ከገረመው ደንቦባ ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ
ማክሰኞ፣ መጋቢት 17 2011ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በኦሎምፒክ ጨዋታዎች የተሳተፈችው በጎርጎሮሳዊው 1956 ዓ.ም. በሜልበርን አውስትራሊያ ነበር። የሳይክል ተወዳዳሪው ገረመው ደንቦባ እና የልዑካን ቡድኑ አባላት ከሰባት ቀናት በኋላ አውስትራሊያ ሲደርሱ እጅግ ተዳክመው ነበር። ገረመው ደንቦባ "አሜሪካ ስሪት አሮጌ ዳኮታ የሚባል አውሮፕላን ተፈቀደልን። አውስትራሊያ ለመድረስ ሰባት ቀን ሰባት ለሊት ፈጀ። ሰባት ቀን አየር ላይ ስንቆይ ምግብ የለ ደርቀን ሥጋ እና አጥንታችን ተጣብቆ ከጦር ምርኮኝነት የተለቀቅን ይመስል ነበር" ሲሉ ከ63 አመታት ገደማ በፊት ያደረጉትን ጉዞ ያስታውሱታል።
በሜልቦርን ኦሎምፒክ ኢትዮጵያ በአስር የውድድር አይነቶች በአስራ ሁለት አትሌቶች ተካፍላለች። አቶ ገረመው በአትሌቲክስ እና በሳይክል ውድድሮች ተካፍለዋል። በጎዳና ላይ በተደረገው የሳይክል ግልቢያ ውድድር 24ኛ ደረጃን ይዘው ጨርሰዋል። በውድድሩ ከአፍሪካ እና ከእስያ ተፎካካሪዎቻቸው ቀዳሚ ነበሩ።
አቶ ገረመው ኢትዮጵያ ካፈራቻቸው የሳይክል ተወዳዳሪዎች ሁሉ ስኬታማው ናቸው። በተለያዩ ውድድሮች ተሳትፈው 26 ዋንጫዎች፤ 32 ሜዳልያዎች ተሸልመዋል።
በባሕር ዳር ከተማ በተካሔደው 14ኛው የአፍሪካ የብስክሌት ሻምፒዮና የተመለከቱት አቶ ገረመው ዘርፉ በርካታ ችግሮች ቢኖሩበትም መልካም ስራ መታዘባቸውን ተናግረዋል።
ሙሉ መሰናዶውን ለማድመጥ የድምፅ ማዕቀፉን ይጫኑ
አለምነው መኮንን
እሸቴ በቀለ