1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከስፖርቱ ዓለም

ሰኞ፣ ግንቦት 19 2005

ሰንበቱን በዓለምአቀፉ የስፖርት መድረክ ላይ ከሁሉም የላቀ ትኩረትን ስቦ ያለፈው ሁለት የጀርመን ክለቦች ለመጀመሪያ ጊዜ እርስበርስ የተገናኙበት የአውሮፓ እግር ኳስ ሻምፒዮና ሊጋ ፍጻሜ ግጥሚያ ነበር።

https://p.dw.com/p/18emh
ምስል Reuters

በለንደኑ ዌምብሌይ ስታዲዮም 90 ሺህ ተመልካች በተገኘበት ባለፈው ቅዳሜ ምሽት በተካሄደው ፍጻሜ ግጥሚያ ባየርን ሙንሺን ዶርትሙንድን 2-1 ሲረታ በጥቅሉ ለአምሥተኛ የአውሮፓ ዋንጫው በቅቷል። በየርን ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ ሁለቴ ለፍጻሜ ደርሶ በኢንተር ሚላንና በቼልሢይ ሲረታ በሶሥተኛ ሙከራው ባለፈው ቅዳሜ ምሽት ዕድል መልሳ አልከዳችውም። ይህ የቀሰቀሰው ስሜትም ከጨዋታው በኋላ ጎልቶ ነበር የታየው።

መለስ ብለን ካስተዋን በጨዋታው ሂደት በአጠቃላይና በተለይም በመጀመሪያው አጋማሽ በመሠረቱ ጠንከር ብሎ የታየው የዋንጫው ባለቤት ባየርን ሣይሆን ዶርትሙንድ ነበር። ሆኖም ቡድኑ በተደጋጋሚ ያገኛቸውን ጥሩ የጎል ዕድሎች ሊጠቀምባቸው ሳይችል ቀርቷል። ጨዋታው እስከ እረፍት ጎል አልባ ሆኖ ሲቆይ በሁለተኛው አጋማሽ ከመጠቃት ወደ ማጥቃት የተሻገረው ባየርን በ 60ኛዋ ደቂቃ ላይ ቀንቶት በክሮኤሺያው ብሄራዊ ቡድን ተጫዋች በማሪዮ ማንጁኪች አማካይነት የመጀመሪያዋን ጎል ያስቆጥራል። ኳሷን ከግራ ክንፍ ግሩም አድርጎ ያቀበለው የኔዘርላንዱ አርየን ሮበን ነበር።

UEFA Champions League Finale FC Bayern München gegen Borussia Dortmund Jubel Bayern Fans
ምስል picture-alliance/dpa

ይሁን እንጂ ዶርትሙንድ 1-0 ቢመራም ጨርሶ መረበሽ አልታየበትም። በተለይም በግሩም አጥቂው በሌቫንዶቭስኪ አማካይነት ከአንዴም ሁለቱ የባየርንን ተከላካዮች እጅጉን ይፈትናል። በዚሁ የማጥቃት ሂደቱም በ68ኛዋ ደቂቃ ላይ ፍጹም ቅጣት ምት ሲያገኝ የመሃል ሜዳ ተጫዋቹ ጉንዶጋን የባየርንን በረኛ ማኑዌል ኖየርን ወደ ግራ ልኮ በአስተማማኝ ሁኔታ በስተቀኝ ከጎሉ ውስጥ ይከታታል። ውጤቱ በዚህ መልክ መልሶ እኩል ለእኩል ሲሆን ሁለቱም ቡድኖች ብርቱ ትግል በተመላበት አጨዋወት ወሣኟን ሁለተኛ ጎል ለማስቆጠር መጣር ይቀጥላሉ።

የባየርን ሙንሺን ሁለተኛና ወርቃማ የድል ጎል የተቆጠረችው እንግዲህ መደበኛው ጊዜ አብቅቶ ጨዋታው ሊራዘም ነው የሚል ስሜት በተመልካች ዘንድ ባደረባት ወቅት በ 89ኛዋ ደቂቃ ላይ ነበር። አርየን ሮበን በዶርትሙንድ ጎል አጠገብ የተፈጠረውን የተከላካዮች መደናበር ተጠቅሞ ኳሷን በሰከነ ሁኔታ ከመረቡ ይከታታል። ግጥሚያው በዚሁ ሲለይለት ጎል አግቢው አሪየን ሮበን እንደገለጸው ውጤቱ በባየርን ተጫዋቾች ዘንድ የቀሰቀሰው የደስታ ስሜት እንዲህ የሚባል አልነበረም።

ግጥሚያው በጥቅል ሲታይ ላቅ ብለው ለታዩት ለዶርትሙንድ ተጫዋቾችና ለደጋፊዎቻቸው ውጤቱ መሪር ነበር። ዶርትሙንድን ምናልባትም ቀደም ሲል እንደተፈራው የሃያ ዓመት ወጣት የመሃል ሜዳ ተጫዋቹ የማሪዮ ገትሰ ታፋውን ታሞ መቅረት በመጨረሻ ሳይጎዳው አልቀረም። ወጣቱ ተጫዋች ግሩም አከፋፋይ ብቻ ሣይሆን አደገና ጎል አግቢ መሆኑም ይታወቃል። ከዚህ አንጻር መኖሩ ለዶርትሙንድ ምናልባትም በተለይ ቡድኑ ተጠናክሮ በታየበት በመጀመሪያው አጋማሽ ብዙ በበጀ ነበር።

Champions League Finale Borussia Dortmund - FC Bayern München
ምስል picture-alliance/dpa

ያም ሆነ ይህ ለጀርመን የእግር ኳስ አፍቃሪዎች በጥቅሉ ዋንጫዋ ማንም ያሸንፍ ማን ወደ ጀርመን የምትመጣ በመሆኗ ሰንበቱ የፌስታ ሆኖ ነው ያለፈው። ዓለምአቀፉና የጀርመን ፕሬስ ጨዋታውን በማድነቅ የጀርመን ቡንደስሊጋ በዓለም ላይ አንደኛ ሆኗል ወደ ማለቱ አዘንብለዋል። ይሁን እንጂ ስሜታዊነቱ ቀርቶ ጨዋታው በትክክል ከታየ በአንድ የሻምፒዮና ሊጋ ፍጻሜ ግጥሚያ የሚጠበቀው የቴክኒክና የጥበብ ጥራት የሚገባውን ያህል የሰመረበት ነበር ማለቱ በመጠኑም ቢሆን የሚያዳግት ነው።

እርግጥ የጀርመን ክለቦች የአጨዋወት ስልት የሆነው ፍጥነትና ትግል ግጥሚያውን ለአንድ አፍታ እንኳ አልተለየውም። መሃል ሜዳውን በመቆጣጠር ታክቲክ ከሁለቱም ወገን በታየው አጨዋወት ብዙ የኳስ መነጣጠቅ፤ ማበላሸትና የቅብብል መሰናከል እንዲሁም ጠለፋና ግጭቶች በብዛት ተከስተዋል። ኳስን በመቆጣጠር ቴክኒካዊና ታክቲካዊ ስክነት በሰፈነበት በአጭር ቅብብል ዘይቤ ስልታዊ የማጥቃት አጨዋወት ምናልባትም የቡድኖቹ ባህርይ ሊሆን ይችላል እምብዛም አልነበረም።

ቢሆንም በውድድሩ ግማሽ ፍጻሜ ሃያላኑን የስፓኝ ክለቦች ያሰናበቱት የጀርመን ክለቦች ለፍጻሜ መድረሳቸውና ባየርንም የዋንጫዋ ባለቤት መሆኑ የሚገባው ነው። ክለቦቹ ይህን የዘንድሮውን ጥንካሬያቸውን በመጨው የውድድር ወቅት ጠብቀው ይቀጥሉ ወይም አይቀጥሉ ግን በጊዜው የሚታይ ይሆናል። በነገራችን ላይ የባየርኑ የሻምፒዮና ሊጋ ድል የአሠልጣኙን የዩፕ ሃይንከስን ተፈላጊነትም ከፍ ሊያደርግ በቅቷል። ሬያል ማድሪድ ለተሰናባች አሰልጣኙ ለሆሴ ሞሪኞ ተተኪ የሚፈልግ ሲሆን ሃይንከስ ወኪሉ ትናንት እንዳስታወቀው ለዚሁ ዝግጁ ነው።

Italien Fußball Miroslav Klose von Lazio
ምስል Getty Images

በተቀረ በሌሎች የአውሮፓ ሊጋዎች በተካሄዱ ጠቃሚ ግጥሚያዎች በኢጣሊያ ላሢዮ የከተማ ተፎካካሪውን ኤ ኤስ ሮማን በስታዲዮ ኦሊምፒኮ 1-0 በመርታት ትናንት ለስድሥተኛ ጊዜ የኢጣሊያ ፌደሬሺን ዋንጫ አሸናፊ ሆኗል። የዋንጫው ድል ላሢዮን በመጪው የውድድር ወቅት ለአውሮፓ ሊግ ተሳትፎም የሚያበቃ ነው። በፖርቱጋል ዋንጫ ደግሞ ቪክቶሪያ ጊማሬሽ ከኋላ ተነስቶ ቤንፊካን 2-1 በመርታት ላልተጠበቀ ድል በቅቷል።

ለቤንፊካ ሽንፈቱ ከአውሮፓ ሊግ ፍጻሜና ከፖርቱጋል ሻምፒዮና ሌላ ሶሥተኛው ሲሆን ለሊዝበኑ ክለብ እጅጉን መሪር ነው። በስኮትላንድ ዋንጫ ደግሞ ሤልቲክ ግላስጎው ለ 36ኛ ጊዜ አሸናፊ ሲሆን በፍጹም ቅጣት ምት በለየለት የስዊድን ዋንጫ ፍጻሜም ጎተቦርግ ቀንቶታል። በተረፈ የአውሮፓው ሊጋዎች ውድድር በመጠናቀቅ ላይ ሳለ የስፓኙ ክለብ ባርሤሎና ራሱን በብራዚሉ ብሄራዊ ተጫዋች በኔይማር እንደሚያጠናክር ታውቋል። የ 21 ዓመቱ ኮከብ በዛሬው ዕለት ውል እንደሚፈርም ይጠበቃል።

የስፓኙ ፕሪሜራ ዲቪዚዮን በሌላ በኩል ከሌላው የላቲን አሜሪካ ኮከብ ከራዳሜል ፋልካኦ ሳይሰናበትም አይቀርም። አትሌቲኮ ማድሪድን በበርካታ ጎሎቹ ለሊጋ ሶሥተኝነትና ለብሄራዊ ዋንጫ ያበቃው የኮሉምቢያ ኮከብ ወደ ሞናኮ ሊሻገር መቻሉ እየተነገረ ነው። አትሌቲኮ ለዚህ ድንቅ ተጫዋች ተተኪ ማግኘቱ ቀላል የሚሆንለት አይመስልም።

Frankreich Sport Leichtathletik Diamond-League-Meeting in Paris David Rudisha aus Kenia
ምስል picture-alliance/dpa

ሰንበቱን ኒውዮርክ ላይ ተካሂዶ በነበረው የአትሌቲክስ ዳያመንድ ሊግ ውድድር በአጭር ርቀት በወንዶችና በሴቶች የአሜሪካና የጃሜይካ አትሌቶች አይለው ሲታዩ በመካከለኛ ርቀት ደግሞ የኢትዮጵያና የኬንያ ተወዳዳሪዎች ግሩም ውጤት አስመዝግበዋል። በወንዶች አንድ መቶ ሜትር አሜሪካዊው ታይሰን ጌይ ሲያሸንፍ በሁለት መቶ ሜትር የጃሜይካው ዎረን ዋይር ቀደምቱ ሆኗል። በአራት መቶ ሜትርና በአራት መቶ መሰናክል ድሉ የአሜሪካውያኑ የዮሹዋ ማንስና የማይክል ቲንስሊይ ነበር።

በስምንት መቶ ሜትር ኬንያዊው የዓለም ሻምፒዮን ዴቪድ ሩዲሻ ሲያሸንፍ በአምሥት ሺህ ሜትር ደግሞ ሃጎስ ገ/ሕይወት ቀዳሚ ሆኗል። በሴቶች አንድ መቶና ሁለት መቶ ሜትር ያሸነፉት የጀሜይካ አትሌቶች ናቸው። በሴቶች ሶሥት ሺህ ሜትር መሰናክል ኬንያዊቱ ሉዲያ ቼፕኩሩዊ ስታሸንፍ እቴነሽ ዲሮና ሶፊያ አሰፋ ሁለተኛና ሶሥተኛ በመሆን ሩጫውን ፈጽመዋል። በ 1,500 ሜትር ደግሞ ለስዊድን የምትወዳደረው የቀድሞ የኢትዮጵያ አትሌት አበባ አረጋዊ አንደኛ ወጥታለች።

ከዚሁ ሌላ በኦታዋ ማራቶን ትናንት የኢትዮጵያ አትሌቶች ድርብ ድል ተጎናጽፈዋል። በወንዶች ታሪኩ ጁፋር አሸናፊ ሲሆን ኬንያዊው ሉካ ሮቲች ሁለተኛ፤ እንዲሁም ሌላው የኢትዮጵያ ተወዳዳሪ ጋሻው መለሰ ሶሥተኛ በመሆን ሩጫውን ፈጽመዋል። አንድ የኢትዮጵያ አትሌት በኦታዋው ማራቶን ለድል ሲበቃ የትናንቱ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነበር። በሴቶች ያሸነፈችው ደግሞ የሺ ኢሣኢያስ ነበረች። በዚህ በአውሮፓ በታላቁ የማንቼስተር ሩጫም በአሥር ኪሎሜትር ውድድር ጥሩነሽ ዲባባ ትናንት አንደኛ ወጥታለች። በወንዶች የኡጋንዳው ሞሰስ ኪፕሢሮ አሸናፊ ሆኗል።

Giro d' Italia Astana-Kapitän Vincenzo Nibali
ምስል imago/Sirotti

ቪንቼንሶ ኒባሊ በትናንትናው ዕለት የዘንድሮው ጂሮ-ዲ-ኢታሊያ የቢስክሌት እሽቅድድም አሸናፊ ሆናል። ኒባሊ በ 2010 እና 2011 ሶስተኛ ሲወጣ የዘንድሮው የመጀሪያው የጂሮ አጠቃላይ ድሉ መሆኑ ነው። የኢጣሊያው ተወላጅ ባለፈው ዓመት በቱር-ዴ-ፍራንስ ሶሥተኛ መሆኑም ይታወሳል። ትናንት ብሬሺያ ላይ በተጠናቀቀው በ 21ኛውና በመጨረሻው ደረጃ እሽቅድድም ቀዳሚ የሆነው ደግሞ የብሪታኒያው ማርክ ካቨንዲሽ ነበር። በዓለም የመንገድ የቢስክሌት እሽቅድድም አጠቃላይ ነጥብ የስዊሱ ፋቢያን ካንቼላራ በአንደኝነት የሚመራ ሲሆን ቪንቼንሶ ኒባሊ ሁለተኛና የስሎቫኪያው ፔተር ሣጋን ሶሥተኛ ሆነው ይከተላሉ።

Formel 1 Monaco Sieger Nico Rosberg Podium
ምስል Reuters

በትናንትናው ዕለት ሞናኮ ላይ ተካሂዶ በነበረው የፎርሙላ-አንድ አውቶሞቢል እሽቅድድም ሁለት የጀርመን ተወዳዳሪዎች ግንባር ቀደም ለመሆን ችለዋል። ኒኮ ሮዝበርግ በእሽቅድድሙ አሸናፊ ሲሆን ሁለተኛ የወጣው ያለፉት ዓመታት የዓለም ሻምፒዮን ዜባስቲያን ፌትል ነው። የአውስትራሊያው ማርክ ዌበር ሶሥተኛ ሲወጣ የእንግሊዙ ሉዊስ ሃሚልተንም እሽቅድድሙን በአራተኝነት ፈጽሟል።

መሥፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ