1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመን እና ሽብርተኝነት

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 27 2002

አንድ የመንገደኞች ማመላለሻ አይሮፕላን ዲትሮይት ሊያርፍ ሲል ሊጣልበት የነበረው ጥቃት የከሸፈበት ድርጊት የመን እንደ አሸባሪዎች መናኸሪያ እንድትታይ ምክንያት ሆኖዋል። ይሁንና፡ የዶይቸ ቬለው ፔተር ፊሊፕ እንደሚለው፡ ያን ያህል ያልተረጋጋችው የመን ይህንኑ ሚና ዛሬ ሳይሆን ከብዙ ጊዜ ወዲህ ስትጫወት ቆይታለች።

https://p.dw.com/p/LLNi
የየመን ፕሬዚደንት አሊ አብዱላ ሳሌህምስል picture-alliance/ dpa


የመን በሽብርተኝነት አንጻር ሁነኛ ርምጃ ለመውሰድ ቆርጣ መነሳትዋን ለማረጋገጥ ስትል ለጎብኚዎች ጸረ ሽብርተኝነት ስልጠና ሲደረግ ታሳያለች። ለጎብኚዎች የማታሳየው ጉዳይ ቢኖር ግን ይህንን ስልጠና የሚሰጡት አሜሪካውያን ጠበብት መሆናቸውን ነው። የመን የአል ቓይዳ ደጋፊዎች መናኸሪያ እየሆነች በመምጣትዋ አሜሪካውያኑ የጦር አሰልጣኖች ካለፉት ዓመታት ወዲህ በዚችው ሀገር ተሰማርተዋል። አሸባሪዎች ግፊት እየበዛባቸው በሄደ ቁጥር ፊታቸውን ለመንቀሳቀስ አማላይ ሆና ወዳገኙዋት ወደ የመን አዙረዋል።
የሀገሪቱ ውስጣዊ ችግር ህዝቡ ከሚገኝበት ከከፋው ድህነት፡ ከዝቅተኛው የትምህርት ደረጃ፡ ከኋላ ቀርነት እና ስር ከሰደደው ባህላዊና ሀይማኖታዊ ልማድ ጋር ባንድነት ተዳብሎ የመንን እክሽፈት አፋፍ ላይ ላይ ጥሎታል። ልክ በአንድ ወቅት አፍጋኒስታን እንደበረችው።
ይህ ሁኔታ በየመን አሁን የቀረውን የመንግስት ቁጥጥር ሊያጠፉ ለሚችሉ አሸባሪ ቡድኖች አማላዩን ሁኔታ የፈጠረው። ከዚህ በተጨማሪም የየመን መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፡ ማለትም ቀንደኛው የአል ቓይዳ መሰረት ከሚገኝባት ከሳውዲ ዓረቢያ ጋር መዋሰን፡ ከሶማልያና ከምስራቅ አፍሪቃ አለመራውና በዋነኞቹ የባህር መተላለፊያዎች መገኘቱ ትልቅ ትርጓሜ እንድትይዝ አድርጓል። በዚህም የተነሳ ሁነኛ እንቅስቃሴ ማድረጉ አስፈላጊ ይሆናል፥ እንደ የየመንዋ የዩኤስ አሜሪካ አምባሳደር ባርባር ቦድን አስተያየት።
« ጉዳዩ እኛ የመንን እንደከሸፈች ወይም በመክሸፍ ላይ እንዳለች ሀገር መቁጠር የለብንም። ነገር ግን የተሳሳተውን አቅጣጫ እንዳትይዝ ምን ማድረግ እንደምንችል መመልከት ይሆናል።
ይሁንና፡ ምንም እንኳን የመን ያልሆነ አቅጣጫ መያዝዋ ገና ከመስከረም አንዱ የአሸባሪዎች ጥቃት በፊት ቢታወቅም፡ ዋሽንግተን እና ተጓዳኞችዋ በዚሁ ረገድ የወሰዱት ርምጃ በጣም ጥቂት ነበር። እአአ በ 2000 ዓም በዩኤስኤስ ኮል የጦር መርከብ ላይ በተጣለ የአጥፍቶ ጠፊ ጥቃት አስራ ሰባት አሜሪካውያን መገደላቸው ይታወሳል። በርካታ የውጭ ዜጎችም ከማዕከላዩ መንግስት የሆነ ነገር ለማግኘት እየተባለ ሲታገቱና ሲፈቱ ታይቶዋል። እርግጥ፡ የጥቃቱን ጠንሳሾች ለመያዝ ጥረትዋን ብትቀጥልም፡ የመን ወደክሽፈቱ አፋፍ ማምራት የያዘችበትን ሁኔታያን ያህል ትኩረት አልሰጠችውም። ትኩረትዋ ያረፈው በኢራቅ፡ አፍጋኒስታን እና በፓኪስታን ነው። በተለይ፡ በጉዋንታናሞ ወህኒ ቤት የነበሩ የነበሩ የየመን ዜጎች ወደሀገራቸው ከተመለሱ በኋላ የአል ቓይዳን ድርጅት ተቀላቅለዋል። በየመን ከወህኒ ቤት የሸሹ አሸባሪዎችም ደም አፋሳሽ ጥቃታቸውን ቀጥለዋል። ከዚህ ሌላም ግፊት የበዛባቸው በሳውዲ ዓረቢያ ያሉ የአል ቓይዳ ደጋፊዎች ከየመኖቹ ጋር ባንድነት የዓረቢያ ከፊል ደሴት አል ቓይዳ ድርጅት አቋቁመዋል።
እነዚህ ምልክቶች ሁሉ በየመን በአል ቓይዳ የሰለጠነው ናይጀሪያዊ አንድ የዩኤስ አሜሪካ አይሮፕላን ላይ ጥቃት ለመጣል እስከሞከረበት ጊዜ ድረስ ችላ ተብለው ነው የቆዩት። በዚህም የተነሳ የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚደንት ባራክ ኦባማ በሀገራቸው የጸጥታ አካል ውስጥ ያለውን ጉድለት እንዲሚመረመር ብቻ ሳይሆን፡ ከየመንም ጋር የጠበቀ ትብብር እንደሚደረግ አስታውቀዋል።
የብሪታንያ ጠቅላይ ሚንስትር ጎርደን ብራውንም በየመን ስለሚታየው ሁኔታ በዚህ በተያዘው የአውሮጳውያኑ ጥር ወር ዓለም አቀፍ ውይይት እንዲደረግበት ሀሳብ አቅርበዋል። ጥቃት አል ቓይዳ ኋላፊነቱን ወስዶዋል። በዚህም የተነሳ የመን በጸረ ሽብርተኝነት አንጻር የተጀመረው ዘመቻ አዲስዋ የጦር ሰፈር እንዳትሆን አስግቶዋል። ትግሉ በኢራቅ፡ በአፍጋኒስታን እና በፓኪስታን የተወሰነ ስኬት ብቻ በማስገኘቱ ቀደም ሲል የተደመጠው አባባል አበረታቺ አይደለም።

ፔተር ፊሊፕ/አርያም ተክሌ

ሸዋዬ ለገሰ