1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የማሊው ምርጫ ውጤት

ዓርብ፣ ሐምሌ 26 2005

27 ተፎካካሪዎችን ያወዳደረው የማሊው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ፣ ባንድ ዙር እልባት ሊደረግለት ባለመቻሉ ነሐሴ 5 ቀን 2005 ዓ ም ፤ በ 2 ኛ ዙር ውድድር እንደሚደመደም ተነገረ። ያኔ የሚቀርቡት 2 ተወዳሪዎች ብቻ ሲሆኑ እነርሱም ፤ የቀድሞው ጠ/ሚንስትር

https://p.dw.com/p/19J5i
ምስል Reuters/Joe Penney

ኢብራሂም ቡባካር ኬይታና የቀድሞው የፋይናንስ ሚንስትር ሱማይላ ሲሴ ናቸው። ምርቻው የሚደገመው ፤ 50 ከመቶ ያመጣ ተፎካካሪ ባለመገኘቱ ነው፤ ኢብራሂም ቡባከር ኬይታ 34,24 ከመቶ ሲያገኙ፤ ሲሴ ፤ 19,44 ከመቶ በማግኘት የመጀመሪያውን ዙር አጠናቀዋል።

Mali Präsidentschaftswahl 30./31. Juli Soumaila Cisse
ምስል DW/K.Gänsler

በፕሬዚዳንታዊው ውድድር ፤ «አዴማ » የተባለው የማሊው እጅግ ትልቅ ፓርቲ ተወካይ፤ የቀድሞው የማዕድን ጉዳይ ዋና ሥራ አስኪያጅ ድራማን ደምበሌ፣ 9,59 ከመቶ ነው ያገኙት። ከ 27 ቱ ተፎካካሪዎች መካከል ብቸኛይቱ ሴት ተወዳዳሪ፣ ሃይዳራ አይሳታ ሲሴ ፣ 0,76 ከመቶ ብቻ እንዳገኙ ነው የተነገረው።

ስለምርጫው ፣ የኢብራሂም ቡባካር ኬይታ፣ ደጋፊ እንዲህ ይላሉ---

«በመሠረቱ ፤ ዳግመኛ ምርጫ ሊያጋጥም ባልተገባ ነበር። ነገር ግን መስተዳደሩ ይህን ውጤት መዝግቧል። ስለሆነም መቀበል ይኖርብናል።»

የሱማይላ ሲሴ ደጋፊ ደግሞ ይህን ብለዋል።

በጣም ጥሩ ነው። የማሊያውያን በጎ ፈቃድ ተቀባይነት አግኝቷል። ህዝቡ በሰፊው ነው አደባባይ ወጥተው በምርቻው የተሳተፉት። እናም ድምጻቸው 2ኛ ዙር ምርቻ እንዲካሄድ አብቅቷል»።

ግዙፏና እጅግ ከደኸዩት አፍሪቃውያን ሃገራት መካከል አንዷ የሆነችው ማሊ፤ አምና ሁለት ብርቱ ፈተናዎች አጋጥመዋት እንደነበረ አይዘነጋም፤ በመጀመሪያ በመጋቢት ወር 2004 ዓ ም፤ መፈንቅለ-መንግሥት ተካሄደ ፤ ከዚያም ሰሜናዊውን የሀገሪቱን ክፍል ፣ ቱዓሬጎች «አዛዋድ » የሚሉትን ለመገንጠል ተንቀሳቀሱ፤ ቀጥሎ ቱዓሬጎችን ወደ ጎን የገፋ አክራሪ እስላማዊ እንቅስቃሴ በጦር ኃይል እየገፋ ከሰሜናዊው ማሊ ወደ ባማኮ ሲያመራ ነው ፈረንሳይ ባስቸኳይ የጦር ኃይል ልካ የተገታውም ሆነ ታጣቂዎቹ ኃይሎች ወደነበሩበት እንዲመለሱ የተደረገው። ማሊ የነበረችበትን የዴሞክራሲ ፈር እንድትይዝ፤ በሀገሪቱ የተከሠቱትን፣ ፖለቲካዊ፣ ኤኮኖሚያዊና፣ ማኅበራዊ ችግሮች እንድትፈታም ነው ሐምሌ 21 ቀን 2005 ባገሪቱ አጠቃላይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማድረግ ያስፈለጋት። በዴሞክራሲ የሚመረጠው አስተዳደርም ፣ የሀገሪቱን የተለያዩ ችግሮች በዴሞክራሲ ወግ ይፈታል ተብሎ ነው የሚጠበቀው።

Präsidentschaftswahl in Mali Wahlwerbung
ምስል DW/K.Gänsler

የአዛዋድ ብሔራዊ ነጻ አውጭ ንቅናቄ የተሰኘው ፤ በሰሜን ማሊ የሚገኘው የቱዓሬጎች ታጣቂ ኃይል ግን ጥርጣሬ አለው።

የንቅናቄው ቃል አቀባይ ሙሣ አሳሪድ--

«እና አልመረጥንም። ለምን የራሳችን እጩ ተወዳዳ የለንምና። ምርጫው ያለ ችግር መከናወኑ ደስ ብሎናል። ማንም ያሸንፍ ፤ እኛ ፤ ከማንም ጋር አብረን ለመሥራት ዝግጁ ነን። የአካባቢው የፖለቲካው ፈቃድ፣የአዛዋድ ህጋዊ ይዞታም በሚታይበት ሁኔታ ላይ ለመነጋገር ዝግጁ ነን። በማሊው ምርጫ የሚያሸንፈው ህጋዊ ሥልጣን ስለሚሰጠው፤ ከዚሁ ፕሬዚዳንትና አስተዳደሩ ጋር ለመደራደር ፈቃደኞች ነን።»

የምዕራብ አፍሪቃዊት ሀገር ማሊ የሀገር አስተዳደር ሚንስትር፣ ኮሎኔል ሲንኮ ሙሣ ኩሊባሊ ዛሬ ባማኮ ውስጥ ፤ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ መሠረት ፣ ከሀገሪቱ 6,5 ሚሊዮን ኑዋሪዎች መካከል ለምርጫ ብቁ ከሆኑት መካከል 51,5 ከመቶው ለምርጫ አደባባይ መውጣታቸውን ነው የገለጹት። በምርጫ ከተወዳደሩት መካከል፣ አምና በመጋቢት የተካሄደውን ወታደራዊ መፈንቅለ መንግሥት ያላወገዙ ኬይታ ብቻ ናቸው። በመሆኑም፤ ጦር ሠራዊቱ የሚደግፋቸው ፖለቲከኛ መሆናቸው ይታሰባል።

በአሁኑ ጊዜ የምዕራብ አፍሪቃ የገንዘብ ኅብረት ፕሬዚዳንት በመሆን በማገልገል ላይ የሚገኙት ሱማኤላ ሲሴ ፣ የሰሜን ማሊዋ ታሪካዊ ከተማ ቲምቡክቱም ተወላጅ ናቸው። ወደ ትውልድ አገራቸው እ ጎ አ በ 1984 ዓ ም ከመመለሳቸው በፊት፤ በፈረንሳይ፤ ለ IBM እና ሌሎች ታላላቅ ኩባንያዎች ሠርተዋል።

እጎ አ በ 20032 በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ፤ ሲሴ 2 ና ሲወጡ ኬይታ 3ኛ ነበሩ። በምርጫው አሸናፊ የነበሩት አማዱ ቱማኒ ቱሬ እንደነበሩ አይዘነጋም። እ ጎ አ በ 2007 ፣ ኬይታ እንደገና በቱሬ መሸነፋቸው የሚታወስ ነው።

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ