እስከ 24 ዓመት የሚጠጉ ከሰሐራ በታች የሚኖሩ ወጣቶች ዘንድ የቫይረሱ ስርጭት ከመቀነስ ይልቅ በየጊዜው እየጨመረ ይገኛል። ኢትዮጵያም ከሰሀራ በታች የምትገኝ ሀገር የመሆኗን ያህል ወጣቱ ለቅፅበትም ቢሆን ከኤድስ አማጪው ቫይረስ ራሱን ከመጠበቅ መዘናጋት የለበትም።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ