1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከጎሣ ጭፍጨፋ በኋላ አዲስ ጅምር በርዋንዳ

ሐሙስ፣ መጋቢት 23 1996

ርዋንዳ ውስጥ አስከፊው የጎሣ ጭፍጨፋ ከተከሰተ ዛሬ ከአሥር ዓመት በኋላ ሀገሪቱ የኤኮኖሚ ዕድገት የሚታይባት ሰላም የሠፈነባት ቦታ ሆናለች። ሥልጣን የጠማው ጨካኝ ቡድን አንዳችም ርምጃ ለመውሰድ ሙከራ ባላደረገ ዓለም አቀፍ ኅብረተ ሰብ ፊት የፈፀመው ዘግናኙ ጭፍጨፋ ሲታሰብ፡ ርዋንዳ አሁን የደረሰችበት ደረጃ የሚያስገርም ነው ለማለት ይቻላል። ይህም ከአንድ ዓመት በፊት እንደገና የብዙኃኑን የርዋንዳ መራጭ ሕዝብ ድምፅ በማግኘት የተመረጡት የሀገሪቱ ፕሬዚ

https://p.dw.com/p/E0l3
የርዋንዳ ፕሬዚደንት ፖል ካጋሜ ደጋፊዎች
የርዋንዳ ፕሬዚደንት ፖል ካጋሜ ደጋፊዎችምስል AP

��ንት ፖል ካጋሜ ተወዳጅነት ከምን እንደመነጨ የሚጠቁም ሆኖዋል።

ከመዲናይቱ ኪጋሊ አየር ማረፊያ ወደ ከተማይቱ ማዕከል የሚወስደው ባለአራቱ ረድፍ ጎዳና ዳር እና ዳር አዳዲስ መደብሮጭና ጽሕፈት ቤቶች፡ ዘመናይ አፓርተማዎች እና መኖሪያ ቤቶች ይታያሉ። የግንባታ ክሬኖችም በብዛት አሉ። ባጠቃላይ ከተማይቱ በማበብ ላይ ናት። ይሁን እንጂ፡ የርዋንዳ ርዕሰ ከተማ አረጋጊውን ኮረብታማ ገፅታዋን አሁንም እንደጠበቀች ትገኛለች። የትራፊክ መጨናነቅ አይታይባታም፤ ጽዳታቸውን የጠበቁ የእግረኛ መንገዶች እና ይፋ ፓርኮችም ሮዝ ቱታ በለበሱና ለኅብረተ ሰቡ ጠቃሚ አገልግሎት ለማያበረከት በወጡ እሥረኞች እንክብካቤ ሲደረግላቸው ማየቱ የተለመደ ነው።

ከስምንት ወራት በፊት ፕሬዚደንት ካጋሜ እንደገና የሀገሪቱ መሪ ሆነው ከተመረጡ በኋላ በመዲናይቱ ባለው የአማሆሮ ስቴድየም ለተሰበሰበው ደጋፊያቸው ባሰሙት ዲስኩር ድሉ ሐቀኛ፡ ሊታጠፍ የማይችል እና የተጠበቀ ነው፤ ይኸው ድልም ርዋንዳ በትክክለኛው ጎዳና ላይ እንደምትገኝ ለቀሪው ዓለም ማስተማር ይገባዋል ማለታቸው ይታወሳል። የአርባ አምስቱ ዓመቱ የቀድሞ የዓማፅያን መሪ ፖል ካጋሜ ለሌላ ሰባት ዓመት ሀገሪቱን እንዲመሩ እንደሚመረጡ ስምንት ተኩል ሚልዮኑ የርዋንዳ ሕዝብ ካላንዳች ጥርጣሬ ነበር የጠበቀው። ይሁንና፡ በካጋሜ የርዋንዳ አርበኞች ግንባር ፓርቲያቸው ያሉት ብሩሕ አመለካከትን ያንፀባረቁ አባላት እንኳን ካጋሜ ዘጠና አምስት ከመቶ የመራጩን ሕዝብ ድምፅ ያገኛሉ ብለው አልጠበቁም ነበር። ግልፁ የካጋሜ ድል የመልሶ ግንባታና የዕርቀ ሰላም ምልክት መሆኑን በርዋንዳ ምክር ቤት የተወከሉት ከጠንካራውእ የርዋንዳ አርበኞች ግንባር ጋር የተጣመረው የንዑሱ ዴሞክራሲያዊ ማዕከላይ ፓርቲ እንደራሴና በምክር ቤት የሴቶች ቡድን ቃል አቀባይ ወይዘሮ አግነስ ሙካባራንጋ አስረድተዋል። ሙካባራንጋ በመቀጠልም፡ ርዋንዳውያን፡ ከጎሣ ጭፍጨፋ ታሪክዋ ጋር መኖር ያለባት ልዩ ሀገር ናት የሚሉዋት ርዋንዳ እንዴት መመራት እንዳለባትና ለዚሁ የአመራር ተግባርም ማንን እንደሚያምኑ በምርጫቸው በግልፅ አሳይተዋል ሲሉ ገልፀዋል። የፖል ካጋሜ መንግሥት ሒሰኞች ግን ርዋንዳ ውስጥ ነፃ ዕጩዎች ክትትል እንደሚደረግባቸውና እእኩል የመወዳደር ዕድል እንደሌላቸው፡ እንዲሁም፡ የሀገሪቱ ኤኮኖሚያዊ ዕድገትም የርዋንዳ መንግሥት

ከአሥር ዓመት በፊት የጎሣውን ጭፍጨፋ ያበቁት ካጋሜ የሀገራቸውን ሕዝብ የሁቱ፡ የቱትሲ ወይም የትዋ ፒግሚ ጎሣ ብለው ከፋፍለው ሳይሆን፡ እንደ አንድ የርዋንዳ ሕዝብ እንደሚመለከቱ ደጋግመው ከመግለፅ አልቦዘኑም። በዚሁ አነጋጋራቸውም በሀገሪቱ የሚነሡ ማንኞቹም የተቃውሞ ቡድኖችን እንደ ጎሠኛ ሊታዩ የሚችሉበትን አጣብቂኝ ሁኔታ ፈጥረውባቸዋል። ርዋንዳ ከጥቂት ጊዜ በፊት ባካሄደችው ሕገ መንግሥታዊ ሬፈረንደም አማካይነት በሀገርዋ የአንዱን ፓርቲ ሥርዓት አስወግዳለች፤ የተከበሩና ታሪ ፕሬዚደንት እንዳሉዋትና የሴቶች ውክልና ከፍተኛ የሆነበት ምክር ቤትም እንዳቋቋመች አሳይታለች። በዚህ ሁሉ መሀል ግን ለጎሣው ጭፍጨፋ ተጠያቂ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ ተከሳሾች ፍርድ፡ ትልቅ ርብርብ ስለሚያስፈልገው፡ አሁንም ገና ተጓታች እንደሆነ ይገኛል። ወደ አንድ መቶ ሺህ የሚጠጉ ተከሳሾች በየወህኒ ቤቶች ይገኛሉ። እስካሁን ጥፋታቸውን አምነው የተቀበሉ ሀያ ሦስት ሺህ እሥረኞች በነፃ ተለቀዋል፤ ሌሎች ሠላሣ እሥረኞችም በሚቀጥሉት ሣምንታት ይለቀቃሉ ተብሎ ይጠበቃል። እነዚህ ግለሰቦችም ከተፈቱ በኋላ የጎሣውን ጭፍጨፋ ወደፈፀሙበት ትውልድ መንደራቸው የሚመለሱበትና በዚያም ከገደሉዋቸው ግለሰቦች ቤተ ዘመዶች ጋር አብረው የሚኖሩበት አሠራር በአሁኑ ጊዜ ርዋንዳ ውስጥ የተለመደ ሂደት እየሆነ መጥቶዋል።