1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመን፤ ከቃጠሎ የተረፉ ኢትዮጵያውያን

ዓርብ፣ መጋቢት 3 2013

ባለፈው እሁድ የመን ሰንዓ በሚገኝ አንድ የስደተኞች እስር ቤት ውስጥ በተነሳ የእሳት ቃጠሎ በርካታ ስደተኞች ሞተዋል እንዲሁም ተጎድተዋል። በስፍራው የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንደሚሉት አሁንም በርካቶች ለህይወታቸው አስጊ የሚባል ሁኔታ ላይ ይገኛሉ። በዛሬው የወጣቶች ዓለም ዝግጅታችን ከቃጠሎው ያመለጡ እና የመን የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን አነጋግራለች።

https://p.dw.com/p/3qVVO
Afrika Migration Jemen Küste Flüchtlinge
ምስል DW/R. Ali

የመን፤ ከቃጠሎ የተረፉ ኢትዮጵያውያን ምን ይላሉ?

መሀመድ ባለፈው እሁድ የመን ሰንዓ በሚገኝ አንድ የስደተኞች እስር ቤት ውስጥ ከደረሰው የእሳት ቃጠሎ ከተረፉ ኢትዮጵያውያን አንዱ ነው። « የተረፍነው ትንሽ ብቻ ነን» የሚለው መሀመድ  በአሁኑ ሰዓት ከሌሎች ኢትዮጵያውያን እና ሶማሊያውያን ጋር ሆስፒታል ውስጥ በህክምና ላይ ይገኛል።  « እግሬ እና እጄ ተቃጥሏል።» የሚለው መሀመድ ሰዎች ናቸው አትርፈውት ወደ ሆስፒታል የወሰዱት« ቦምብ ተጣለብን፣ ፍራሽ እና ብርድ ልብሱ እንዳለ ነደደ ። በኋላ ላይ ደግሞ ጭስ ተለቀቀብን። ከዛ እንስል ነበር።» መሀመድ በየመን እውቅና የሌለው ስደተኛ ነው። ከኢትዮጵያ የተሰደደው ሳውዲ አረቢያ ጅዳ ለመግባት እንደነበር ይናገራል። ይሁንና መሀመድ የመን ከገባ አንድ አመት የሆነው ሲሆን ከሶስት ወር በፊት ወታደሮች በቁጥጥር ስር አውለው አሁን ቃደሎው የደረሰበት እስር ቤት ከተውታል። ሌላኛው ከቃጠሎው የተረፈው ኢትዮጵያዊም መሀመድ ይባላል። እሱ ጉዳት ሳይደርስበት ከሌሎች ስደተኞች ጋር ለማምለጥ ችሏል። « አላህ ነው ያተረፈኝ። መፀዳጃ ቤት ነበርኩ። » መሀመድ በፖሊስ ተይዞ እስር ቤቱ ከገባ ገና አንድ ሳምንቱ ነበር። ሌላው በዚህ እስር ቤት ውስጥ የነበረ እና ከሞት የተረፈው ኢትዮጵያዊ ወጣት ሻሚል ይባላል። እንዴት ህይወቱ እንደተረፈ ሲናገር፤« በመጀመሪያ አንድ ቦታ ሰብስበውን ነበር። ለ 4 ወራት ያህል። ከዚያ በኋላ እስራቱ ሲበረታብን ልቀቁን ብለን የረሃብ አድማ ጀመርን። ወደ ሀገራችን መልሱን ብለን ደጋግመን ስንጮህ ነበር። እስር ላይ እያለን ለህክምና የሚሆን ገንዘብ እስከ 1000 ድረስ አምጡ ብለውንም ነበር። ቦምብ የተወረወረብን እኛ የርሃብ አድማ ከጀመርን በኋላ ነው። በጥቃቱ ከኛ ውስጥ ብዙዎቹ ሞተዋል። እኔም በላዬ ላይ የነበሩ የሟቾችን አስክሬን ካነሱ በኋላ ነው ያወጡኝ። »ይላል ሻሚል።

Afrika Migration Jemen Küste Flüchtlinge
በርካታ የኢትዮጵያ ስደተኞች የመን ይገኛሉምስል DW/R. Ali

የሀገሪቱ መገናኛ ብዙኃንን ጠቅሶ የጀርመን ዜና ምንጭ እንደዘገበው ቢያንስ 80 ሰዎች በዚሁ ቃጠሎ ሞተዋል ከ 150 በላይ ስደተኞችም ቆስለዋል። እንደ ዓለም አቀፉ የስደተኞች መርጃ ድርጅት IOM ከሆነ 900 የሚጠጉ ፣ አብዛኞቹም ኢትዮጵያውያን የሆኑ ስደተኞች በእስር ቤቱ ውስጥ ነበሩ። በአንድ የመንግስት ሆስፒታል ውስጥ የፅዳት ሰራተኛ ሆነው የሚሰሩ አንድ ኢትዮጵያዊ እንዳሉን ከሆነ አደጋው ከደረሰ በኋላ በርካታ አስክሬን እና ተጎጂዎችን የጫኑ አምቡላንሶች እሳቸው ወደሚገኙበት ሆስፒታል መጥተው ነበር። የሞቶትን ሰዎች ቁጥር ግን በውል አያውቁም። «  በአምስት መኪና ያህል የመጡት ሆስፒታሉ እንዲወርዱ ተደረጉ። ቀሪዎቹ ሌላ ቦታ ነው የተወሰዱት»  ምንም እንኳን የፅዳት ሰራተኛ ቢሆኑም እሳቸውም ተጎጂዎቹን ለመርዳት የቻሉትን ያህል እንደሞከሩ ነው የሚናገሩት። « ማታ እነሱ ጋር ገብቼ ሰውነታቸው ላይ ያለውን ሱሪ በመቀስ ቆርጬላቸዋለሁ። አልጋ ላይ ተኝተው ነው ያሉት። ስድስቱ ምንም አይሉም። ሁለቱ ግን በጣም ታመዋል።» የመን የሚገኙ የስደተኞችን ሁኔታ በቅርበት የሚከታተሉት አቶ በሽር ሀሰን በርካታ ስደተኞች የመን ውስጥ ታፍሰው እየታሰሩ እንደሆነ እና ርዳታ እንደሚሹ ከዚህ ቀደም ለዶይቸ ቬለ DW አስታውቀው ነበር። ይህ ቃጠሎ እንደደረሰም ወደ ስፍራው በመሄድ የሆነውን ታዝበዋል። ከበርካታ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ጋርም ተነጋግረዋል። ቃጠሎውም ሆን ተብሎ ሳይከሰት አይቀርም ይላሉ። « ከቃጠሎው የተረፉትን ልጆች ስንጠይቅ የምግብ አድማ አድርገን ነበር። ወደ ሀገራችን መልሱን ብለን። አንዱ ሰው ብሉ ብሎ ሲያስገድደን ከአንዱ ኢትዮጵያዊ ጋር ችግር ተፈጠረ » እንዳሏቸው  ይናገራሉ። ከተወሰነ ጊዜ በኋላም በተሰበሰቡት ስደተኞች ላይ ሰዎቹ መጥተው « የጋዝ ጭስ እንደተተኮሰባቸው» ከቃጠሎው የተረፉ ስደተኞች ነግረዋቸዋል። 
እሳት እንዴት እና በምን ሁኔታ እንደተቀሰቀሰ እስካሁን በየመን በኩል በግልጽ ይፋ የሆነ ነገር የለም ይሁንና በእስር ቤቱ አቅራቢያ ሳዑዲ መራሹ ጦር በሁቲ አማጽያን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መፈጸሙ ለቃጠሎው መነሻ ሳይሆን እንዳልቀረ የዜና ምንጮች ዘግበዋል። ከ 27 ዓመት በላይ ራሳቸውም በተመድ ከፍተኛ ኮሚሽን UNHCR ስር ስደተኛ ሆነው የመን ሀገር የኖሩት አቶ በሽር ሀሰን እንደሚሉት ይህ ጥቃትን የሰነዘሩ ሰዎች ታስረዋል። « የአማፂያኑ ባለስልጣናት ደንግጠዋል። እኛ አናውቅም ብለው። 15 ስደተኞችን ከተኙበት ተሽሏቸዋል ብለው ገንዘብ እና ልብስ ሰጥተው ለቀዋቸዋል። » ይሁንና አሁንም በርካታ ስደተኞች ችግር ላይ ይገኛሉ። የእሳት ቃጠሎው ከደረሰ ማግስት ጀምሮ ስደተኞች ወደ ተመድ ከፍተኛ ኮሚሽን UNHCR መስሪያ ቤት በመሄድ በየዕለቱ ድምፃቸውን በማሰማት ላይ ይገኛሉ። አቶ ኦብሳ ገዳ ከሰልፉ አስተባባሪዎች መካከል አንዱ ናቸው። የስደተኞቹ ጥያቄ « አንደኛ የሞቱትን አስክሬን ይስጡንና እንቅበር ሁለተኛ የቆሰሉትን እንድናያቸው ይፈቀድልን ሶስተኛ ወደ ሀገራችን እንድንመለስ ያድርጉን።» ሲሉ ያስረዳሉ።
ኢትዮጵያውያኑ እንደሚሉት ከሞቱት ስደተኞች መካከል በ UNHCR ም ሆነ በየመን መንግሥት በኩል የተመዘገቡ ስደተኞች ይገኙበታል።  የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ ኮሚሽንን ግን በጉዳይ ላይ ለማነጋገር በተደጋጋሚ በስልክ ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።  አቶ በሽር እንደነገሩን ከሆነ ከቃጠሎው የተረፉ ስደተኞችን በአሁኑ ሰዓት በማሰባሰብ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን የምግብ ርዳታ ለመለገስ እየሞከሩ ይገኛሉ። ከሰልፉ በኃላም ሰዎች አስክሬን እንዲረከቡ የሚደረግበት መንገድ እየተመቻቸ ነው። 

ልደት አበበ

Jemen I Schwere Gefechte in Sanaa
በሰሞኑ ጥቃት ቢያንስ 120 የሁቲ ተዋጊዎች በተሰነዘረባቸው ጥቃት መሞታቸው ተዘግቧልምስል Hani Al-Ansi/dpa/picture alliance

አዜብ ታደሰ