1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኦባማ ሄሮሺማን ጉብኙ

ዓርብ፣ ግንቦት 19 2008

ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የጃፓንዋን ሄሮሽማ ከተማ ዛሬ ጎበኙ። በዚህም ባራክ ኦባማ ሄሮሽማን የጎበኙ የመጀመርያዉ በስልጣን ላይ የሚገኙ የዬኤስ አሜሪካ ፕሬዚዳንት ያደርጋቸዋል። የ

https://p.dw.com/p/1IvzG
Japan Hiroschima Obama Gedenkstätte Überlebende Atombombenabwurf
ምስል Reuters/C. Barria

ጃፓንዋ ሄሮሽማ ከተማ በጎርጎረሳዉያኑ ነሐሴ 6, 1945 ዓ,ም ከዩኤስ አሜሪካ በተወረወረ የአዉቶሚክ ቦንብ ከጥቅም ዉጭ ሆና በአመድ ተዉጣ እንደነበር ይታወቃል። ኦባማ ዛሬ ሄሮሺማን ሲጎበኙ «የሠላም ፓርክ » በተሰኘዉ ቦታ ላይ በኒኩልየር ቦንቡ ሕይወታቸዉን ላጡ የመታሰብያ አበባ ጉንጉን አኑረዋል። ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ባደረጉት ንግግር ለወደፊቱ ይህንን አይነት ሐዘንና ጥፋት ለማስቀረት እንዲህ አይነቱን ታሪክ የማየትና የመጠየቅ ኃላፊነት አለብን፤ ዓለምን ከኑኩልየር ነጻ ማድረግ አለብን ብለዋል።


«ሰዉን የተረገመ ተግባር እንዳይፈጽም ማገድ አይቻል ይሆናል። መንግሥታትና የምንመሰርተዉ ኅብረት ራሳቸዉን መከላከል መቻል አለባቸዉ። በተለይ እንደኔ ሃገር አይነቶቹ የኒኩልየር ቦንብ ያከማቹ ሃገራት ከፍራቻ የትባህል ወጥተን ኒኩልየር የሌለባት ዓለም ለመመስረት ድፍረቱ ሊኖረን ይገባል።»

Japan Hiroschima Obama Kranzniederlegung Gedenkstätte
ምስል picture-alliance/AP Photo/S. Kajiyama


በሄሮሽማዉ ጥቃት ወደ 140 ሺህ ሰዎች በፍንዳታዉና ፍንዳታዉን ተከትሎ በመጣዉ የአቶም ጨረር ተገድለዋል። በሄሮሽማ ላይ የተጣለዉ አዉቶሚክ ቦንብ በዓለማችን የመጀመርያዉ የአቶም መሳርያ ጥቃት መሆኑም ተዘግቦአል ። እንዲያም ሆኖ ፕሬዚዳንቱ በጉብኝታቸዉ ሃገራቸዉ ሄሮሽማ ላይ ስላደረሰችዉ የኒኩልየር ጥቃት ይቅርታን አልጠየቁም። የጃፓኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ሺንዞ አቤ ኦባማ ኤሮሽማን ሲጎበኙ አብረዋቸዉ ነበሩ። ይህ የኦባማ ታሪካዊዉ የሄሮሽማ ጉብኝት ጃፓን ላይ የተካሄደዉን 7ቱ በኢንዱስትሪ የበለፀጉ ሃገራት ጉባኤን ተከትሎ የመጣ ነዉ።

አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሐመድ