ኬንያ የስደተኞች መጠልያ የመዝጋት እቅድና ስጋቱ
ዓርብ፣ ግንቦት 5 2008በኬንያ የስደተኞና የደሕንነት ጉዳይን የሚከታተለዉ የኬንያ የሃገር አስተዳደር ሚኒስቴርና ብሔራዊ የመንግስት ማስተባበርያ ቃላ አቀባይ መዌንዳ ንጆካ ሃገሪቱ እንዲህ ዓይነቱን ርምጃ ለመዉሰድ የተነሳሳችበት ሌላ ምክንያት በአሁኑ ወቅት ሶማልያ በተለየ ሁኔታ በመረጋጋቷ፤ ስደተኞች ወደ ሃገራቸዉ መመለስ አለባቸዉ ብለን ስላሰበን ነዉ ሲሉ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። በዳዳብ መጠለያ ጣብያ የሚገኙትን ሶማልያዉያን ስደተኞች ወደ መጡበት ለመመለስ ለጅማሮ የኬንያ መንግስት 10 ሚልዮን ዶላር መመደቡም ተገልፅዋል። ቃላ አቀባይ ንጆካ ጉዳዩ ከተመደበለት የበለጠ ገንዘም ሊያስወጣ እንደሚችል፤ ዉስብስብና ረጅም ጊዜን እንደሚወስድም ሳይገልፁ አላለፉም።
ንጆካ ስደተኞቹን ለመመለስ የተቀመጠዉ ቀነ ገደብ እና አካሄዱን በተመለከተ፣ «ትላንት በአገር አስተዳደር ሚኒስቴር ልዩ ግብረኃይል ተመስረተዋል። ይህ ግብረኃይል ሪፖርቶችንና የጊዜ ሴሌዳን ለሚንስትሩ በዚህ ወር መጨረሻ እንድሚያሰረክብ ይጠበቃል። እቅዱና የጊዜ ሴሌዳዉ አንዴ ከመጣ ሚንስትሩ ስደተኞቹን ለመመለስ ምን ያህል ጊዜ እንደሚወስድ እና መቼ እንደሚጀምር ማወቅ ይቻላል። ይህን ስል በጣም በቅርብ ጊዜ ዉስጥ ወይም በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ዉስጥ እንደምንጀምር ነዉ። ስደተኞቹን ለመመለስም ሦስት አማራጮች አሉን። ወይ ወደ መጡበት ሃገር መመለስ ነዉ ወይም ስደተኞቹን ለመቀበል ፍላጎት ወደ አላቸዉ አገር መላክ ነዉ። ስደተኞቹ ሊመለሱ የሚችሉት ደግሞ ሶማሊያ ዉስጥ ደሕንነት ወደአለበት አከባቢ ነዉ።»
መዌንዳ ንጆካ ሶማሊያ ትልቅ መሆኑዋን እና ስደተኞች የደንነት ችግር ወደሌለበት አካባቢ እንዳሚላኩ ተናግረዋል።
በሌላ በኩል በኬንያ የተባበሩት መንግስታት አካል የሆንዉ ከፍተኛዉ የስደተኞች ማስተባበርያ ኮሚሽን በዚህ ጉዳይ ከኬንያ መንግስት ጋር ለመወያየት እየሞከረ መሆኑን የገለፁት የኮሚሽኑ ቃላ አቀባይ ዱክ መዋንቻ ኬንያ ስደተኞችን ለማስተናገድ ዓለም አቀፍ ግዴታ እንዳለባት ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። የሶማልያ ስደተኞችን የመመለስ ሁኔታዉ የዓለም አቀፍ ሕግጋቶችን ጠብቆ በፍላጎትና ደንነታቸዉ በተጠበቀ መልኩ መሆን እንዳለበትም መዋንቻ ገልፀዋል።
ይህ የኬንያ ርምጃ ከዓለም አቀፍ ሕግ ጋር ይፃረራል ሲሉ ትችት የሚያቀርቡ ጥቂት አይደሉም። የኬንያ መንግስት ይህን ርምጃ የሚወስድ ከሆነ የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን «UNHCR» ከመንግስት ጎን እንደማይቆም ዱክ መዋንቻ ተናግረዋል።
ምክንያቱም ይላሉ ቃልአቀባዩ፣ «እንደ ዓለምአቀፉ ሕግ ተገን የሚጠይቁ ስደተኞችን ሊፈቀድላቸዉ ይገባል። መመለስም ካለባቸዉ በፍላጎታቸዉ በራሰቸዉ መወሰን አለባቸዉ። ለዚህ ዉሳኔ ጠለቅ ያለ መረጃ እንድያገኙ ማድረግ ይኖርባቸዋል። በፍቃዳቸዉ መመለስ ከፈለጉም ደሕነት እና ክብር በተሞላበት ርዳታ ልደረግላቸዉ ይገባል።»
ግን ለኬንያ መንግስት ጉዳዩ ልዩ ነዉ ይላሉ ንጆካ፣ «አይደለም፣ አይደለም፣ ልንገርህ። አዉሮጳ ከስርያ በመጡ ስደተኞች ተጥለቅልቃች። ሶርያ ከሶማሊያ በበለጠ የደሕነት ችግር አለባት። አዉሮጳዎች ለደሕነታቸዉ ሲሉ ድንበር ዘግተዋል። ስለዚህ ለየትኛዉም መንግስት የመጀመርያ ግዴታ የሚሆነዉ የዜጎቹን እና የአገሩን ደንነት ማስጠበቅ ነዉ ። ስለዚህ የዓለምአቀፍ ሕግጋት የሚባለዉ ጥያቄ የሚመጣዉ አንድ አገር የህዝቡን ደንነት ስያስጠብቅ ብቻ ነዉ። ከዓለምአቀፍ ሕግጋት ጋር ለመቆራኘት ሕዝብን እስኪጎዳ ድርስ መሄድ የለብህም።»
ይህ የሰደተኞች መጠልያ መዘጋቱ ለኬንያም ሆነ ለጎረቤት አገሮች ላይ ሰብዓዊ ቀዉስ ሊያስከትል እንደሚችል ቃል-አቀባይ ዱክ መዋንቻ ተናግረዋል ።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ