1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሊቢያው መሪ የፈረንሣይ ጉብኝት

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 1 2000

ኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊ፤የኑክሊየር ኃይል ባለቤት ለመሆን ባላቸው ፅኑ ፍላጎት እና አሸባሪነትን አስመልክቶ በያዙት አቓም፤በብዙዎቹ ምዕራባዊያን አገራት ዘንድ በመልካም አይነሱም።ሆኖም በፈረንሣዩ ፕሬዚዳንት ኒኮላስ ሳርኮዚ የጉብኝት ጥሪ መሰረት ግን ከሰኞ ህዳር ሰላሳ አንስቶ ፓሪስ ተገኝተዋል።

https://p.dw.com/p/E87L
ሣርኮዚና ጋዳፊ የሆድ የሆዳቸውን...
ሣርኮዚና ጋዳፊ የሆድ የሆዳቸውን...ምስል AP

ሊቢያ እ.ኤ.አ. በሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ስምንት ዓ.ም. ሎከርቢ፤ስኮትላንድ ላይ በቦምብ በጋየው የፓናማ ጃምቦ የመንገደኞች ጀት ምክንያት በተባበሩት መንግስታት ማዕቀብ ተጥሎባት ቆይታለች።ሆኖም እ.ኤ.አ. በሁለት ሺህ ሶስት ዓ.ም. የአደጋውን ሀላፊነት ከወሠደችና አሸባሪነትን በይፋ ካወገዘች በኃላ ግን ማዕቀቡ ተነስቶላታል።እንዲያም ሆኖ ታዲያ ፕሬዚዳንቷ ኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊ የኒኩሊየር ኃይል ባለቤት የመሆን ፅኑ ፍላጎታቸውና አሁንም ድረስ አሸባሪነትን አስመልክቶ የያዙት አቓም አስተማማኝ ባለመሆኑ በበርካቶቹ የምዕራባውያን አገራት ዘንድ በመልካም አይነሱም።

የሊቢያና የፈረንሳይ ግንኙነት መጠናከር የጀመረው እ.ኤ.አ. በሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ዘጠኝ ዓ.ም.ነው።ያኔ ኒጀር ላይ ተተኩሶበት የተከሰከሰውን የፈረንሣይ አውሮፕላን አስመልክቶ ሊቢያ ኃላፊነቱን ከወሠደች እና ለተጎጂዎችም ካሣ ከከፈለች በኃላ ማለት ነው።የሁለቱ አገራት ፕሬዚዳንቶች፤የአፍሪቃዊው ሙአመር ጋዳፊና አውሮጳዊው ኒኮላስ ሳርኮዚ ወዳጅነት በቡልጋሪያዊያኑ ነርሶች ስህተት ደግሞ የበለጠ ተጠናክሯል።ቡልጋሪያውያኑ ነርሶች ሊቢያውያን ህፃናቱን በ HIV ቫይረስ ሆን ብለው እንዲያዙ አድርገዋል በሚል ክስ የሞት ፍርድ ባስጨነቃቸው ሰሞን።

ያኔ ፈረንሳዊው ፕሬዚዳንት ሣርኮዚ የቀድሞው ባለቤታቸው ሴሲሊያን ለድርድር ወደ ሊቢያ በመላክ መላውን አውሮጳ ግራ አጋብተዋል፣አስደንቀዋልም።ሆኖም ሣርኮዚ ገና የፕሬዚዳንትነት ሹመትን በተቀዳጁ ሰሞን የፈፀሙት ተግባር ግን ከሊቢያ ጋር ከፍተኛ ወዳጅነትን አትርፎላቸዋል።ምናልባትም ሰሞኑን የኒኩሊየር ቴክኖሎጂ እና ግዙፉ ኤይርባስ አውሮፕላንን የሚመለከት የሶስት ቢሊዮን ዩሮ ስምምነት ሣርኮዚ ኮሎኔል ጋዳፊን ያስፈርሟቸዋል ተብሎም ይጠበቃል።