1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምሥራቅ አፍሪቃ ተጠንቀቅ ኃይል የምርጫ ታዛቢዎች ሥራ ጀመሩ

ቅዳሜ፣ ሰኔ 12 2013

የምሥራቅ አፍሪቃ ተጠንቀቅ ኃይል በእንግሊዝኛ ምህፃሩ (EASF) የፊታችን ሰኞ ሰኔ 14 ቀን፣ 2013 ዓ.ም የሚደረገውን የኢትዮጵያ ምርጫ የሚከታተሉ 28 ታዛቢዎቹን ዛሬ በይፋ ወደ ሥራ አሰማራ። ኃይሉ ኢትዮጵያን ጨምሮ ዐሥር አባል ሃገራት አሉት። ነገር ግን የሰኞውን ምርጫ የሚከታተሉ ታዛቢዎች የተውጣጡት ከስምንቱ ሃገራት ነው።

https://p.dw.com/p/3vEQx
Äthiopien | Eastern Africa Standby force
ምስል Solomon Muchie/DW

የምሥራቅ አፍሪቃ ተጠንቀቅ ኃይል በእንግሊዝኛ ምህፃሩ (EASF) የፊታችን ሰኞ ሰኔ 14 ቀን፣ 2013 ዓ.ም የሚደረገውን የኢትዮጵያ ምርጫ የሚከታተሉ 28 ታዛቢዎቹን ዛሬ በይፋ ወደ ሥራ አሰማራ። ኃይሉ ኢትዮጵያን ጨምሮ ዐሥር አባል ሃገራት አሉት። ነገር ግን የሰኞውን ምርጫ የሚከታተሉ ታዛቢዎች የተውጣጡት ከስምንቱ ሃገራት ነው። የታዛቢው ቡድን የበላይ ኃላፊዎች ዛሬ ስቱዲዮ ከመግባታችን ጥቂት ቀደም ብሎ አዲስ አበባ ውስጥ በሠጡት መግለጫ እንዳሉት ኢትዮጵያ አስተናጋጅ በመሆኗ የታዛቢውን ቡድን አትቀላቀልም። ሌላኛዋ አባል ሀገር ሱዳን ታዛቢ አባል አልላከችም። ኃላፊዎቹ በዚህ ጉዳይ ላይ ዝርዝር ማብራሪያ መስጠት የእኛ ኃላፊነት አይደለም ብለዋል። ይሁንና የሚሽኑ ምክትል ኃላፊ ሊና ሆሬስ እንዳሉት፦ የኢትዮጵያን ምርጫ መታዘብ ለዐሥሩም አባል ሃገራት ጠቃሚ ነው።

«ኢትዮጵያ የእኛ አንዷ አባል አገር ናት፤ ለቀጠናችንም የመረጋጋት ምንጭ ናት። ሰላማዊትና የበለፀገች ኢትዮጵያ ማለት ደግሞ በሁሉም (EASF) ምስራቅ አፍሪቃ አባል ሃገራት ቀጠና ሰላምና ብጽግና ማለት ነው። ሁሉም ከዚህም ያተርፋሉ።»

የምሥራቅ አፍሪቃ ተጠንቀቅ ኃይል (EASF) የምርጫ ታዛቢ ልዑካን ቡድኑ የተውጣጡት ከተጠባባቂ ኃይሉ 8 አባል ሃገራት ማለትም፦ከብሩንዲ፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ሲሼልስ፣ ኡጋንዳ፣ ሩዋንዳ እና ኮሞሮስ ነው።  የምርጫ ታዛቢው የልዑካን ቡድን በጅቡቲው አምባሳደር አብዲላሂ ኦውሌድ ዓሊ እና በምክትላቸው የሲሼልስ ዜጋ በኾኑት ወይዘሮ ሊና ኦራዬ የሚመራ መሆኑም ልዑኩ ትናንት ባሠራጨው መግለጫው ገልጧል። ዛሬ በሰጠው በጋዜጣዊ መግለጫውም ቀጣዩን አክሏል።

«በምሥራቅ አፍሪቃ ተጠንቀቅ ኃይል ርእይ መሠረት ተልእኮዋችንን መጀመራችን ሳሳውቃችሁ ደስታ ይሰማኛል። ዋነኛ ኃላፊነታችንም የምርጫ ኺደቱን መታዘብ እና መረጃ ማጠናቀር ነው። ማናቸውንም ተግዳሮቶች ከታዘብን ለአስተናጋጇ ሀገር ጠቃሚ ምክረ-ሐሳብም እናቀርባለን።»

የታዛቢ ቡድኑ ልዑካን ከሀገሪቱ የፖለቲካ አመራር፣ ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አባላት፣ ከመገናኛ አውታሮች፣ ከሲቪል ማኅበረሰብ ተወካዮች እንዲሁም ስድስተኛውን አጠቃላይ የኢትዮጵያ ምርጫ ለመታዘብ ፍቃድ ካገኙ የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አባላት ጋር እንደሚገናኝም ዐሳውቋል። የፖለቲካ መሪዎች እና እጩዎች በምርጫው ወቅት በመከባበር እና በመቻቻል የሰብአዊ መብትቶችን ባከበረ መልኩ እንዲንቀሳቀሱም ከወዲሁ አሳስቧል። መራጮች በንቃት በመሳተፍ የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ እና ሕገመንግሥታዊ ተግባራቸውን እንዲተገብሩም ጥሪ አስተላልፏል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ሰለሞን ሙጬ

ነጋሽ መሐመድ

ኂሩት መለሰ