1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከገምሻት ተራራ ስር

ዓርብ፣ ሐምሌ 20 2004

ሰሜን ወሎ ኡርጌሳ የሚባል ቦታ ላይ ነው የሚገኘው፤ ገምሻት አማተር ከያኒያን የስነፅሁፍ ክበብ ይሰኛል። የክበቡ አባላት የዛሬ ሶስት ዓመት ግድም መስከረም ወር ላይ ጥቂት ሆነው ሲሰባሰቡ ያለማንም አደራጅነት በራሳቸው ተነሳሽነት ነበር። ዛሬ ክበቡ 22 ወንዶችን እና 8 ሴቶችን ያካተተ የወጣት ስብስብ አባላት አሉት።

https://p.dw.com/p/15f4b

ሰሜን ወሎ ኡርጌሳ የሚባል ቦታ ላይ ነው የሚገኘው፤ ገምሻት አማተር ከያኒያን የስነፅሁፍ ክበብ ይሰኛል። የክበቡ አባላት የዛሬ ሶስት ዓመት ግድም መስከረም ወር ላይ ጥቂት ሆነው ሲሰባሰቡ ያለማንም አደራጅነት በራሳቸው ተነሳሽነት ነበር። ዛሬ ክበቡ 22 ወንዶችን እና 8 ሴቶችን ያካተተ የወጣት ስብስብ አባላት አሉት። እንዲያም ሆኖ ግን ክበቡ ዛሬም ድረስ የመሰብሰቢያ ጽ/ቤት የለውም። የክበቡ መስራች እና ሰብሳቢ የሆነው ወጣት ስለክበቡ አመሰራረት፣ የስራ እንቅስቃሴ እና ውጣ ውረድ የሚለን ይኖራል።

ገምሻት አማተር ከያኒያን የስነፅሁፍ ክበብን ካቋቋሙት ጥቂት ወጣቶች መካከል አንዱ ነው። አሁን የክበቡ ሰብሳቢ ሲሆን፤ በኮሌጅ ደግሞ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ ነው። ወጣት ሠኢድ ይመር መሐመድ ይባላል። ክበባቸው የሚገኝበትን ቦታ መልክዓምድራዊ አቀማመጥ እንዲህ በመግለፅ ይጀምራል።

የገምሻት ተራራ ከውስጡ እያፈለቀ ወደ ታች የሚያንፏልለው የጎሎ ወንዝ ለኅብረተሰቡ ከሲሳይነት ርግማን ጥፋቱ ቢጎላም፤ ወጣቶቹ ግን ተራራውን ተቀይመው አላኮረፉትም። ይልቁንስ ስሙን እንደቁመቱ አግዝፈው የአማተር ከያኒያን የስነፅሁፍ ክበባቸውን «ገምሻት» ሲሉ ሰየሙት። ያኔ የሰፈር ልጆች በራሳቸው ጊዜ ተሰባስበው ነበር ክበቡን ያቋቋሙት።

Symbolbild Theater und Masken
ምስል picture-alliance/dpa

እንደ ወጣት ሠኢድ ገለፃ የክበቡ አባላት በተለያዩ ሕዝባዊ በዓላት፣ በት/ ቤቶች ሚኒ ሚዲያዎች እንዲሁም በወላጆች ቀን እየተገኙ የስነፅሁፍ ትሩፋቶቻቸውን እና የተውኔት ስራዎቻቸውን በማቅረብ ከኅብረተሰቡ ጋ ለመገናኘት ይሞክራሉ። በወረዳ ደረጃ የሚዘጋጁ የስነፅሁፍ ውድድሮች ላይም ይሳተፋሉ። ከሶስት ዓመት በፊት ግን ክበባቸውን ለማቋቋም ያነሳሳቸው ምን ነበር?

የገምሻት አማተር ከያኒያን ክበብ አባላት ምንም እንኳን የተያያዙት ጎዳና አባጣ ጎርባጣ ቢበዛውም በየሳምንቱ እሁድ ዕለት ግን ሳይገናኙ የቀሩበት ጊዜ የለም። ምናልባት የክረምት ወቅት መጥቶ አብዛኛው አባላት ዘመድ ጥየቃ ወደ ተለያዩ ቦታዎች ከመንቀሳቀሱ ውጪ ማለት ነው። እሁድ ወጣቶቹ ተሰባስበው የሬዲዮ መርሐ ግብሮችን በአንድነት የሚያዳምጡበት ቀን ነው። ወጣት ሠኢድ በተለይ የዶቸ ቬለ ራዲዮ ስርጭትን ሳያዳምጥ ያለፈበት ቀን እንደሌለ ነው የሚገልፀው።

ወጣት ሠኢድ የአማተር ክበባቸውን ወክሎ ወደፊት ያነገቡትን ራዕይ በዚህ መልኩ ይገልፃል።

ሰሜን ወሎ ውስጥ የሚገኘውን ገምሻት አማተር ከያኒያን የስነፅሁፍ ክበብ በተመለከተ ከክበቡ መስራች እና ሰብሳቢ ጋር ያደረግነው ቆይታ በዚህ ይጠናቀቃል። ክበቡ ወደፊት የሚደግፈው አካል አግኝቶ የበለጠ እንዲደራጅ እና የወጣቶቹ ህልምም ዕውን እንዲሆን ምኞታችን ነው።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ