1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉሃ ህይወት፤ ዉሃ ጥፋት

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 27 2005

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሚከሰቱ የባህር ማዕበሎች ብዛትና ኃይል እየጨመረ መሄዱን ባለሙያዎች ያመለክታሉ። ሰሞኑን ሳንዲ የሚል ስያሜ የተሰጣት ማዕበል በካረቢያን አካባቢ ሀገሮች ጀምራ ዩናይትድ ስቴትስንና ካናዳን አዳርሳለች።

https://p.dw.com/p/16dpI
ምስል Reuters

የዓለማችንም ሆነ ሰዉነታችን አብዛኛዉ በፈሳሽ የተሞላ መሆኑን ሳይንስና ምርምሩ ይናገራል። ስለፍጥረተ ዓለም የሚያወሱ መፅሐፍትም ሰማይ ከምንለዉ በላይ ዉሃ፤ ምድርን ርቀን ጠልቀን ብንፈትሻትም ዉሃ፤ እንደምናገኝ ይገልፃሉ። ዉሃ መጠኑን ከጠበቀ ህይወት፤ ገደብ መጠኑን ሲያልፍ ጥፋት መሆኑን ለመረዳት የኖህን ዘመን ወደኋላ ሺ ዘመናት ርቆ በዓይነ ህሊና መዳሰስ ባለንበት ዘመን አስፈላጊ ከማይሆንበት ደረጃ የደረሰ ይመስላል። እንዴት ለሚል፤ የዛሬ ሰባት ዓመት ገደማ የሱናሚ ማዕበል በኢንዶኔዢያና ታይላንድ፤ የ230 ሺ ሰዉ ህይወት ሲያጠፋ፤ 110 ሺ ሰዎች ሲጎዳ፤ 1,7 ሚሊዮን ህዝብ መጠለያ ሲያሳጣ ታይቷል። በዓመቱ ካተሪና የሚል ስያሜ የተሰጣት ማዕበል የአሜሪካንን ግዛቶች መታ ለ1836 ሰዎች ህልፈት ምክንያት ስትሆን፤ ከ700 የምልቁትም የገቡበት እንዳልታወቀ ተሰምቷል።

USA Flash-Galerie Naturkatastrophen Katrina
ምስል AP

ከአንድ ዓመት ከስምንት ወር በፊት እንዲሁ ጃፓን ዉስጥ ሱናሚ የ12,690 ሰዎችን ህይወት ሲነጥቅ፤ 14, 700ዎች የደረሱበት መጥፋቱ ተዘግቧል። ይህ ማዕበል በወቅቱ እንደተሰማዉ 17,500 ኗሪዎች ካሏት አንዲት የወደብ ከተማ 10ሺዎቹን ጨርሷል። ሱናሚዉና ርዕደ መሬቱ ተባብረዉ የተነኮሱት የሀገሪቱ የኒኩሊለር ጣቢያ ከሚያስከትለዉ አደገኛ ጨረር ጋ ተዳምሮ 500 ሺህ ህዝብ ከአካባቢዉ ተፈናቅሏል። 400 ሺ ህዝብም አጥንት በሚነካ ጠንካራ ቅዝቃዜ ዉስጥ መጠለያ አጥቷል። የዉሃዉ ጥፋት በሰዎች ሳይገታ 117,570 ህንፃዎችን ከጥቅም ዉጪ ሲያደርግ በተለይ 14 ሺ ገደማ የሚሁኑትን ፈፅሞ አዉድሟል። ሰሞኑን ደግሞ ከካረቢያን አካባቢ ተነስታ የዩናይትድ ስቴትስ 15 ግዛቶች የገረፈችዉ ሳንዲ ማዕበል፤ ቀደም ብላ ጃማይካ፤ ሃይቲ፤ ዶሜኒካን ሪፑብሊክ፤ ኩባን የባሃማ ደሴቶችና አካባቢዉን አዳርሳ ቀላል የማይባል ጉዳት አስከትላለች። በዕርግጥ የግዙፏ ሀገር የአሜሪካ ጉዳት ጎልቶ ተወራ እንጂ ሳንዲ ጃማይካ ዉስጥ 70 በመቶ የሚሆነዉን ህዝብ ከኤሌክትሪክ አገልግሎት አሳጥታለች፤ በደሃዋ ሀገር የ55,23 ሚሊዮን ዶላር ኪሳራም አስከትላለች፤ ሃይቲ ላይ የ52 ሰዎች ህይወት ነጥቃ፤ 200 ሺዎችን መጠለያ አልባ ስታደርግ የምግብ እጥረትም ተከስቷል።  ኩባ 11 ሰዎችን ለሞት ዳርጋ 15 ሺህ ቤቶችን በማዉደም የ2 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ አስከትላለች። የአንድ መቶ ዘጠኞችን ህይወት አሜሪካና ካናዳ ላይ ያጠፋችዉ የሳንዲ ማዕበል በንብረት ላይ ያደረሰችዉ ጉዳት በገንዘብ ሲሰላ የኢትዮጵያ የአምስት ዓመት በጀት፤ አለያም በርከት ያሉ የህዳሴዉን ግንብ ያሠሩ እንደነበር ነዉ ካናዳ ካልጋሪ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ተፈጥሮ ላይ የሚያተኩረዉ ዘርፍ ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶክተር ጌታቸዉ አሰፋ የለፁልን። ሳንዲ ያደረሰችዉ ጉዳት ሳይጠገን አሁንም ቀጣይ ማዕበል ወደአሜሪካ መቃረቡን ነዉ የአየር ንብረት ትንበያዎች የሚያመለክቱት።

Sandy Schäden
ምስል Reuters

ሸዋዬ ለገሠ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ