ዚምባቡዌ ከምርጫ በኋላ
ረቡዕ፣ ነሐሴ 1 2005
ባለፈዉ ሮብ ዚምባቡዌ ዉስጥ በተደረገዉ ምርጫ የተሸነፈዉ ንቅናቄ ለዴሞክራሲያዊ ለወጥ (MDC) የምርጫዉን ሒደትና ዉጤት በመቃወም ለፍርድ ቤት አቤት ብሏል።በፕሬዝዳታዊዉ ምርጫ የተሸነፉት ጠቅላይ ሚንስትር ሞርጋን ቻንግራይ እና ፓርቲያቸዉ አዲስ ምርጫ እንዲደረግ ይፈልጋሉ።ፍርድ ቤቱም ሆነ የአካባቢዉ መንግሥታትና ማሕበራት ግን (MDC)nö ፍላጎት የሚያሳካ ብይን መስጠታቸዉ ሲበዛ አጠራጣሪ ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ዳንኤል ፔልስ በዘገበዉ ላይ ተመስርቶ ያጠናቀረዉ ዘገባ አለን።
የዚምባቡዌ ብሔራዊ ምርጫ ኮሚሽን ባለፈዉ ቅዳሜ ይፋ ባደረገዉ ዉጤት መሠረት ጠቅላይ ሚንስትር ሞርጋን ቻንግራይ አይሸነፉ-ሽንፈት ነዉ የገጠማቸዉ።ፕሬዝዳት ሮበርት ሙጋቤ ሥልሳ-አንድ ከመቶ።ቻይንግራይ ሰላሳ-አራት።በምክር ቤት አባላት ምርጫም የዚምባቡዌ የረጅም ጊዜ ገዢ ፓርቲ ZANU-PF MDCን በሰፊ ልዩነት ነዉ-የዘረረዉ።
ከሁለት መቶ አስሩ የምክር ቤት መቀመጫ-የሙጋቤዉ ZANU-PF አንድ መቶ ሥልሳዉን ተቆጣጥሯል።MDC አርባ-ዘጠኝ።ጠቅላይ ሚንስትር ሞርጋን ቻግራይ ምርጫዉን ዉጤት ቅዳሜዉኑ ዉድቅ አድርገዉታል።
«MDC የሐምሌ ሰላሳ-አንዱን ምርጫ ሙሉ በሙሉ ዉቅድቅ አድርጎታል።ሀ.በሒደቱ፥ ለ.የተሐድሶ ለዉጥ ባለመደረጉ-ምክንያት።»
አሁን ደግሞ የMDC ሥራ-አስፈፃሚ ኤዲ ክሮስ እንደሚሉት ፓርቲያቸዉ «ተጭበርብሯል» የሚለዉ ምርጫ ዉጤት ተሰርዞ አዲስ ምርጫ እንዲጠራ በፍርድ ቤት ሊሟገት አቤት ብሏል።
«ፕሬዝዳንታዊዉን ምርጫም፥ ለምክር ቤት አባላት በብዙ ሥፍራ የተሰጠዉን ድምፅም በመቃወም ክስ መስርተናል።ይሕን የምናደርገዉ ትክክለኛ ብይን እናገኛለን ብለን አይደለም።ምክንያቱም ፍርድ ቤቶቹ ራሳቸዉ ከፍተኛ ተፅዕኖ ይደረግባቸዋልና።ይሁንና ሁሉንም ነገር በሕጋዊ መንገድ ለመረጃነት ለማስቀመጥ ነዉ።»
የMDC ሥሌት መረጃዎቹ ሕጋዊ መሠረት ካገኙ የዉጪ ሐይላት በተለይም የአፍሪቃ ሕብረት እና የደቡባዊ አፍሪቃ የልማት ማሕበረሰብ (SADC) በፕሬዝዳት ሙጋቤ ላይ ግፊት እንዲያደርጉ ይጠቅማሉ ነዉ።ከተሳካ አዲስ ምርጫ።የአካባቢዉ ሐገራት ግን GIGAበሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጣራዉ የጀርመን ጥናት ተቋም ባልደረባ ክርስቲያን ፎን ዞስት እንደሚሉት ዙምባቡዌ የዛሬ አምስት ዓመት ወደነበረበችበት ግጭት እንድትገባ አይፈልጉም።
«የአጎራባች ሐገራት ዓላማ የዚምባቡዌ ሠላም እንዳይታጎል ነዉ።ያሁኑ ምርጫ ስሕተት አለበት ከተባለ የሚኖረዉ አማራጭ አዲስ ምርጫ መጥራት ነዉ።መራጮች ተመዝግበዉ፥ ሁሉም ነገር እንዳዲስ ይደረግ ቢባል ሁከትና ምሥቅል ቅል መፈጠሩ አይቀርም።ይሕን ደግሞ የአካባቢዉ ሐገራት አይፈልጉትም።»
ከአምስት ዓመት በፊት በተደረገዉ ምርጫ ዉጤት ሰበብ የተጫረዉ ግጭት እዚያዉ ዚምባቢዌ ዉስጥ ከሁለት መቶ በላይ ሕይወት አጥፍቷል።ግጭቱን ሽሽት ወደ ደቡብ አፍሪቃ የተሰደዱት ሰወስት ሚሊዮን ሕዝብ ደግሞ ከደቡብ አፍሪቃዉያኑ ጋር ተጋጭቶ በርካታ ሰዎች ተገድለዋል።
የMDC ሥራ አስፈፃሚ ኤዲ ክሮስ ፓርቲያችን «ያለፈዉ አይነት ግጭት፥ ወይም የአረብ ሐገራት አይነት ሕዝባዊ አመፅም አይፈልግም ባይ ናቸዉ።
«በየትኛዉም መንገድ ቢሆን ሕዝባዊ ንቅናቄ እንዲኖር አንፈልግም።ይሕን የማንፈልግበት ምክንያት ፀጥታ አስከባሪዎች ሕዝባዊ ንናቄዉን ለመደፍለቅ በኛ ላይ ጠንካራ የሐይል እርምጃ እንደሚወስዱ ሥለምናዉቅ ነዉ።ሕዝባችንን ለዲሕ አይነቱ የግፍ እርምጃ ማጋለጥ አንፈልግም።»
የሮቡ የድምፅ አሰጣጥ ሒደት እብዙ ሥፍራ መሳካር ታይቶበታል።አንዳድ ዘገቦች እንደጠቆሙት ደግሞ ድምፅ ለመስጠት ከተመዘገበዉ ሕዝብ በሰላሳ-አምስት ከመቶ የሚበልጥ ካርድ ታትሞም ነበር።የአፍሪቃ ሕብረት ታዛቢዎች ለችግሩ እንግዳ አይደሉም።የታዛቢዉ ቡድን መሪ የቀድሞዉ የናይጄሪያ ፕሬዝዳት ኦሌሴጎን ኦባሳንጆ ግን ችግሮቹን «ጥቃቅን» በማለት ነዉ-ያለፏቸዉ።አጠቃላይ ሒደቱንም «ነፃና ፍትሐዊ» ብለዉታል።የሳዴክ የታዛቢዎች ቡድንም ምርጫዉን «ነፃና ሠላማዊ» ነዉ-ያለዉ።
ዩናይትድ ስቴትስ፥ ብሪታንያና ጀርመን ግን የምርጫዉን ሒደትና ዉጤት አሳሳቢ ብለዉታል። ያለፈዉን ይደገማል ብለዉ የሚፈሩት አፍሪቃዉያኑ ግን ጉዳዩን በጥንቃቄ መያዙን ነዉ-የመረጡት።
ነጋሽ መሐመድ
ሸዋዬ ለገሠ