1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የመካከለኛዉ ምሥራቅ ትርምስና ኃያሉ ዓለም

ሰኞ፣ ነሐሴ 20 2005

ሠፊዉ ዓለም የግብፅን እልቂት ፍጅት፤ የሌላዉን ዓለም አፀፋ በቅጡ ለማስተንተን እንደገና ጊዜ አልነበረዉም።ወይም የሰዉ ደም ጠጥቶ ደም የሚጠማዉ ምድር ለሌላ ጥማቱ እርካታ ሶሪያን በመርዝ ጋዝ ሲያጥናት ትልቁም፥ ትንሹም፥ ምሥራቁም ምዕራቡም ቱጃሩም፥ ሐያሉም በሶሪያ የእልቂት ዜማ ያንጎራጉር ሌላዉ ይፎክር-ይዝት ገባ።

https://p.dw.com/p/19WOX
COMBINATION PICTURE - (FILES) - A file picture dated 30 November 2011 show the the head of Israel's parliamentary opposition Tzipi Livni (L) during a news conference at the Knesset, in Jerusalem, Israel. Another file picture dated 26 May 2013 shows Palestinian Chief negotiator Saeb Erekat at the second day of World Economic Forum, Dead Sea, west of Amman, Jordan. EPA/ABIR SULTAN/Jamal Nasrallah (Zu dpa "Israelis und Palästinenser nehmen direkte Friedensgespräche auf")
የእስራኤልና የፍልስጤም ተደራዳሪዎችምስል picture-alliance/dpa

የፍልስጤም እስራኤሎች የሰላም ተስፋ-በግጭት ዉዝግብ እንደጠወለገ ነዉ።ግብፅ በለመደችዉ ግጭት ጦርነት መሐል ብልጭ ያለባት ሠላም ዴሞክራሲ ለብቋት ታስመልሳለች።ሶሪያ በእልቂት ፍጅት ኢራቅን ለመቅደም ጥይት ቦምብ አልበቃ ብሏት መርዛማ-ጋዝ አክላበታለች።ሊባኖስ የሶሪያዉ እልቂት አጥኗት ደም ያስተፋታል።የአረብ ቱጃሮች፥ የዓለም ሐያላን ለየጥቅማቸዉ፥ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥትን በቀጥታም በተዘዋዋሪም እየደገፉ፥ከየተፋላሚዎቹ አንዱን እየረዱ ለሠላም፥ ለፍትሕ፥ ለዴሞክራሲ ሥርፀት ቆመናል ይላሉ።የመካከለኛዉ ምሥራቅ ሰሞናዊ እዉነት መነሻ፥ የቱጃር ሐያሉ ዓለም መንታ አቋም ማጣቃሻ፥ የሠላም ፍትሕ ዴሞክራሲዉ ተስፋ ፅልመት መድረሻችን ነዉ-ላፍታ አብራችሁኝ ቆዩ።


የፍልስጤማዉዊዉ ወጣት እና የብጤዎቹ ስሜትን የሚገልፀዉ ፅሁፍ የተነበበዉ፣ ወጣቱ አርኪ ቃል ያጣለት ደስታዉን የገለጠበት ንግግሩ የተሰማዉ፣ዋሸግተን፣ ቴል አቪብ፣ ረመላሕ ላይ እንዳዲሰ የተነገረዉ አሮጌ ዲፕሎማሲ፥ ቃል፣ እቅድ በእሰራኤ ሁለት ተቃራኒ እርምጃዎች በተስፋ፣ ቀቢፀ ተስፋ መቃረጡ ሲተነተን ነበር።ከሁለት ሳምንት በፊት።የዲፕላሚሲዊዉ ዘዋሪዎች፣ የዕቅዱ አርቃቂዎች፥ ቃል የገቡት፣ ገቢራዊነቱን መጀመራቸዉንም ለዓለም የነገሩት የዓለም ትልቅ ዲፕሎማት ናቸዉ።የዉጪ ጉዳይ ሚነሰተር ጆን ኬሪ።

«እንደሚመስለኝ ምክንያታዊ ማካካሻ ማድረግ የዚሕ ሁሉ ጥረት የማዕዘን ድንጋይ ነዉ።ድርድሩ ከባድ እንደሚሆን አዉቃለሁ።የዚያኑ ያክል አለመሞከር የሚያስከትለዉ መዘዝ የባሰ መሆኑንም አዉቃለሁ።»

የኬሪ ቃል፥ ቃላቸዉ መሆኑን ካረጋገጡት አንዱ፥ከዓለም ሐያላን መንበር የሚያጋራ ፈርጣማ ጡንቻ ያላቸዉ፤ የመካከለኛዉ ምሥራቅ የትላልቆች ትልቅ ናቸዉ።ጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ። ሁለተኛዉ ወሰን፣ ድንበሩ የተከለለ፣ ሉዓላዊነቱ የታወቀ ሐገር፣ በቅጡ የተደራጀ መንግሥት ፣ የሚያዙት ጦር ሳይኖራቸዉ ከነፃ ሐገር፣ ከደረጀ መንግሥት መሪ፣ ከጠንካራ ጦር ጠቅላይ አዛዥ እኩል የሚከበሩ፣ የሚጠሩት ናቸዉ።ፕሬዝዳንት ማሕሙድ አባስ።ሁሉንም ያፀደቁ፥የመረቁት ደግሞ የዘመኑ ዓለም ርዕሠ-ርዑሳን ናቸዉ።ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ።

የዓለም ትላልቆች የዓለምን ትልቅ ችግር ለመፍታት የገቡት አሮጌ-አዲስ ቃል፥ ጅምር በእስራኤል እርምጃ ሲጠናከር የፈነጠቀዉ ተስፋ፣ በቅፅበት፣ በሌላ የእስራኤል እርምጃ የመለንቆሱ ቀቢፀ ተስፋ ትልቁን ዓለም ሲያንጫጫ፣ በትላልቆቹ ፈቃድ መሠረት አባቱ የተፈታለት ትንሹ ፍልስጤማዊ ዓለመም፣ የዓለም ትላልቆችም «ያሻቸዉን ይበሉ» ዓይነት አለ።አባቴ እንደሁ ተፈትቷል።ስሙ አላዕ ሻዓት።

«ይሕን አጋጣሚ ለሃያ-አንድ አመታት ጠብቄዋለሁ።ይሕ ጊዜ አንድ ሚሊዮን ዓመት የሆነ ያክል ነዉ-የሚሰማኝ።በሕፃንነቴ አባቴ ተለየኝ።አሁን ተመለሰልኝ።ሃያ-ስምንት ዓመቴ ነዉ።ግን የሰባት አመት ልጅ የሆንኩ ያሕል ይሰማኛል።»

የትላልቆቹ እቅድ፣ ቃል፣ ጅምር የሐያ-አንድ ዘመን ሐዘን መከራዉን ባስወገደለት ማግሥት እስራኤል በሐይል በያዘችዉ የሐገሩ ግዛት የአይሁድ ሠፈራ መንደሮች መገንባቷን ለመቀጠል መወሰኗ የትላልቆቹን አሮጌ-አዲስ እርምጃ ባፍጢሙ ሊደፋዉ፣ የተፈቱት አባቱን መልሶ ወሕኒ ሊያስወረዉር እንደሚችል፣ አላዕ አላሰበዉም።ወጣቱም ብጤዎቹም ተራ ፍልስጤማዉያን ላስብ፥ ላሰላስል ቢሉም ጊዜ አልነበራቸዉም።

እንደ እዉነቱ ከሆነ ተራዉ ሠፊዉ ዓለምም ሠላም በማያዉቁት ወገኖች መሐል ሠላም የማዉረዱ አሮጌ-አዲስ እቅድ-ጅምር የምር ወይስ ለዲፕሎማሲ አመታዊ ግብር፥ ለኦባማ ወይም ለኬሪ ታሪክ ተጨማሪ ዝክር መሆን አለመሆኑን ለማስተንተን ፋታ አላገኘም።

የፍልስጤም ደፈጣ ተዋጊዎች ስደሮት የተባለችዉን የእስራኤል የድንበር ከተማ በሮኬት መቱ፥ እስራኤል ባፀፋዉ ጋዛን በጦር ጄት ደበደበች ሲባል፥ ዓለም-አይን ትኩረቱን ከዋሽግተን፥ ቴል አቪቭ፥ ረመላሕ ነቅሎ ጋዛ ላይ ተከለ።እንደ አላዕ አባት ከእስራኤል እስር ቤት ከተፈቱት የጋዛ ፍልስጤሞች አንዱ ደግሞ እንዲሕ አሉ።

«ድርድሩን አንደግፍም።የምዕራባዊ ዮርዳኖስ ወንዝ ዳርቻና የጋዛን የመላዉን ፍልስጤምን አንድነት ነዉ የምንደግፈዉ።አንድነቱ ይፈጠራል የሚል ተስፋ አለኝ።»ዓለም፥ ፍልስጤም፥ እስራኤል፥ ስደሮት ጋዛ፥ ማለት ሲጀምር ከወደ ግብፅ ቀልቡን የሚያናጥብ ሌላ እልቂት ተሰማ።መካከለኛዉ ምሥራቅ ለእልቂት ፍጅት ከሆነ ፋታ አያቅም። የትልቁን ታሪካዊ ምድር ትልቅ የስምንት ሺሕ-ዘመን ታሪካዊት ሐገርን ለወር ከሳምንት ሲያንተከትክ የነበረዉ ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት፥ ዉዝግብ፥ ግጭት፥ ገነፈለ።ነሐሴ-አጋማሽ።(ቀን ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ።) ግብፅ፥ በአደባባይ እልቂት፥ ባንዳዶች ቋንቋ «በጅምላ» ግድያ፥ በዘፈቀደ እስራት፥ በቃጠሎ ትንጨረጨር ገባች።

«ጦር ሐይሉ ወይም ሐገሪቱን ባሁኑ ወቅት የሚገዛዉ ሐይል በረበዓ እና በናዳ ሠላማዊ ሠልፈኞች ላይ በወሰደዉ እርምጃ ጭፍጨፋ መፈፀሙን አይተናል።በትንሽ ሰዓታት ብቻ ስድስት መቶ ሰዎችን መግደል ጭፍጨፋ ከመባል ሌላ ሌላ ሊባል አይችልም።»

አሉ እሳቸዉ።ግብፃዊ ናቸዉ።ሰዓቱ ሲጨምር የግብፅ ጦር፥ በአደባባይ የሚረሽነዉ ሰዉ ቁጥር እየጨመረ ከሺሕ በለጠ።ወታደራዊዉን መፈንቅለ መንግሥት የሚቃወመዉ ሙስሊም ወንድማማቾች እንደሚለዉ ከሁለት ሺሕ በለጠ።የአደባባዩ ግድያ ቃጠሎ ወደ ወሕኒ ቤት ተዛመተ።

«ወንድሜ ትናንት አቡ ዛአብል እስር ቤት ታስሮ ነበር።ትናንትናዉኑ እስር ቤቱ ተደበደበ በወድሜ ላይ የደረሰዉን አናዉቅም።ሰላሳ-ስድስት እስረኞች መገደላቸዉን ሰምተናል።ወደ እስር ቤት ለመሔድ አቅደን ነበር።ግን እሱም ተገድሎ እንደሁ ብለን አስከሬኑን ፍለጋ ወደዚሕ ወደ አስከሬን መከማቻዉ ክፍል መጣን።»

መስጊድም ከመፀለያነት ወደ ሰዎች ቄራነት ተለወጠ።በርካቶች መገደል መቁሳላቸዉ ተዘግቧል። መሳጂዶች፥ አብያተ-ክርስቲያናት፥ የመንግሥት መስሪያ ቤት ሕንፃዎች፥ ጋይተዋል።ጊዚያዊ የድንኳን ሐኪም ቤቶች ከነቁስለኞቻቸዉ መንደዳቸዉም ተዘግቧል።መፈንቅለ መንግሥቱን የሚቃወሙ፥የሙስሊም ወድማማቾች ማሕበረሰብ ደጋፊዎች፥አባላት፥ መሪዎች እየታፈሱ ታስረዋል።የአደባባይ ሠላማዊ ሠልፍ ታግዷል። የሠዓት እላፊ ገደብ ተደግጓል።

የቀድሞዉ የአዉሮጳ ሕብረት ምክር ቤት ፕሬዝዳት-ጀርመናዊዉ ፖለቲከኛ ሐንስ-ጌርት ፖተሪንግ እንደሚሉት ሕብረቱ ከግብፅ ዲያሞክራሲያዊ ሐይላት ጎን ነዉ የቆመና የሚቆመዉ።

«የካቲት ሁለት ሺሕ አስራ-አንድ ተሕሪሪ አደባባይ (ተሰልፈዉ) የነበሩ አስደናቂ ወጣቶችን አነጋግሬያለሁ።በክብር መኖር እንደሚፈልጉ ነግረዉኛል።ኑራቸዉን እራሳቸዉ በነፃነት መወሰን ይፈልጋሉ።በዲሞክራሲያዊ እና ፍትሐዊ ሥርዓት መኖር ይፈልጋሉ።ከነዚሕኞቹ ጎን ነዉ እኛ የቆም ነዉ።»

እርግጥ ነዉ የግብፅ ጦር ሐይል ሠላማዊ ተቃዋሚ ሠልፈኞችን ካደባባይ እስከ ድንኳን፥ ከወሕኒ ቤት እስከ መስጊድ እያሳደደ መግደል፥ ማቃጠል፥ መደብደብ ማሠሩን ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እስከ አዉሮጳ ሕብረት የሚገኙ ግዙፍ ማሕበራት አጥብቀዉ ተቃዉመዉታል።ከፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ እስከ መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ያሉ የሐያሉ ዓለም መሪዎች አዉግዘዉታል።

«የግብፅ ጊዚያዊ መንግሥትና የፀጥታ ሐይላት የወሰዱትን እርምጃ ዩናይትድ ስቴትስ አጥብቃ ታወግዛለች።ሠላማዊ ተቃዉሞን ጨምሮ ለሰዉ ልጅ በጣም አስፈላጊ የሆነዉን ሁለንተናዊ መብቶችን እንደግፋለን።ከሰወስች ነፃነት ፀጥታ ማስከበር ይበልጣል ወይም ሐይል ሁሉንም ያስገብራል በሚል ሰበብ እነዚሕን መሠረታዊ መብቶች የሚገፈዉን የአስቸኳይ ጊዜ ድንጋጌን እንቃወማለን።»

ግብፅን ከሁለት ዓመት የሠላም፥ የዲሞክራሲ ብልጭታ በሕዋላ ለዘመናት ወደለመችዉ አምባገነናዊ አገዛዝ የዶለዉ፥ከእልቂት ፍጅት የጨመረዉ የሐገሪቱ ጦር ሐይል በሕዝብ የተመረጡትን ፕሬዝዳት ከስልጣን ማስወገዱ ነበር።

ጄኔራል አብዱል ፈታሕ አል-ሲሲ በሕዝብ የተመረጡትን ፕሬዝዳት መሐመድ ሙርሲን አስወግደዉ፥ መንግሥታቸዉን አፍርሰዉ፥ በሕዝብ የተመረጠ ምክር ቤት፥ በሕዝበ-ዉሳኔ የፀደቀ ሕገ-መንግሥት ሽረዉ አዲስ መንግስት ሲያቆሙ «ሐይ» ባይ ካለ «ሐይ» ሊላቸዉ በተገባ ነበር።እንዲያዉም የጀኔራሉን እርምጃ የሪያድ፥ የማናማ፥ የኩዌት ነገስታት አሞገጋገሱት።ከየሕዝባቸዉ ሐብት ያለ-ሕዝባቸዉ ፈቃድ ቆንጠረዉ አስራ-ሁለት ቢሊዮን ዶላር ለገሱት።ሌላም ሊያንቆረቁሩለት ቃል ገቡ።

ለሰብአዊ መብት መከበር፥ ለፍትሕ ዲሞክራሲ ሥርፀት፥ ለሰዎች መብት-እኩልነት ቆሚያለሁ የሚለዉ ፥ በአዉሮጳ ሕብረቱ ፖለቲከኛ ቋንቋ «ከዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ጎን» የተሰለፈዉ ሐያል ዓለም መፈንቅለ መንግሥቱን ሊያወግዝ ቀርቶ በይፋ «መፈንቅለ መንግሥት» ለማለት እንኳ አልፈለገም።ሠፊዉ ዓለም የግብፅን እልቂት ፍጅት፤ የሌላዉን ዓለም አፀፋ በቅጡ ለማስተንተን እንደገና ጊዜ አልነበረዉም።ወይም የሰዉ ደም ጠጥቶ ደም የሚጠማዉ ምድር ለሌላ ጥማቱ እርካታ ሶሪያን በመርዝ ጋዝ ሲያጥናት ትልቁም፥ ትንሹም፥ ምሥራቁም ምዕራቡም ቱጃሩም፥ ሐያሉም በሶሪያ የእልቂት ዜማ ያንጎራጉር ሌላዉ ይፎክር-ይዝት ገባ።

የሶሪያ መንግሥትን በሐይል ለማስወገድ የሚዋጉት አማፂያን እንደሚወነጅሉት የሶሪያ መንግሥት ጦር ባለፈዉ ሮብ ደማስቆ አጠገብ በረጨዉ ወይም በተኮሰዉ መርዛማ ጋዝ ከአንድ ሺሕ በላይ ሰዎች አልቀዋል።የሶሪያ መንግሥት ግን ዉንጀላዉን አስተባብሏል።ወትሮም የበሽር አል-አሰድን መንግሥት የሚፋለሙትን ሐይላት የሚደግፈዉ ሐያል ዓለም ግን ማስተባበያዉን የወንጀላዉን ያክል ለመስማት ትዕግሥት አልነረዉም።እንዲያዉም የአሰድ መንግሥት እንደተጠረጠዉ ሰዎችን በመርዛማ ጋዝ ገድሎ ከሆነ አፀፋዉ ቀላል እንደማይሆን ያስፈራራ ገባ። የብሪታንያዉ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ዊሊያም ሔግ ከቀዳሚዎቹ አንዱ ነበሩ።

«ከተረጋገጠ ይሕ ሶሪያ ዉስጥ የኬሚካዊ ጦር መሳሪያን ጥቃት የሚያባብስ አስደንጋጭ ድርጊት ነዉ።ድርጊቱን የፈፀሙት ሰዎችን አንድ ቀን ተጠያቂ ለማድረግ ቆርጠናል።ደማስቆ የሚገኘዉ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የመርማሪዎች ቡድን (ጋዙ ወደ ተተኮሰበት) አካባቢ ያለገደብ ለመግባት ይፈቀድለታል የሚል ተስፋ አለኝ።ብሪታንያ ይሕን ጉዳይ ለፀጥታዉ ጥበቃ ምክር ቤት ታቀርባለች።»

የፈረንሳዩ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ደግሞ የብሪታንያ አቻቸዉን ሐሳብ አሻሽለዉ ሐያሉ ዓለም ወደ ሶሪያ ጦር ሊያዘምት እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።ፉከራ ማስጠንቀቂያዉ ከፓሪስ ለንደን፥ ዋሽግተን ሲንቆረቆር የደማስቆ መንግሥትን የሚደግፉና የሚቃወሙ የሊባኖስ ደፈጣታ ተዋጊዎች የቦምቦ ኳስ ይወራወሩ ያዙ።ሰጋጆች መስጊድ፥ተላዋሾች መንደር ተገደሉ።


ምዕራባዉያኑ እንደዛቱ-እንደፈኮሩት የደማስቆን መንግሥት በሐይል ማስወገዱ ጥሩም-መጥፎም ሊሆን ይችላል።በሶሪያዉ የርስ በርስ ጦርነት ሰዎች በመርዝ ጋዝ መገደል አለመገደላቸዉ በገለልተኛ ወገን መጣራቱ ግን ተገቢ ነዉ።ገዳዮች ለፍርድ እንዲቀርቡ መጠየቁም ትክክል ነዉ።ግን የግብፅን ግድያ ያወገዘዉ ዓለም ግድያዉ እንደ ሶሪያዉ እንዲጣራ ያልጠየቀበት፥ ሠላማዊ ሰልፈኞችን የገደሉት ለፍርድ እንዲቀርቡ ያልገፋፋበት በሔግ አገላለፅ «ያልቆረጠበት» ምክንያት ለአመክንዮ ሲበዛ ግራ ነዉ።

ለነገሩ-የግብፅ የጦር ጄኔራሎች ሺዎችን ባስገደሉ ማግሥት ዘጠኝ መቶ ያክል ሰዎችን በማስገደል የተወነጀሉት የቀድሞዉ የሐገሪቱ ገዢ፥ የቀድሞዉ የአየር ሐይል ማርሻል ሆስኒ ሙባረክ ከእስር ቤት ተለቀዋል።«መዓሰላማ ዲሞክራሲ» ይል ይሆን ግብፅ።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

Hosni Mubarak Afrikanische Union Gipfel in Scharm el Scheich Ägypten Egyptian President Hosni Mubarak attends the closing session of the African Union summit in Sharm el-Sheikh, Egypt, Tuesday, July 1, 2008. Prospects for a peaceful deal between Zimbabwe President Robert Mugabe and his top opponent appeared to grow more distant Tuesday despite efforts by African leaders at the summit.(AP Photo/Nasser Nasser)
ሙባረክምስል AP
Egyptian protesters evacuate an injured fellow protester, center on the motorcycle during clashes with security forces, unseen at Tahrir Square in Cairo, Egypt Wednesday, June 29, 2011. Egyptian security forces clashed with hundreds of youths for a second day Wednesday in Cairo over demands that the country's military rulers speed up the prosecution of police officers accused of brutality during mass protests that forced Hosni Mubarak to step down. Some 180 people have been injured, officials said. (Foto:Nasser Nasser/AP/dapd)
ግብፅምስል AP
Smoke is seen above people gathering outside a mosque on the site of a powerful explosion in the northern Lebanese city of Tripoli on August 23, 2013. Two powerful explosions killed several people: one rocked the city centre near the home of outgoing Prime Minister Najib Mikati, the second one struck near the port of the restive city with a Sunni Muslim majority. The explosions come a week after a suicide car bombing killed 27 people in a Beirut stronghold of the Lebanese Shiite movement Hezbollah, which is fighting alongside Assad's forces. AFP PHOTO IBRAHIM CHALHOUB (Photo credit should read IBRAHIM CHALHOUB/AFP/Getty Images)
ሊባኖስምስል Ibrahim Chalhoub/AFP/Getty Images
Pigeons lie on the ground after dying from what activists say is the use of chemical weapons by forces loyal to President Bashar Al-Assad in the Damascus suburbs of Arbeen August 24, 2013. Picture taken August 24, 2013. REUTERS/Ammar Dar (SYRIA - Tags: POLITICS CIVIL UNREST CONFLICT ANIMALS TPX IMAGES OF THE DAY)
ሶሪያምስል Reuters

ነጋሽ መሐመድ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ