1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከ50ሺህ በላይ ተፈናቃዮች ወደ ቤንሻንጉል ክልል ተመለሱ 

ረቡዕ፣ ሰኔ 23 2013

በአማራ ክልል ቻግኒ ከተማ አቅራቢያ ራንች የተባለው የተፈናቃዮች መጠለያ ሙሉ በሙሉ መዘጋቱን የአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መንግስታት ዐስታወቁ። በመጠለያው የነበሩ ከ50 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች በሙሉ ወደ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ መመለሳቸውን የአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ የጋራ ግብረ ኃይል አመልክቷል።

https://p.dw.com/p/3vpc9
Äthiopien Rückkehrer aus Benshangul Gumuz
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

50ሺህ 553 ተፈናቃዮች ባለፈው ሳምንት ተጠቃልለው ተመልሰዋል

በአማራ ክልል ቻግኒ ከተማ አቅራቢያ ራንች የተባለው የተፈናቃዮች መጠለያ ሙሉ በሙሉ መዘጋቱን የአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መንግስታት ዐስታወቁ። በመጠለያው የነበሩ ከ50 ሺህ በላይ ተፈናቃዮች በሙሉ ወደ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ መመለሳቸውን የአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ የጋራ ግብረ ኃይል አመልክቷል። ዳንጉር፣ ቡለን፣ ድባጤ እና ማንዱራ ወረዳዎች ወደሚገኙ ማእከላት መመለሳቸውም ተገልጧል። ከጊዜያዊ ርዳታው ባሻገር ማንዱራ ወረዳ ላይ ባለፈው እሁድ ባሕላዊ እርቅ መከናወኑም ተጠቅሷል። ለማቋቋሚያ ግማሽ ቢሊዮን ብር ያስፈልጋልም ተብሏል። ከዚህ ቀደም አንዳንድ ተፈናቃዮች የፀጥታው ስጋት ሳይቀረፍ ያለፍላጎታቸው ወደ ቤንሻንጉል ክልል መመለሳቸውን ለዶይቸ ቬለ ተናግረው ነበር። ዓለምነው መኮንን ከባሕር ዳር ዝርዝር ዘገባ ልኮልናል። 

የሁለቱ ክልላዊ መንግስታት በደረሱት የጋራ ስምምነት መሰረት ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ተፈናቅለው በአማራ ክልል ራንች የተፈናቃዮች መጠለያ የነበሩ 50ሺህ 553 ተፈናቃዮች ባለፈው ሳምንት ተጠቃልለው ወደ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በዳንጉር፣ በቡለን፣ በድባጤና በሙንዱደራ መጠለያዎች መዛወራቸውን የአማራና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ የጋራ ግብረ ኃይል አባል አቶ በትግሉ ተስፋሁን ገልፀዋል። በአሁኑ ሰዓት የጊዜያዊ እርዳታ አቅርቦትና ጎን ለጎንም ባህላዊ እርቅ እየተካሄደ እንደሆነም አቶ በትግሉ አመልክተዋል።ተፈናቃዮች ያለፍላጎታቸው ነው ወደ ነበሩበት ክልል የተመለሱት የሚለው ክስ መሰረት የሌለውና ምናልባትም የተለየ ትቅም ያላቻው ሰዎች የሚያስወሩት “ወሬ” ብለውታል።ተፈናቃዮችን ሙሉ ለሙሉ መልሶ ለማቋቋም ግማሽ ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግም አቶ በትግሉ አመልክተዋል።

Äthiopien Rückkehrer aus Benshangul Gumuz
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

ከተመላሾች መካከል በዳንጉር ጊዜያዊ መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ተመላሽ በመመለሳቸው ደስተኛ እንደሆኑና እየተደረገላቸው ያለው ድጋፍም በቂ ነው ብለዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ታሲሳ በስልክ እንደገለፁልን የራንች የተፈናቃዮች መጠለያ መዘጋቱንና ተፈናቃዮች መመለሳቸውን፣ ተመላሾችም ተቀባዩም ህዝብ ደስተኞች ናቸው፡፡ 
የአማራ ክልል አደጋ መከላከል፣ ምግብ ዋስትናና ልዩ ድጋፍ የሚሹ አካባቢዎች ማስተባበሪያ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ዘላለም ልጃለም ተፈናቃዮች በሙሉ መመለሳቸውንና ካምፑ መዘጋቱን አረጋግጠዋል፡፡

በያዝነው ኣመት መጀመሪያ ጀምሮ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ተፈጥሮ በነበረው አለመረጋጋት በርካቶች በአካባቢው ታጣቂዎች በግፍ መገደላቸውና በርካቶች ከቀያቸው መፈናቀላቸው የሚታወስ ነው፡፡

ዓለምነው መኮንን

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሀመድ