1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ፤ ሠላም እና ጦርነት

ሐሙስ፣ ነሐሴ 3 2010

ታሽስኬዲ እና ደጋፊዎቻቸዉ ትናንት የምርጫ ኮሚሽኑን ሕንፃ ከበዉ ምርጫዉ እንዳይጭበረበር ሲጠይቁ ነበር።ከፖሊስ ጋር ተጋጭተዉ ብዙ ሰዉ ቆስለዋል።UDPS በሚል የፈረንሳይኛ ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የታስሽኬዲ ፓርቲ ቃል አቀባይ ፊስቶን ምቡዮ ግን ያስጠነቅቃሉ ምርጫዉ ነፃ እና ትክክል ካልሆነ ሌላዉ አማራጭ ጦርነት ነዉ።

https://p.dw.com/p/32uoM
DRC Präsident Joseph Kabila
ምስል Reuters/K. Katombe

ኮንጎ

የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ የረጅም ጊዜ ፕሬዝደንት ጆሴፍ ካቢላ በመጪዉ ታሕሳስ ሊደረግ በታቀደዉ ፕሬዝደንታዊ ምርጫ እንደማይወዳደሩ ትናንት በይፋ አስታዉቀዋል።የገዢዉ ፓርቲ ቃል አቀባይ ትናንት እንዳስታወቁት የካቢላ የቅርብ ታማኝ የቀድሞዉ የኮንጎ የሐገር ዉስጥ ጉዳይ ሚንስትር ኢማኑኤል ራማዛኒ ሻዳርይ ፓርቲዉን ወክለዉ ለፕሬዝደንትነት ይወዳደራሉ።የፓርቲዉን የመሪነት ሥልጣን ግን ካቢላ እንደያዙ ናቸዉ።የካቢላ ድብቅ ሥልት፤የአስመራጭ ኮሚሽኑ አሰራር እና የተቃዋሚ ፓርቲዎች ስሞታ፤ ዚሞነ ሽሊንድቫይን እንደዘገበችዉ፤ የኮንጎን መጪ ፖለቲካ በሰላም እና ጦርነት መሐል እንዳቃረጠዉ ነዉ። ነጋሽ መሐመድ ዝርዝሩን አጠናቅሮታል።

እንደ ጎርጎሪያኑ አቆጣጠር በ2001 በሰዉ እጅ የተገደሉትን የአባታቸዉን መንበር እንደ ዙፋን የወረሱት ጆሴፍ ካቢላ ካባንጋ ዛሬም ፕሬዝደንት ናቸዉ።በሐገሪቱ ሕግ መሠረት ሥልጣን መልቀቅ የነበረባቸዉ ከሁለት ዓመት በፊት ነበር።አልለቀቁም።በዉርስም፤ በምርጫም በጉልበትም 17 ዓመት የቆዩበትን ሥልጣን ከእንግዲሕም «አልቅም» ወይም ባዲሱ ምርጫ «እንዳዲስ እቀጥላለሁ» ይላሉ ተብሎ ሲነገር፤ሲወራ፤ ሲፈራ፤ ትናት «አልፈልግም» አሉ።የ47 ዓመቱ ጎልማሳ።
የረጅም ጊዜዉ ገዢ የትናንት ዉሳኔ ጦርነት፤ግጭት፤በሽታ ለሚፈራረቅበት ለኮንጎ ሕዝብ እፎይታ ነዉ-የሆነዉ።ግን ሥጋትም አለዉ።በሰወስት ምክንያት።የሥልጣናቸዉን ዋልታ እና ማገር የጦር ኃይሉን እንዳዲስ በማደራጀት ሰም የአዛዥነቱን ሥልጣን ለታማኝ ጄኔራሎቻቸዉ ደልድለዋል።
                                           
«ጦር ኃይሉን እንዳዲስ አደራጅተዉታል።በአዛዥነት ሥልጣን አዳዲስ ጄኔራሎችን ሾመዋል።ተሿሚዎቹ በሥልጣን ላይ መቆየት የሚፈልጉ እና የሥርዓት ለዉጥ መደረጉን የማይይቀበሉ ናቸዉ።ይሕ፤ ጦር ኃይሉ ሚሊሺያዎችን ጓጉጦ አዲስ ግንባር ሊከፍት ይችላል።በመጨረሻም ካቢላ የጦር አዛዣችሁ እኔ ነኝ ብለዉ በሥልጣን ለመቆየት የሚረዳቸዉ አዲስ ንቅናቄ ለማድረግ ይጠቀሙበት ይሆናል።»
ይላሉ የፖለቲካ ፕሮፌሰር ፓምፊሊ ንጎማ።የንጎማ አስተያየት ቢስት እንኳን ካቢላ ከሥልጣን ላለመራቅ ታዛቢዎች እንደሚሉት ሌሎች ሁለት ስልቶች አላቸዉ።የዳግም ግንባታ እና የዴሞክራሲ ሕዝባዊ ፓርቲ (PPRD) የተባለዉን ፓርቲያቸዉን የመሪነት ሥልጣን እንደያዙ ነዉ።ፓርቲያቸዉን ወክለዉ ለፕሬዝደንትነት እንዲወዳደሩ የሰየሟቸዉ ዕጩ ከታማኞቻቸዉ ሁሉ ታዛዣቸዉን ነዉ።ኢማኑኤል ራማዛኒ ሻዳርይ።
በምርጫዉ ሻዳርይ እንዲያሸነፉ 17 ዓመት የተጠራቀመዉ ገንዘብ፤ኃይል፤የማጭበርበር ሥልት ሁሉም ገቢር ይሆናል።ሻደርይ ካሸነፉ በኋላ ታዛቢዎች እንደሚሉት ካቢላ ቭላድሚር ፑቲን፤ ሻደራይ ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ ይሆናሉ።
የተቃዋሚ ፓርቲ ፖለቲከኞች እንደሚሉት ሻዳርይ እንዲያሸንፉ ዕጩዎቻቸዉን ማዋካብ ማንገላታቱ ካሁኑ ተጀምሯል።በቅርቡ ዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች መዳኛ ፍርድ ቤት ከእስር የለቀቃቸዉ የካቢላ ቀንደኛ ተቀናቃኝ የቀድሞ ምክትል ፕሬዝደንት ዤን ፔሪ ቤምባ ለታሕሳሱ ምርጫ ቢመዘገቡም ከምርጫ ኮሚሽኑ ጋር እንደተወዛገቡ ነዉ።
ሌላዉ የካቢላ ዋና ተቀናቃኝ ሞይስ ካቱምቢ ሐገር እንዳይገቡ ታግደዋል።ከገቡ ከዚሕ ቀደም ሰርተዉታል በተባለ ወንጀል እንደሚታሰሩ እየተነገረ ነዉ።ሰዉዬዉ ግን እወዳደራለሁ እያሉ ነዉ።የዕጩ ምዝገባዉ ጊዜ ግን ትናንት አብቅቷል። 
ሰወስተኛዉ ጠንካራ ዕጩ ፌሊክስ ታሺስኬዲ ናቸዉ።ታሽስኬዲ እና ደጋፊዎቻቸዉ ትናንት የምርጫ ኮሚሽኑን ሕንፃ ከበዉ ምርጫዉ እንዳይጭበረበር ሲጠይቁ ነበር።ከፖሊስ ጋር ተጋጭተዉ ብዙ ሰዉ ቆስለዋል።UDPS በሚል የፈረንሳይኛ ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የታስሽኬዲ ፓርቲ ቃል አቀባይ ፊስቶን ምቡዮ ግን ያስጠነቅቃሉ ምርጫዉ ነፃ እና ትክክል ካልሆነ ሌላዉ አማራጭ ጦርነት ነዉ።
                                  
«ለምርጫ ኮሚሽኑ ፕሬዝደንት የሐገር ወዳዶች መልዕክት አለኝ።ሐገሪቱ ዳግም ከጦርነት እንዳትዘፈቅ ከፈለጉ ተዓማኒና ግልፅ ምርጫ ማደራጀት አለባቸዉ።ሰላማችንን የሚያስከብረዉ እንዲሕ ዓይነቱ ምርጫ ብቻ ነዉ።ገዢዉ ፓርቲ እንዲያሸንፍ ከተባበሩ ወይም ምርጫዉን ሒደት ካጭበረበሩ ግን አመፅ ይከተላል።እና ለሚፈሰዉ ደም እሳቸዉ ተጠያቂ ይሆናሉ።»
ምርጫ እና ጠመንጃ የተፋጠጡባት የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ወጣቶች ሁለቱንም የሚሹት አይመስሉም።በተለይ LUNCH የተባለዉ የወጣቶች ማሕበር ተወካይ ኢኖች ንያምዊሲ እንደሚለዉ ምርጫዉም-ጠመንጃዉም የሰፊ-ሐብታሚቱን ግን የግጭት፤ ግድያይቱን ሐገር-ሰፊ ችግር አያስወግድም።

Belgien Brüssel | Protest gegen Joseph Kabila, Präsident Kongo
ምስል picture-alliance/dpa/Belga/H. Kaghat
Kongo Emmanuel Ramazani Shadary
ምስል REUTERS

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ