1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከስፖርቱ ዓለም

ሰኞ፣ ነሐሴ 20 2005

እግር ኳስ፣ አትሌቲክስና የአውቶሞቢል እሽቅድድም በዚህ ዝግጅት ዋና ማተኮሪያዎቻችን ናቸው።

https://p.dw.com/p/19WEo
ምስል picture-alliance/dpa

ዘገባችን ባለፈው ሣምንት ሞስኮ ላይ በተጠናቀቀው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ 800 ሜትር ሩጫ ለኢትዮጵያ የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝቶ ከነበረው አትሌት ከመሐመድ አማን ጋር የተካሄደ ቃለ ምልልስንም ይጠቀልላል።

በቅድሚያ በእግር ኳስ ላይ እናተኩርና የአውሮፓ ቀደምት ሊጋዎች የ 2013/14 አዲስ የውድድር ወቅት ከጅምሩ አንዳንድ አስደናቂ ውጤቶች እየታዩበት ነው። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ከሁለተኛው ዲቪዚዮን የወጣው ካርዲፍ ሢቲይ ትናንት ማንቼስተር ሢቲይን ባልተጠበቀ ሁኔታ 3-2 በመርታት ለታሪካዊ ድል በቅቷል። ለካርዲፍ ከሶሥት ሁለቱን ጎሎች ፍሬይዘር ካምፕቤል ሲያቆጥር ድሉ ለመጤው ክለብ በከፍተኛ ግጥሚያ በሜዳው ከ 51 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘ ነበር።

Englisch Premier Fussball League LOGO
ምስል DW

በፕሬሚየር ሊጉ ሁለተኛ ግጥሚያዎች ከዚሁ ሌላ አርሰናል ፉልሃምን 3-1፤ ሊቨርፑል ኤስተን ቪላን 1-0፤ ስቶክ ሢቲይ ክሪስታል ፓላስን 2-1፤ ቶተንሃም ሆትስፐር ስዋንሲይ ሢቲይን 1-0 ሲረቱ ኒውካስልና ዌስትሃም ዩናይትድ፤ እንዲሁም ኤቨርተን ከአልቢዮን አቻ ለአቻ ተለያይተዋል። ቀደምቱ ክለቦች ማንቼስተር ዩናይትድና ቼልሢይ የሚጋጠሙት ዛረ ማምሻው ላይ ነው። ከፕሬሚየር ሊጉ ሁለት ግጥሚያዎች በኋላ ቼልሢይ፣ ሊቨርፑልና ቶተንሃም በስድሥት ነጥቦች የሚመሩ ሲሆን ዌስት ሃም ዩናይትድና ሳውዝሃምፕተን በአራት ነጥቦች ይከተላሉ።

በስፓኝ ፕሪሜራ ዲቪዚዮን ባርሤሎና በሁለተኛ ግጥሚያውም ማላጋን 1-0 ለማሸነፍ ችሏል። ባርሣ በአካል ጉዳት ምክንያት ዋና ኮከቡን ሊዮኔል ሜሢን ማሰለፍ ባይችልም መልካም ጅማሮ ከማድረግ አልተገታም። እንደ ባርሤሎና ሁሉ አትሌቲኮ ማድሪድ፣ አትሌቲክ ቢልባዎና ቪላርሬያልም በሁለተኛ ግጥሚያዎቻቸው ለድል ሲበቁ በእኩል ስድሥት ነጥቦች ቀደምቱ ናቸው። ሬያል ማድሪድ ገና ዛሬ ማምሻውን ከግሬናዳ የሚጋጠም ሲሆን ካሸነፈ የአመራሩ ተሻሚ ነው።

Bundesliga - Bayern München vs. FC Nürnberg
ምስል picture-alliance/dpa

በጀርመን ቡንደስሊጋ ከሶሥት ግጥሚያዎች በኋላ ዶርትሙንድ፣ ሌቨርኩዝን፣ ባየርንና ማይንስ እኩል ዘጠኝ ነጥቦች ኖሯቿው ይመራሉ። የሰሜን ጀርመኑ ክለቦች በርሊንና ብሬመን ደግሞ ጥቂት ወረድ ብለው አምሥተኛና ስድሥተኛ ናቸው። በኢጣሊያ ሤሪያ-አ ውድድሩ ባለፈው ሰንበት ሲከፈት ከአንድ ግጥሚያ በኋላ ስምንት ክለቦች እኩል ሶሥት ነጥቦች በመያዝ ቀደምቱ ናቸው። በፈረንሣይ ሻምፒዮና ኦላምፒክ ማርሢይ ሶሥት ግጥሚያዎቹን በሙሉ በማሸነፍ በብቸኝነት አመራሩን ሲይዝ በፖርቱጋል ሊጋ ውስጥም ቤንፊካና ፖርቶ ግንባር ቀደም ሆነው ቀጥለዋል።

800 Meter Lauf Männer Goldmedaille Mohammed Aman Leichtathletik Weltmeisterschaft 2013 Moskau
ምስል Getty Images

ከሣምንት በፊት ሞስኮ ላይ የተጠናቀቀው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለኢትዮጵያ ከሞላ-ጎደል ስኬታማ ሆኖ ማለፉ አይዘነጋም። ኢትዮጵያ በሶሥት ወርቅ፤ ሶሥት ብርና አራት ናስ ሜዳሊያዎች በአጠቃላይ ውጤት ስድሥተኛ ስትወጣ ለዚሁ ታላቅ ድርሻ ከነበራቸው አትሌቶች አንዱም መሐመድ አማን ነበር። ወጣቱ አትሌት በ 800 ሜትር ሲያሸንፍ ከ 5 ሺህ ሜትር ርቀት በታች እንደ ኢትዮጵያዊ የዓለም ሻምፒዮን ሲሆንም የመጀመሪያው መሆኑ ነው። መሐመድ አማንን በውድድሩ መጨረሻ ዕለት እዚያው ሞስኮ እንዳለ በስልክ አነጋግሬው ነበር፤ ያድምጡ!

Sebastian Vettel Sieger Großer Preis von Belgien
ምስል Tom Gandolfini/AFP/Getty Images

በትናንትናው ዕለት ቤልጂግ ውስጥ የተካሄደው የፎርሙላ-አንድ አውቶሞቢል እሽቅድድም አሸናፊ ጀርመናዊው ዜባስቲያን ፌትል ሆኗል። ለፌትል የትናንቱ ድል በ 11 እሽቅድድሞች አምሥተኛው መሆኑ ነበር። በውድድሩ የቅርብ ተፎካካሪው የስፓኙ ፌርናንዶ አሎንሶ ሁለተኛ ሲወጣ የብሪታኒያው ሉዊስ ሃሚልተን ደግሞ ሶሥተኛ ሆኗል። ዜባስቲያን ፌትል አሁን በአጠቃላይ 197 ነጥቦች የሚመራ ሲሆን አሎንሶ በ 151 ይከተለዋል።

መሥፍን መኮንን

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ