1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመማርና ማስተማር ሁኔታ በኦሮሚያ 

Merga Yonas Bula
ሐሙስ፣ መጋቢት 20 2010

በኢትዮጵያ በተለይም በኦሮሚያ ክልል በፖለቲካ ቀውስ ምክንያት የትምህርት ሕደቱ መስተጓጎሉን ከዚሕ ቀደም ዘግበን ነበር። አሁንም በተለያዩ አካባቢዎች ከአንደኛ እስከ ከፍተኛ ደረጃ ያሉት የትምህርት ተቋማት በየጊዜዉ ትምሕርት እንደሚቋረጥ እየተነገረ ነዉ።

https://p.dw.com/p/2v988
Äthiopien Geschäfte streiken wegen Steuergesetz in Oromiya (Ambo)
ምስል DW/Y. Geberegziabeher

Teachig, Learning Situation in Oromia - MP3-Stereo

በሃሮማያ ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት ግን ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ አስተያየት ሰጪ «ያለዉ ሁኔታ ጥሩ አይደለም» ይላሉ። የሃሮማያ ዩኒቬርስቲ ተማሪዎች የተሰጣቸዉን የአምስት ቀን እረፍት ጨርሰዉ እንደተመለሱ፣ የምዝገባ ማለቂያ ቀን ባለፈዉ አርብ እንደነበር  መምህሩ ይናገራሉ።

ከሰኞ ጀምሮ ትምህርት ይጀመራል ቢባልም እስካሁን ትምህርት እንዳልተጀመረ ገልጸዋል ። መምሕሩ ዩኒቨርስቲዉ ግቢ የሰፈረዉ  የፀጥታ ኃይል  እየወሰደ ነዉ ያሉትን ርምጃ እንዲህ ያስረዳሉ፣ «ለአሁኑ የማስተማር መማር ሂደት ቆሞ ነዉ ያለዉ። ግቢዉ ዝግ ነዉ። ሰዉ እንደልቡ ወቶ መግባት አይችልም። በትንሹ 12 ተማርዎች ምዝገባ ተመዝግቦ፣ ትምህርት እስከጀመር ብሎ ወደ ቤቴሰብ እየተመለሱ ሳሉ ታስረዉ የት እንደገቡ አይታወቅም። የዩኒቬርስቲዉ አስተዳደሮችም ሆነ ቤቴሰቦቻቸዉ የታሰሩት የት እንዳሉ አያዉቁም። በግቢ ዉስጥ ያሉት ተማሪዎች የታሰሩት እስኪ ፈቱ ድረስ ትምህርት አንጀምርም ብለዉ አቋም ይዘዋል። አጋዚ የተባለዉ (ጦር ኃይል ወታደሮች) ተማሪዎችን ክፍል ግቡ፥ እያሉ በየዶርሙ እየሄዱ  እየደበደቡ ናቸዉ። ለምሳሌ ከትላንት በስትያ የሴቶች ዶርም በመሄድ ተመሳሳይ ርምጃ ሊወስዱ ሲሉ ተማሪዎቹ በራቸዉን ዘግተዋል።»

ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ገበታቸዉ የመመለስ ፍላጎት ያለዉ የዩኒቨርስቲዉ አስተዳደር ቢሆንም የአስተዳዳሪዎቹ አባላት ወደ ግቢ እንዳይገቡ መከልከላቸዉን እንደሰሙ እኚሁ መምህር ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።

በአምቦ ዩኒቬርሲቲ ተማሪ የሆነዉ እና  እሱም ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ፤ ተማሪዎች ከእረፍት መልስ ምዝገባ ጨርሰዉ ግን እስካሁን ትምህርት ሳይጀመር ሁለኛ ሳምንቱን መያዙን ያስረዳል።

የሃሮማያ ዩኒቨርሲቲ መምህሩ እንደሚሉት በሥነ-ትምህርቱ ደንብ መሰረት ክፍል የሚገኙት ተማሪዎች ካጠቃላይ ቁጥራቸዉ ከግማሽ ካነሱ መምሕራን ትምሕርት መስጠት የለባቸዉም። መምህሩ: «እኛንም መምህራንን ግቡ እያሉ ኢያስፈራሩን ነዉ። በቅርቡ በኢንግሊዘኛ እና  በአማርኛ ማስታወቂያ አዉጥተዋል። በዚህም ማስታወቅያ ክፍል ያልገባ መምህር የኛ መምህር ስላልሆነ እናባርራለን የሚል ይዘት አለዉ። መምህራኑም ወደ የክፍሉ ቢሄዱም ተማሪዎች ስለሌሉ የመማርና ማስተማር ሂደቱ አልተጀመረም።»

አዳማ ዉስጥ  ከአንደኛ እስከ ከፍተኛ ደረጃ የሚማሩ ተማርዎች ሙሉ በሙሉ ወደ ትምህርት ገበታቸዉ እንዳልተመለሱ፣ ብዙም ተነሳሽነት እንደሌላቸዉ አንድ ስማቸዉ ለደህንነታቸዉ ሲባል እንዳይጠቀስ የፈለጉ የከተማዋ ነዋሪ ይናገራሉ። ተማሪዎች ወደ ትምሕርት ገበታቸዉ እንዳይመለሱ የሚጠይቅ  በራሪ ወረቀት እንደሚበተንም ግለሰቡ አክሎበታል። የወረቀቱ ይዘት በተመለከተ እንዲህ ያስረዳሉ፣ «አገሪቱ ዉስጥ ባለዉ ሁኔታ ጋር ተያይዞ፣ አንድ፣ ያለ ሕዝቡ ፍላጎት ለሁለተኛ ዙር የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁና ክልሉ በወታደራዊ ኃይል እንዲተዳደር  መደረጉ፣ አዋጁንም ለማሳለፍ በፓርላማ ድምጽ ስለተጨበርበረ፣ አዋጁ እስኪነሳ ድረስ ወደ ትምህርት መመለስ የለባቸሁም፣ ጫና፣ ተቃዉሞ ማድረግ አለባቸሁ የሚል ነዉ»።

በሐገሪቱ ብሎም በክልሉ ያለዉን የመማር ማስተማር ሂደት፣ እንዲሁም ግለሰቦቹ ያነሰዋቸዉ ጉዳዩች ላይ ማብራርያ እንዲሰጡን የትምህርት ሚኒስቴር ባለሥልጣናትን ብንጠይቅም መልስ መስጠት እንደማይችሉ ተናግረዋል።

መርጋ ዮናስ

ነጋሽ መሐመድ