1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማርክስ ከተወለደ 200 ዓመት ተቆጠረ

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 30 2010

  በፍልስፍናው ዓለምን መቀየር የቻለው ማርክስ ለራሱ ሳይሆን እድሜ ልኩን ለሌሎች ሰዎች የታገለ በመሆኑ ከቡዙዎች ይለያል።የኮምኒዝም ፍልስፍና አፍላቂው ማርክስ በአመለካከቱ ሰበብ ከሀገሩ ተሰዶ በስደት ኖሮ በስደት ተቸግሮ ነው ያለፈው።

https://p.dw.com/p/2xNtY
Kultur.21 Karl Marx in Farbe
ምስል DW

የካርል ማርክስ ልደት 200ኛ ዓመት

 ፍልስፍናው ብዙ ተከታዮችን አፍርቷል። ሀሳቡ በብዙ የዓለም ክፍል ተቀባይነት አግኝቶ የአብዮት እና ለውጥ ምክንያት ሆኗል። ፈላስፋ፣ የምጣኔ ሀበት ሊቅ ፣የታሪክ ምሁር ጋዜጠኛ  እና ደራሲ  ጀርመናዊው ካርል ማርክስ። የኮምኒዝም ፍልስፍና አፍላቂው ማርክስ በአመለካከቱ ሰበብ ከሀገሩ ተሰዶ በስደት ኖሮ በስደት ተቸግሮ ነው ያለፈው። በፍልስፍናው ዓለምን መቀየር የቻለው ማርክስ ለራሱ ሳይሆን እድሜ ልኩን ለሌሎች ሰዎች የታገለ በመሆኑ ከቡዙዎች ይለያል። ጀርመን የተማሩት እና የሚሰሩት ዶክተር ልጅ አስፋወሰን አሥራተ  የአፍሪቃ እና የመካከለኛው ምሥራቅ የንግድ አማካሪ ደራሲ እና የፖለቲካ ተንታኝ ቀደም ሲል አድናቆት የቸሩት ማርክስ ምዕራብ ጀርመን በራይንድ ፋልስ ግዛት በምትገኘው ትሪየር በተባለችው ከተማ ከ200 ዓመት በፊት ከባለፀጋ ይሁዲ ቤተሰብ ነበር የተወለደው። አባቱ የህግ ምሁር  እናቱ ደግሞ የሀብታም ልጅ ነበሩ። 4 ዓመት ሲሆነው ቤተሰቦቹ ሃይማኖታቸውን ወደ ፕሮቴስታንት እምነት ቀየሩ። ማርክስ ከቤተሰቡ 9 ልጆች ሦስተኛው ነበር።  

Enthüllung Karl-Marx-Statue in Trier
ምስል picture-alliance/AP Photo/M. Probst

ምንም ሳይጎድልበት ተቀማጥሎ ያደገው ማርክስ ፣ጉልበቱ ለሚበዘበዘው ሠራተኛ መብት መታገል የጀመረው የሚደርስበትን ጭቆና በቅርብ መመልከት ከቻለ በኋላ ነበር። ማርክሲዝም በሀያኛው ክፍለ ዘመን ከፈለቀበት ከአውሮጳ ተነስቶ አፍሪቃን ጨምሮ ብዙውን የዓለም ክፍል አዳርሷል። ሆኖም ከሶቭየት ህብረት መፈራረስ በኋላ እየከሰመ የሄደ ርዕዮተ ዓለም ነው። በአሁኑ ጊዜ በኮምኒዝም ስርዓት የሚተዳደሩ በጣት የሚቆጠሩ ሀገራት ናቸው።በዶክተር ልጅ አስፋወሰን አስተያየት የሰው ልጆች መብት እንዲከበር የሠራተኛው መብት እንዲጠበቅ እድሜውን በሙሉ ሲታገል ኖሮ ያለፈው የማርክስን ፍልስፍና፣ማርክሲዝምን እንከተላለን በሚሉ እና ይሉ በነበሩ ሀገራት የሚሆነው እና የሆነው ታቃራኒው ነው። ይህም ማርክሲዝም በትክክል መተግበሩን አጠያያቂ ያደርገዋል ይላሉ።

Asfa-Wossen - deutschsprachiger Autor und Unternehmensberater
ምስል picture-alliance/dpa/E. Elsner

የማርክስ ፍልስፍና ከኖረበት ዘመን አልፎ  እስካሁን ድረስ ተሻግሯል። ሀሳቦቹ ዛሬም ድረስ ሰፊ ተቀባይነት አላቸው። ያኔ እርሱ የተቃዋመው እና የተነበየው የካፒታሊዝም ስርዓት አልጠግብ ባይነት ያስከተለው መዘዝ በቅርብ ዓመታት ዓለማችን በገጠሟት የገንዘብ ቀውሶች ታይቷል ይላሉ ዶክተር አስፋወሰን አሥራተ ከሶሻሊስት አሰተሳሰብ አባቶች አንዱ የሆነው ማርክስ በሀያኛው ክፍለ ዘመን ፖለቲካ እና ግጭቶች ውስጥ ዐብይ ድርሻ የነበራቸው የኮሚኒስት ማኒፌስቶ እና  ዳስ ካፒታል ወይም ካፒታል የተባሉት መፀሀፎች ደራሲ ነው። እነዚህና ሌሎች በተከታታይ የጻፋቸው ዘመን የማይሽራቸው ድርሰቶቹ የህያውነቱ ምስክር ናቸው። ዓለምን በፍልስፍናው የቀየረው ካርል ማርክስ ካረፈ ባለፈው መጋቢት  138 ዓመት ተቆጠረ።

ኂሩት መለሰ 

ማንተጋፍቶት ስለሺ