ኪስማዩና የሶማሊያ ተፋላሚ ኃይሎች
ረቡዕ፣ መስከረም 9 2005የሶማሊያው ደፈጣ ተዋጊ ቡድን አሸባብ ከመቅዲሾ በስተደቡብ ከምተገኘዋ ከኪስማዩ ካፈገፈገ ቀናት ተቆጥረዋል ። ይሁንና ከተማይቱ እስከ ዛሬ በአፍሪቃ ህብረት ኃይል በሚደገፈው በሶማሊያ መንግሥት ወታደሮች እጅ አልገባችም ። የመቅዲሾ የዶቼቬለ ወኪል አዌስ ሁሴን እንዳለው አሁን በከተማይቱ የአስተዳደር ክፍተት ተፈጥሯል ። ነዋሪዎችም ከተማይቱን ለቀው እየሄዱ ነው ።
ደቡብ ሶማሊያ የምትገኘው የወደብ ከተማ ኪስማዩ ለሶማሊያው ደፈጣ ተዋጊ ቡድን አሸባብ ደቡባዊ ዘመቻዎች በማዕከልነት የምታገለግል ቁልፍ ከተማ ነበረች ። አሸባብ ከዚህች ከተማ ያፈገፈገው መቅዲሾ የሚገኘው የዶቼቬለ ወኪል አዌስ ሁሴን እንዳለው በአሚሶምና በሶማሊያ ወታደሮች ከባድ ኪሳራ ከደረሰበት በኋላ ነው ።
« ከኪስማዩ ውጪ ከባድ ውጊያ ነበር በዚህ ውጊያ ትልቁ ምሽጋቸው በአሚሶምና በሶማሊያ ወታደሮች ወድሟል ።ጠንካራ ይዞታቸው ከተደመሰሰ በኋላ ነው ከተማይቱን ለቀው መውጣት የጀመሩት ። »
ትንንት በወጡ ዘገባዎች መሰረት አሸባብ አዛዦቹን ከኪስማዩ አስወጥቶ እግረኛ ተዋጊዎችን እዚያው ትቷል ። አዌስ ሁሴን እንደሚለው አሸባብ ኪስማዩን ለቆ የወጣው ከ3ቀናት በፊት ቢሆንም እስከ ዛሪ ከሰአት በኋላ ድረስ ከተማይቱን የያዘ ኃይል የለም ።
«ከኪስማዩ የምንሰማው ዜና ፣ የአሸባብ ኃይሎች ከ 3 ቀናት በፊት ከከተማይቱ ሸሽተው ኪስማዩ ዙሪያ ወደ ሚገኙ አካባቢዎች በተለይም ወደ ሰሜን ኪስማዩ አካባቢ እንደሄዱ ነው የሚጠቁመው ። በአፍሪቃ ህብረት ሰላም አስከባሬ ኃይል አሚሶም የሚደገፉት የሶማሊያ መንግስት ወታደሮች እስካሁን ከተማይቱ አልገቡም ። ያሉት ከከተማይቱ ውጭ ነው ። በከተማዋ አሁን የአስተዳደር ክፍተት አለ »
ይህ የአስተዳደር ክፍተትም እንደ አዌስ ነዋሪዎችን ስጋት ውስጥ ከቷል ። በዚህ ሰበብ በርካታ የከተማይቱ ነዋሪዎች ወደ ሌላ አካባቢ ሸሽተዋል ። በአዌስ አባባል በኪስማዩ ለህዝቡ የእለት ተለት ኑሮ አሰፈላጊ የሆኑ እንቅስቃሴዎች የሉም ።
«ነዋሪዎች በተፈጠረው የአስተዳደር ክፍተት ስጋት ላይ ነን ያላሉ ። የሚያስተማምን ነገር የለም ። ዝርፊያ አለ ። ከተማይቱን የሚቆጣጠር ስለሌለ አንዳንድ ዝርፊያ ይካሄዳል ። የንግድ እንቅስቃሴ የለም ። ሁሉም ነገር ቆሟል ። ከተማይቱን የሚያስተዳድር ባለመኖሩ ሰላማዊ ሰዎች ከተማይቱን ለቀው እየወጡ ነው ።»
አሸባብ ከኪስማዩ ከወጣ ሶስት ቀናት ከተቆጠረና የአስተዳደር ክፍተትም መፈጠሩ ከታወቀ ፣ የሶማሊያ መንግሥት ወታደሮች ከተማይቱን ያልያዙበት ምክንያት ምን ይሆን ? ለአዌስ ያቀረብኩት ጥያቄ ነበር ።
«ይህ በኪስማዩና አካባቢው የሚኖሩ ሰዎች ርስ በርስ የሚጠያያቁት ጉዳይ ነው ። ከ3 ቀናት አንስቶ የአስተዳደር ክፍተት አለ ። ሆኖም ኪስማዩ የሚገኝ ዘጋቢ እነዚህ ኃይሎች በሰዓታት ውስጥ ወደ ከተማይቱ ለመግባት እየሞከሩ መሆኑን ተናግሯል »
አሸባብ ከጠንካራ ይዞታው ከኪስማዩ ቢወጣም አሁንም በቁጥጥሩ ስር ያሉ ሌሎች አካባቢዎች አሉ ። አዌስ እንዳለው ከነዚህ መካከል በመካከለኛው ጁባ ያሉት ጃማማና ጃሊብ ይገኙበታል ። አሸባብ ኪስማዩን ለቆ መውጣቱ እንደ ትልቅ ሽንፈት ተወስዷል ። ይሁንና በደፈጣ ጥቃቱ መቀጠሉ በብዙዎች ግምት አያጠያይቅም ።
ሂሩት መለሰ
አርያም ተክሌ