1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሔይቲ አደጋና የዩናይትድ ስቴትስ ርዳታ

ዓርብ፣ ጥር 21 2002

ዩናይትድ ስቴትስ ግን አምሳያዋ ለመሆን የምትዳክረዉን የትንሽ ጎረቤትዋን ነፃ ሐገርነት ለማወቅ ሐምሳ-ስምት አመታት ቆይታለች።ከዚያ በሕዋላ የአለም ትልቋ ሐብታም ሐገር የምዕራቡ አለም ያጣች-የነጣች ትንሽ ጎረቤቷን ከድህነት አረንቋ ለማዉጣት ብዙ አስታዉሳት አታዉቅም።

https://p.dw.com/p/Lj41
ቁስለኛዉምስል AP

28 01 10

ሔይቲን በመታዉ የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ የሞተዉ ሕዝብ በፊት ከተገመተዉ መብለጡ እንደማይቀር የፈራረሰዉ የሐገሪቱ መንግሥትና የርዳታ ሠራተኞች አስታወቁ።የሐገሪቱ ፕሬዝዳት ሬኔ ፕሬቫል እንዳስታወቁት እስከ ትናንት ድረስ 170 ሺሕ አስከሬን ተገኝቷል።ትናንትናዉኑ አዲት ወጣት ከፍርስራሽ ሥር በሕይወት ወጥታለች።በአደጋዉ የተጎዳዉን ሕዝብ ለመርዳታ እና የወደመችዉን ሐገር መልሶ ለመጠገን ከመላዉ አለም የሚሰጠዉ ድጋፍ እየጎረፈ ነዉ።ርዳታ ከመላክ ፀጥታ እስከ ማስከበር ባለዉ ሒደት ግን ዩናይትድ ስቴትስን የተስተካከለ ሐገር የለም።ዳንኤል ሼሽክቪትስ እንደዘገበዉ ዩናይትድ ስቴትስ የሔይቲን ለመርዳት ቀድማ የደረሰችበት ምክንያት ብዙ ነዉ።

ዛሬም-አስከሬን ይሠተራል።ይቀበራል።ቁስለኛ ይታከም-ይቆጠራል።ፍርስራሽ፥ ሥብርባሪ ይጠረጋል። እሕል-ዉሐ፥ ቤት-ታዛ አልባዉ ይሰላል።ቀኑም እንዲሁ።አስራ-ስድስት አለ።ዛሬ።ትናንት በአስራ-አምስተኛ ቀኑ አንዲት የአሥራ-ስድስት አመት ወጣት በሕይወት መገኘቷ እንባ በሚያራጨዉ እልቂት መሐል-አጃኢብ አሰኝቷል።

የርዳታ ብዛትም በርግጥ አስደናቂ ነዉ።ከአፍሪቃ እስከ አዉስትሬሊያ፥ ከእስራኤል እስከ ቻይና፥ ቃል-ያልገባ-የርዳታ እጁን ያልዘረጋ የለም።ከወታደር እስከ ሐኪም፥ ከአስከሬን ፈላጊ-፥እስከ ድምፃዊ-ያልዘመተ፥ያልተረባረበ ጥቂት ነዉ።ግን ማን እንደ ዩናይትድ ስቴትስ።ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ ጊዜ አላጠፉም።

«ይሕን ያሕል መጠን ያለዉ አደጋ ያደረሰዉን ጥፋት ለመቋቋም የብሔራዊ አቅማችንን ሁለተናዊ አላባ ይጠይቃል።ዲፕሎማሲያችንን፥ የልማት ርዳታችንን፥ የጦር ሐይላችንን፥ ከሁሉም በላይ የሐገራችንን ፍቅር---»

ኦባማ በሰአታት ልዩነት ሐገራቸዉ አንድ መቶ ሚሊዮን ዶላር እንደምትረዳ ቃል ገቡ።ዩናይትድ ስቴትስ ሔይቲን ከሁሉ ቀድማ፥ አብልጣም የምትረዳበት ምክንያት ከሰብአዊነትም በላይ ታሪካዊ፥ ፖለቲካዊ፥ መልከዓ ምድራዊ፥ ማሕበራዊዉ ምክንያት አላት።ሔይቱ እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ አቆጣጠር በ1804 ከፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ ነፃ እንደወጣች የአስተዳደር ሥርዓት-የግዛት መዋቅሯን በዩናይትድ ስቴትስ አምሳያ ነበር የመሠረተችዉ።

US Militär Flughafen Haiti Port au Prince
የአሜሪካ የርዳታ ሔሊኮብተርምስል AP

ዩናይትድ ስቴትስ ግን አምሳያዋ ለመሆን የምትዳክረዉን የትንሽ ጎረቤትዋን ነፃ ሐገርነት ለማወቅ ሐምሳ-ስምት አመታት ቆይታለች።ከዚያ በሕዋላ የአለም ትልቋ ሐብታም ሐገር የምዕራቡ አለም ያጣች-የነጣች ትንሽ ጎረቤቷን ከድህነት አረንቋ ለማዉጣት ብዙ አስታዉሳት አታዉቅም።

መከራ ሲወድቅባት ግን አልተለየቻትም።ዩናይትድ ስቴትስ ወደ ሐይቲ ከምግብ-ቁሳቁስ ርዳታ አልፋ ጦር ሥታዘምት ሃያ-አመት ባልሞላ ጊዜ ዉስጥ ያሁኑ ሰወስተኛዋ ነዉ።እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ አቆጣጠር-በ1994 የጦር ጄኔራሎች የያኔዉን ፕሬዝዳት ዦን ቤርትራድ አርስቲዲን ከስልጣን ሲያስወግዱ-የአሜሪካ ባሕር ሐይል ባፍታ ፖርቶ ኦ ፕረስ ደረሰ።

«ትልቁ የጦር ጓድ፥ የባሕር ሐይል ፖርት ኦ ፕረንስ እየደረሰ ነዉ----»

ዩናይትድ ስቴትስ በጦር ጡንቻ፥ በዲፕሎማሲም ዳግም ወደ ስልጣን የሰቀለቻቸዉ አርስቲድ ሥልጣን በያዙ ባስረኛ አመታቸዉ ሙስናን ለማስወገድ፥ አመፅ ሁከትን ለመቆጣጠር አመራር-ብልሐቱ ጠፍቷቸዉ ግራ-ቀኝ ሲላጉ ዩናይትድ ስቴትስ ከሥልጣም ከሐገርም ለማስለቀቅ ሌላ ጦር አዘመተች።2004።ዘንድሮ ደግሞ ርዳታ-ፀጥታ ጠባቂ አስራ-ሺሕ ጦር አሠፈረች።
ዩናይትድ ስቴትስ የሄይቲ መስቅልቅል ካየለ ፍሎሪዳን የመሳሰሉት የካረቢክ አዋሳኝ ግዛቶቿ በስደተኞች ይጠለቀለቃሉ ብላ ትሰጋለች።የዋሽንግተን ባለሥልጣናት ድሕነት፥ ሥራ አጥነት፥ ተስፋ መቁረጥ ሔይቲን የወሮበሎችና የአደንዛዥ ዕፅ አዘዋዋሪዎች መናኸሪያነት ከቀየሯት መዘዙ ለሐገራቸዉ እንደሚተርፍ ያዉቃሉ።

Haiti nach dem Erdbeben
የአሜሪካ ጦር ፖርቶ ፕረስምስል AP

አዉሮጶች፥አሁን ደግሞ ብራዚል እና ቻይና አፍንጫዋ ሥር ባንዲራቸዉን ሲተክሉ የግዙፊቱ ሐገር ተፅዕኖ መሸራረፉ አይቀርም።ይሕ እንዲሆን ዋሽንግተን አትፈቅድም።የፕሬዝዳት ኦባማ መስተዳር ደግሞ ጀርመናዊዉ የደቡብ አሜሪካ አዋቂ ኦሊቨር ግሊይሽ እንደሚሉት ተጨማሪ ምክንያትም አለዉ።

«የመጀመሪያዉ በርግጥ የፕሬዝዳት ኦባማ መንግሥት ዉሳኔ ሰባዊነትን አመልካች ነዉ።አብሮም የመራጮች ጉዳይ አለ።በሁለት ሺሕ አምስት ሉዊዚያና በጎርፍ በተጥለቀለችበት ወቅት በቡሽ (መስተዳድር) ላይ የተሰነዘረዉ ወቀሳ መዘንጋት የለበትም።የያኔዉ አደጋ አብዛኞቹ ሠለቦች ያሁንን ፕሬዝዳት የመረጡት ወገኖች የሆኑ ጥቁሮች ናቸዉ።»

ዩናይትድ ስቴትስ አደጋዉ ከመድረሱ በፊትም አለም አቀፉ የገዘብ ድርጅት አይ ኤም ኤፍ ለሔይቱ ጠቀም ያለ ድጋፍ እንዲሰጥ ከፍተኛ ግፊት ሥታደርግ ነበር። የ1.2 ቢሊዮን ዶላር እዳም ሰርዛላታለች።

ዳንኤል ሸሽከቪትዝ/ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ