1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

እስክንድር ነጋ ስለታሰሩ ወጣቶች ይናገራል

ሰኞ፣ መጋቢት 2 2011

"ለአዲስ አበባ ምን ይደረግ?" በሚል ትላንት በአዲስ አበባ በተካሔደ ውይይት የተሳተፉ ታዳሚያን የከተማዋን አስተዳደር በብርቱ ወቀሱ። የከተማዋ አስተዳደር "በእርግጥ የነዋሪዎቹን ጥቅም እያስከበረ ነው ወይ?" የሚል ጥያቄ ተነስቶበታል።

https://p.dw.com/p/3EopE
Äthiopien Diskussion Politk und das Schicksal der Haupstadt
ምስል DW/S. Muchie

እስክንድር ነጋ ስለታሰሩ ወጣቶች ይናገራል

ምክትል ከንቲባ ታከለ ዑማ የሚመሩት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር "የሌላ አካልን ጥቅም ለማስጠበቅ የቆመ ነው" ሲሉ በትላንትናው ህዝባዊ ስብሰባ ላይ የተሳተፉ አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል። የትላንትናውን ስብሰባ ካዘጋጁት ውስጥ አንዱ የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ አሁን ያለውን የከተማዋን አስተዳድር "እንደማይቀበለው" ለተሳታፊዎች ገልጿል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በከተማይቱ "ጥቅም ላይም የመደራደር ህጋዊም፣ ፖለቲካዊም ስብዕና የለውም" ሲል እስክንድር አቋሙን ለታዳሚያኑ በንባብ አሰምቷል፡፡ "አዲስ አበባ የተሰራችው በፍቅር፣ በአንድነት እና በወንድማማችነት ስሜት በመሆኑ ይህችን የጋራ ቤታችን የምንመኛት የአፍሪካ መዲና እንድትሆን ነው" ሲል ጋዜጠኛ እስክንድር ተናግሯል። 

"ስለ አዲስ አበባ ምን ይደረግ?" በሚል ትላንት መጋቢት 1 ቀን 2011 በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ የታደሙ ተሳታፊዎች "ከተማዋ ባለቤቶቿ ነዋሪዎቿ እንደሆኑ እና በነዋሪዎቿ የተመረጡ ወኪሎች ሊኖሯት እንደሚገባም" በመስማማት ሙሉ ውክልናቸውን ለውይይቱ አዘጋጆች ሰጥተዋል፡፡ ቁጥሩ በርከት ያለ የከተማዋ ነዋሪ በተሳተፈበት በዚህ ውይይት ላይ ስለ ህግ፣ ፍትህ እና ሰብአዊ መብት እንዲሁም ስለ ምርጫ ነዋሪው የነቃ ተሳትፎ እና ክትትል እንዲያደርግ ጥሪ ቀርቧል፡፡

የውይይቱ አዘጋጆች ህዝባዊ ስብሰባውን በሰፊ አዳራሽ ለማድረግ ከከተማ አስተዳደሩ መከልከሉን ገልጸዋል። በቀጣይ መሰል የውይይት መርሃ ግብር በመስቀል አደባባይ እንደሚያደርጉም አሳውቀዋል። 

በትላንቱ ህዝባዊ ስብሰባ ላይ ተሳታፊ የነበሩ ሰዎች ከውይይቱ ማብቃት በኋላ መታሰራቸው ተሰምቷል። ስለ ወጣቶቹ እስር ከህዝባዊ ስብሰባው አዘጋጆች አንዱ የሆነውን እስክንድር ነጋን DW አነጋግሮት ነበር።

የእስክንድርን ቃለ ምልልስ እና የትላንቱን ስብሰባ ዝርዝር ለማድመጥ ከታች የተያያዙትን የድምጽ ማዕቀፎች ይጫኑ።  

ሰለሞን ሙጬ

ተስፋለም ወልደየስ

እሸቴ በቀለ 

 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ