1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሌጎስ ጎስቋላ ሰፈር ነዋሪዎች ድል

ቅዳሜ፣ ሰኔ 17 2009

በአፍሪቃ ብዙ የአዳጊ ሀገራት መንግሥታት ካለ እቅድ ፈጥነው በማደግና በመስፋፋት ላይ ያሉ ከተሞቻቸውን ዘመናይ ለማድረግ ሲሞክሩ ይታያል። ፈጣን እድገት ከሚታይባቸው ከተሞች መካከል  የናይጀሪያ ከተማ ሌጎስ አንዷ ናት። የሌጎስ ከተማ አስተዳደር ባለስልጣናት ወደ 20 ሚልዮን የሚጠጋ ሰው የሚኖርባትን ከተማ ለማዘመንና ባለወረቶችን ለመሳብ ይፈልጋሉ።

https://p.dw.com/p/2fIHZ
Nigeria schwimmender Slum in Lagos
ምስል picture-alliance/AA/ABACAPRES.COM/M. Elshamy

lagos - MP3-Stereo

ይህን ዓላማቸውን ከግብ ለማድረስም በብዙኃኑ የከተማይቱ ነዋሪዎች፣ ብሎም በድሆቹ  አንጻር  ይሉኝታ የሌለው የጭካኔ ተግባር ይፈጽማሉ። የሌጎስ ከተማ አስተዳደር ከተማይቱን በዘመናይ መንገድ ለማልማት እና ለማሻሻል  በወጠነው እቅዱ መሰረት፣ ካለፈው ኅዳር ወር ወዲህ የጀመረውን የከተማይቱን ጎስቋላ ሰፈሮች ማፈራረስ ርምጃው፣  ባለፈው መጋቢት እና ሚያዝያም በፖሊስ የተረዱትን አፍራሽ ግብረ ኃይሎቹን ወደ አካባቢው በመላክ ካላንዳች ቅድመ ማስጠንቀቂያ የድሆቹን መኖሪያ ቤቶች በእሳት አጋይተው ብዙዎቹንም ካላንዳች መጠለያ ማስቀረታቸው ይታወሳል። አካባቢውን በፈቃደኝነት መልቀቅ ያልፈለጉት ነዋሪዎች በአፍራሽ ግብረ ኃይሎቹ በግዳጅ ተባረዋል። ነዋሪዎቹ በዚሁ የከተማይቱ አስተዳደር ርምጃ በዛም አነሰ የነበረቻውን ሁሉ አጥተዋል። ኪርስቲኑ ግቤኑ እና እናቷ በዚሁ ርምጃ ብቸኛ የገቢ ምንጭ ሆኖ ሲያገለግል የቆየውን ንዑሱን መደብራቸውን አጥተዋል። ክሪስቲኑ ግቤኑ ሁኔታው እንዴት እንደሚቀጥል አታውቅም፣  ዘመዶችዋ ለጊዜው በሚኖሩበት ጀልባ አስጠግተዋታል። «ስራ የለኝም። እድሜ ለጎረቤቶቻችን ርዳታ እንደምንም መኖር ችለናል።»

ክሪስቲኑ ግቤኑ እና ቤተሰቧ ከብዙ አሰርተ ዓመታት ወዲህ በዚሁ በኦቶዶ ግባሜ ሰፈር ይኖራሉ። ይኸው በከፊል በዉኃ ላይ የቆመው ጎስቋላ ሰፈር አመቺ በሚባል አካባቢ፣ ማለትም፣ ሌኪ በተባለው የሀብታሞች  ሰፈር አቅራቢያ ነው የሚገኘው። በብዛት ጥሩ ደሞዝ የሚያገኙ ሰዎች የሚኖሩበት ይኸው አካባቢ ካለፉት ጥቂት ጊዜያት ወዲህ እንደ አማላይ ሰፈር ተፈላጊነቱ ከፍ እያለ ሄዷል። ለዚህም በማልማቱ ስራ የሚሰማሩትን እና የከተማይቱን አስተዳደር ኃላፊዎች ተጠያቂ ናቸው ሲሉ ወቀሳ አሰምተዋል።
« ያካባቢው መንግሥት እንደሆን ለኛ ደንታ የለውም። ምርጫ በሚካሄድበት ጊዜ ብቻ ፣ ድምፃችን ስላስፈለጋቸው፣ ወደዚህ መጥተው ነበር። አሁን ከተመረጡ በኋላ ግን መኖሪያ ቤቶቸንን በእሳት አጋይተውታል።  ኅልውናችንን ለማረጋገጥም ሆነ ለደህንነታችን አንድም የሚያደርጉልን ነገር የለም። »
የከተማይቱ አስተዳደር አንድ የሌጎስ ፍርድ ቤት የኦቶዶ ግባሜ ጎስቋላ ሰፈር እንዳይፈርስ ቀደም ሲል ያስተላለፈውን ትዕዛዝ በመጣስ ነበር  ይህን ርምጃ የወሰደው።  የጎስቋላው ሰፈር ነዋሪዎች ርምጃው ሕገ ወጥ ነው ፣ አስተዳደሩም ቹ በከተማይቱ አስተዳደር ላይ ክስ መስርተዋል።  የኦቶዶ ግባሜን ነዋሪዎች ክስ  ባለፈው ረቡዕ ባካሄደው ችሎት  ያዳመጠው ፍርድ ቤት፣ የሌጎስ መንግሥት አስተዳደር ነዋሪዎቹ የሰፈሩበትን ቦታ በሕገ ወጥ መንገድ ነው የያዙት፣ ይህም በፀጥታ አጠባበቁ እና በተፈጥሮ አካባቢ ላይ ስጋት ይደቅናል በሚል ያቀረበውን መከራከሪያ ሀሳብ ውድቅ በማድረግ፣ ያካባቢው መንግሥት ርምጃ የነዋሪዎቹን ሰብዓዊ መብት የጣሰ ነው በማለት፣ ካሳ እንዲሰጣቸው ብይን አሳልፏል። ኪርስቲኑ ግቤኑ እና የኦቶዶ ነዋሪዎች   በብይኑ ደስታ እንደተሰማቸው በመግለጽ የፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ተግባራዊ የሚሆንበትን ቀን በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።

Nigeria schwimmender Slum in Lagos
ምስል picture-alliance/Anadolu Agency/M. Elshamy

« አሁን አንድ ነገር ነው የምፈልገው፤ ይኸውም ከነልጆቼ  ወደ ኦቶዶ ግባሜ መመለስ ነው። » የኦቶዶ ግባሜ ነዋሪዎች ጠበቃ ኦማታዮ ኤኑጂውጋም የደንበኞቻቸውን መብት ለማስጠበቅ እንደሚሰሩ ገልጸዋል። « ከመንግሥት ጋር ጠቃሚ ድርድር ማካሄድ ከተሳካልን የኦቶዶ ግባሜ ነዋሪዎችን መብት ማስከበር የምንችልበት መፍትሄ ልናገኝ ይገባል።» ይህ መፍትሄ እንስኪገኝ ድረስ ግን ኪርስቲኑ ግቤናን የመሳሰሉት የመንግሥት ርምጃ ሰለባዎች የሆኑት  መጠለያ አልባ የቀሩት የኦቶዶ ግባሜ ሰፈር ነዋሪዎች በየዘመዶቻቸው ቤት ተጠግተው መኖር ይገደዳሉ።

አርያም ተክሌ

ማንተጋፍቶት ስለሺ