ወባን የማጥፋቱ ጥረት
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 18 2008በመላዉ ዓለም የወባ ቀን ሲታሰብ የዓለም የጤና ድርጅት ይፋ ባደረገመዉ መረጃ መሠረት አልጀሪያ፤ ቦትስዋና፣ ኬፕ ቬርዴ፣ ኮሞሮስ፣ ደቡብ አፍሪቃ እና ስዋዚላንድ እስከ ጎርጎሪዮሳዊዉ 2020ዓ,ም ድረስ ወባን ፈፅመዉ ማጥፋቱ ሊሳካላቸዉ እንደሚችል ተነግሯል። መረጃዎች እንደሚያመለክቱት ደቡብ አፍሪቃ ዉስጥ የዛሬ 16ዓመት በወባ በሽታ የሚሞተዉ ሰዉ ቁጥር በዓመት 64 ሺህ ነበር። በቅርቡ የተካሄደዉ በሽታዉን የማጥፋት ጥረት የሟቾቹ ቁጥር ወደ11 ሺህ ገደማ ዝቅ እንዲል አስችሏል። ደቡብ አፍሪቃ ዉስጥ የወባ በሽታ በተለይ ከስዋዚላንድ፣ ዚምባቡዌ እና ሞዛምቢክ በምትጎራበትበት የድንበት አካባቢ ጎልቶ እንደሚታይ ነዉ የሚገለጸዉ። እናም በዚህች ሀገር ወባን በታቀደዉ ጊዜ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ለማጥፋት በሀገር ዉስጥ ከሚካሄደዉ የቀናጀ ጥረት በተጨማሪ ከጎረቤት ሃገሮችም ጋር በመተባበር በጋራ ወባን የመቆጣጠሩ ሥራ እንደሚከናወን የዓለም የጤና ድርጅት አመልክቷል። ከአፍሪቃ ዉጭም ቻይና፣ ማሌዢያ፣ እና ደቡብ ኮሪያ ከእስያ፣ ኮስታ ሪካ፤ ብራዚል፣ ኤል ሳልቫዶር፣ ሜክሲኮ፣ አርጀንቲና፣ ፓራጓይ፣ ኤኳዶር እንዲሁም ሱሪናም ከላቲን አሜሪካም በተጠቀሰዉ የጊዜ ገደብ ወባን ፈፅመዉ ያጠፋሉ ተብሏል። ኢራን፣ ስዑድ አረቢያ፣ ኦማን፣ ሲሪ ላንካ፣ ቤታን፣ ቲሞር ሌስቴ እና ኔፓልም በዚሁ ጊዜ ዉስጥ ከወባ ስጋት እንደሚላቀቁ ይጠበቃል። ባለፈዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 214 ሚሊየን የሚሆን ሕዝብ በወታ ተይዟል። 438 ሺዉ ደግሞ ወባ ፈጅቷቸዋል። ከ10 ሟቾቹ ዘጠኙ ደግሞ ከሰሃራ በስተደቡብ በሚገኙ ሃገራት የተከሰተ መሆኑን የዓለም የጤና ድርጅት አመልክቷል። ኢትዮጵያስ? ምላሹን ከድምጡ ዘገባዉ ያገኛሉ።
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ