1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፤ የኦሮሞና የአማራ ብሔሮች ግንኙነት

ነጋሽ መሐመድ
እሑድ፣ ኅዳር 3 2010

አንዳዶች የኦሮሞና የአማራ ሕዝብ ያሳያዉን ትብብር «ለመቀማት ያለመ» ሲሉት፤ ሌሎች ደግሞ ዉጪ በሚኖሩ የአማራና የኦሮሞ ልሒቃን መካካል የታየዉን መቀራረብ «ለመቅደም» የተዘጋጀ ነዉ ባዮች ነዉ።ሌሎች ባንፃሩ በገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ዉስጥ ከፍተኛ ጫና የሚያሳድረዉን ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሐትን) ለማግለል ያለመነዉ ባይ ናቸዉ

https://p.dw.com/p/2nQtA
12.06.2013 DW Online Karten Basis Äthiopien Englisch

ዉይይት፤ የኦሮሞና የአማራ ብሔሮች ግንኙነት

ጤና ይስጥልኝ እንደምን አመሻችሁ።ለዛሬዉ ዉይይታችን የአማራ እና የኦሮሞ ግንኙነት የሚል ጥቅል ርዕስ ሰጥተነዋል።ባለፈዉ ሳምንት ማብቂያ የኦሮሞ አባገዳዎች፤የኦሮሞ እና የአማራ የሐገር ሽማግሌዎች፤የኃይማኖት መሪዎች፤ ታዋቂ ግለሰቦች እና የሁለቱ መስተዳድሮች ከፍተኛ ባለሥልጣናት የተካፈሉበት የጋራ ሥብሰባ ባሕርዳር ዉስጥ ተደርጓል።«የአማራና የኦሮሞ የጋራ ምክክር መድረክ» ከተባለዉ  ስብሰባ እና ዉይይት በተጨማሪ በሁለቱ ሕዝቦች መካከል ቅራኔ ይፈጥራሉ የተባሉ ችግሮችን አስወግዶ የሁለቱን ሕዝቦች ነባር ወዳጅነት ለማጠናከር ይረዳሉ የተባሉ ጉብኝቶች፤ የባሕል ልዉዉጦች እና ዉይይቶች ተደርገዋል።የግንኙነቱን ደረጃና ወደፊት መደረግ የሚገባዉን ጉዳይ የቃኙ ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርበዋልም።

የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ሥልጣን ከያዘበት ከ1983 ወዲሕ የሁለቱ ብሔሮች ተወላጆች በዚሕ ደረጃ ዉይይት ሲያደርጉ ያሁኑ የመጀመሪያዉ ነዉ።ታዛቢዎች እንዳሉት በስብሰባዉ  የተነሱት ሐሳቦች ባለፉት 27 ዓመታት  ይሰበክ የነበረዉን አንዱ ብሔር ሌላዉን የመጨፍጨፍ፤የመርገጥ፤ መጨቆን፤ መግዛቱን ታሪክ የሚቃረን ነዉ።የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሠ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸዉ «ታሪክን በፕሮፓጋንዳ መሳሪያነት በመጠቀም የሁለቱን ሕዝቦች አንድነት ለማዳከም ለዓመታት የተሰራ...» በማለት የተናገሩትም የእስካሁኑን እዉነት ጠቋሚ ነዉ።

ስብሰባዉ ካለፈዉ ታሪክ በተጨማሪ ባለፉት 26 እና 27 ዓመታት በሁለቱ ብሔሮች ተወላጆች መካከል በየስፍራዉ ለተከሰቱ ደም አፋሳሽ ግጭቶች ምክንያት የሆኑ ችግሮችን ለማስወገድ መፍትሔ የጠቆመም መስሏል።ሁለቱ ብሔረሰቦች ለመቀራረብ ማሰብ፤መወያየት እና  መስማማታቸዉን ብዙ አስተያየት ሰጪዎች ደግፈዉታል።ይሁንና በተለይ የሁለቱ ክልልሎች መስተዳድሮች እስከ ዛሬ የትነበሩ የሚል ጥያቄ ማስነሳቱ አልቀረም።አንዳዶች አሁን ስብሰባ የተደረገዉ ባለፉት ሁለት ዓመታት መንግሥትን ለመቃወም አደባባይ የወጣዉ የኦሮሞና የአማራ ሕዝብ ያሳያዉን ትብብር እና ጥያቄ «ለመቀማት ያለመ» ሲሉት፤ ሌሎች ደግሞ በተለይ ዉጪ በሚኖሩ የአማራና የኦሮሞ ልሒቃን መካካል የታየዉን መቀራረብ «ለመቅደም» የተዘጋጀ ነዉ ባዮች ነዉ።ሌሎች ባንፃሩ በገዢዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ዉስጥ ከፍተኛ ጫና የሚያሳድረዉን ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሐትን) ለማግለል ያለመነዉ ባይ ናቸዉ።በዛሬዉ ዉይይታችን የስብሰባዉን ትክክለኛ ዓላማ፤ ዉጤቱን እና መልዕክቱን እንቃኛለን።

ነጋሽ መሐመድ

ማንተጋፍቶት ስለሺ