1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እርዳታ ለጋሾችን ያወከዉ የዳርፉር ችግር

ዓርብ፣ ሰኔ 10 1997

በደቡብ ሱዳን የተሰማሩ የግብረ ሰናይ ድርጅቶች የዳርፉርን የጦር ወንጀለኞች ክስ ጉዳይ ከያዙት ዓለም ዓቀፍ የወንጀል መርማሪዎች ጋር በዛሬዉ ዕለት ስብሰባ ያደርጋሉ።

https://p.dw.com/p/E0js

እነዚህ በዓለም በግንባር ቀደምትነት የታወቁት የግብረ ሰናይ ቡድኖች ከወንጀል መርማሪዎቹ ጋር ሲገናኙ ችግር ባለባት በዳርፉር አካባቢ በእርዳታ ሰራተኞችና በኗሪዎቹ ላይ እየተባባሰ በመጣዉ የደህንነት ስጋት ዙሪያ በስፋት ይነጋገራሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የዉይይቱ ነጥብ የተመረጠዉ መቀመጫዉን ኒዉ ዮርክ ባደረገዉ ማክአርተር ፋዉንዴሽን የበላይ ጆን ዲ. እና ካተሪን ቲ, ሲሆን በለጋሽ ድርጅቶቹና በዓለም ዓቀፍ የወንጀል ችሎት አቃቤ ህግ ሉዊሶርኖ ዖካምፓ መካከል የትብብር አጋጣሚዎችን ለማመቻቸት ታስቦ ነዉ።
ሆኖም ግን እርምጃዉ የግብረ ሰናዩ ቡድኖቹ በዚያ በግጭት ወረዳ ለረጅም ጊዜ በገለልተኝነት ዉጤት ባለዉ መልኩ ሲሰሩ የመቆየታቸዉን ነገር ጥያቄ ላይ የሚጥል ይሆናል የሚል ስጋት አስነስቷል።
የዓለም ዓቀፍ የስደተኞች ጉዳይ ፕሬዝደንት ኬኔዝ ባኮን እንደሚሉት ምንም ቢሆን የግብረ ሰናይ ሰራተኞችን ደህንነት ፈተና ዉስጥ የሚጥልና ስራቸዉን ለመስራት እንቅፋት የሚጋርጥ ችግር ለማምጣት ማንም አይፈልግም።
እንደ እሳቸዉ አባባል የእርዳታ ሰጪዎቹን ቡድን ማንም በሚገነዘበዉ መልኩ የዳርፉርን የደህንነትና የሰላም ሁኔታን የሚያደፈርሰዉ ማንኛዉም ጉዳይ ያሳስባቸዋል።
አሁን ባለዉ ሁኔታም የዓለም ዓቀፉ የወንጀል ችሎት የሚያካሂደዉ የምርመራ ተግባር ሁኔታዎችን እንዳያባብስ ቢሰጉም በሌላ በኩል ደግሞ የማይሆንበት አጋጣሚም ሊፈጠር ይችላል የሚል ተስፋ ይዘዋል።
በእሳቸዉ እምነትም ይህ ሁለቱ ወገኖች የሚያካሂዱት የዛሬዉ ስብሰባ በዳርፉር ለተከሰቱ ችግሮችና በተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ለሚደረገዉ ዉይይት የመጀመሪያ ይሆናል።
ዋና ፅህፈት ቤቱ ካሊፎርኒያ የሚገኘዉ ዓለም ዓቀፍ የህክምና ባለሙያዎች ቡድን ዋና ተጠሪ ናንሲ ዖሴይ በፃፉት ማብራሪያ እንደገለፁት በስፍራዉ ስለተፈፀሙ የጦር ወንጀሎች ለምርመራ የሚሆን መረጃ መሰብሰብ የእነሱ ተግባር አይደለም።
በእሳቸዉ እምነትም የሰራተኞቻቸዉና የአገልግሎታቸዉ ተጠቃሚ የሆነዉ የተፈናቀለዉ የደቡብ ሱዳን ህዝብ የደህንነቱ ሁኔታ ከሁሉም በላይ በአካባቢዉ ባለዉ ተቀባይነት ላይ ብቻ የተመሰረተ ነዉ።
በስብሰባዉ የሚሳተፉትም በአካባቢዉ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙ ሰራተኞቻቸዉና የእነሱን እርዳታ የሚፈልገዉ ህዝብ የሚገኙበትን ሁኔታና የሚያሰጓቸዉን ጉዳዮች ከሌሎች ወገኖች ጋር ለመወያየት ነዉ።
በዳርፉር በየወሩ ይቀሰቀሱ በነበሩ ግጭቶች ሳቢያ ከ2ሚሊዮን በላይ ሰዎች ከቤት ንብረታቸዉ ተፈናቅለዋል በሺዎች የሚቆጠሩም ህይወታቸዉ አልፏል።
የዓለም ዓቀፉ የወንጀል ችሎት በሰዉ ዘር ማጥፋት፤ በጦር ወንጀለኝነትና በጅምላ በሚፈፀም የሰብዓዊ መብት ረገጣ ተግባር የተከሰሱ ሰዎችን የሚዳኝበት የተዋጣ ያሰራር ስልት በዳርፉር ይፈተናል ተብሎ ይጠበቃል።
ባለፈዉ ዓመት የተባበሩት መንግስታት የፀጥታዉ ምክር ቤት በስፍራዉ የተፈፀሙ ወንጀሎችን እንዲያጣራ የራሱን መርማሪ ኮሚሽን ልኮ ነበር።
ዋና ፀኃፊዉ ኮፊ አናንም የሰየሙት ኮሚሽኑ አጣርቶ ያቀረበላቸዉን የ51 ተጠርጣሪዎች ስም ለዓለም ዓቀፍ የወንጀል ችሎቱ ሰጥተዋል።
ሱዳንም በበኩሏ ዜጎቿ ከአገራቸዉ ዉጪ እንዲዳኙም ሆነ በወንጀለኝነት ተጠርጥረዉ እንዲከሰሱ አሳልፋ ለመስጠት ፈቃደኛ እንደማትሆን ተናግራለች።
ከሁለት ሳምንት በፊት ደግሞ የተሳሳተ መረጃ ነዉ ያወጡት በማለት ሁለት የድንበር የለሽ የህክምና ቡድን ሰራተኞችን ወደ ወህኒ አዉርዳለች።
እነዚህን የድንበር የለሽ የህክምና ቡድን የሰራተኞች ለክስ ያበቃቸዉ በዳርፉር የሚፈፀመዉ አስገድዶ መድፈርና ወሲባዊ ጥቃት ያስከተለዉ መዘዝ በሚል ያሳተሙት የጥናት ዘገባቸዉ ነዉ።
ከዚህ በመነሳት የዛሬዉ ስብሰባ አዘጋጅ የሆነዉ ማክአርተር ፋዉንዴሽን ሃላፊዎችም የጉዳዩን አሳሳቢነት በመረዳት ተሳታፊዎቹ በምስጢር እንዲይዙት ጠይቋል።
በስብሰባዉም CARE USA, WORLD VISION, Oxfam America, የህፃናት አድን ድርጅት፤ የክርስቲያን በጎ አድራጎት፤ ዓለም ዓቀፍ ቀይ መስቀል፤ የካቶሊክ የእርዳታ ድርጅት፤ ዓለም ዓቀፍ ፈጣን የህይወት ታዳጊ ኮሚቴ፤ እና Concern USA ይሳተፋሉ።