በየመን ሰንዓ እስር ቤት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የድረሱልን ጥሪ
ሰኞ፣ ጥቅምት 3 2012ከ 800 በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያዉያን ወደ ሀገራቸዉ ኢትዮጵያ ለመመለስ የዓለም አቀፍን የፍልሰተኞች መርጃ ድርጅት «IOM» ርዳታ እየጠበቅን ነዉ ሲሉ ከየመን መዲና ሰንዓ ጥሪ አሰሙ። ስደተኞቹ እንደተናገሩት ዓለም አቀፉ የፍልሰተኞች መርጃ ድርጅት «IOM» ይወስደናል ብለዉ በዝያዉ ባሉበት እስር ቤት ሲጠባበቁ ዘጠኝ ወርና ከዚያ በላይ ሆንዋቸዋል።
ኢትዮጵያውያኑ በየመን ለእስር የተዳረጉት በየመን ባሕር በር በኩል በሕገ-ወጥ መንገድ ወደ የመን ለመግባት ሲሞክሩ በፀጥታ ኃይላት ከተያዙ በኋላ ነዉ። «IOM» ስደተኞቹ ከታጎሩበት እስር ቤት በየሁለት ወሩ እየመጣ የተወሰኑ ስደተኞችን ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ ቢያደርግም ድርጅቱ ላለፉት ዘጠኝ ወራት ሰንዓ ከሚገኘዉ የኢሚግሬሽን እስር ቤት አንድም ኢትዮጵያዊ ወስዶ እንደማያዉቅ ኢትዮጵያዉያኑ ተናግረዋል።
ከ10 ዓመታት በላይ በሰንዓ የምትኖረዉ ኢትዮጵያዊት ሰብለ ዮሐንስ ባለቤትን ለመጠየቅ ሰነዓ ከተማ አለ በተባለዉ የኢሜግሬሽን እስር ቤት በሄደችበት ሰአት ስልክ ደዉለን አነጋግረናታል። ሰብለ፤ የኢሚግሬሽን እስር ቤት በሚባለዉ ቦታ ወደ ስምንት መቶ ኢትዮጵያዉያን እንደሚገኙ በመናገር ትጀምራለች። በሰንዓ እስር ቤት የሚገኝ አንድ ኢትዮጵያዊ በበኩሉ መንግሥት ወደ ሀገራችን ይመልሰን በማለት ተማፅኗል።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ