1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምስራቅ ዩክሪይን ዉዝግብ መቋጫ ሊገኝ ነዉ ?

ማክሰኞ፣ ኅዳር 30 2012

በሩስያንና ዩክሪይን መካከል ከፍተኛ መቃቃርን ያስከተለዉ እና ለዓመታት ተቋርጦ የነበረዉ የምስራቅ ዩክሬይን የሰላም ድርድር ገቢራዊ የሚሆን የሰላም መፍትሄ እደተገኘለት ተመለከተ። «የኖርማንዲ ፎርማት » የተባለዉ ይህ ጉባዔ ፤ ለመጨረሻ ጊዜ የዛሬ ሦስት ዓመት በርሊን ላይ ተካሂዶ እንደነበር የሚታወስ ነዉ።  

https://p.dw.com/p/3UZ1i
Paris Ukraine-Gipfel PK
ምስል AFP/L. Marin

በሩስያንና ዩክሪይን መካከል ከፍተኛ መቃቃርን ያስከተለዉ እና ለዓመታት ተቋርጦ የነበረዉ የምስራቅ ዩክሬይን የሰላም ድርድር ገቢራዊ የሚሆን የሰላም መፍትሄ እደተገኘለት ተመለከተ። የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥትን ጨምሮ የአራት ሃገራት መሪዎች ትናንት ምሽት ፓሪስ ፈረንሳይ ላይ ይፋ እንዳደረጉት ሦስት ሳምንት በቀረዉ የጎርጎረሳዉያን 2019 መጨረሻ ድረስ በምስራቅ ዩክሪይን ሙሉ በሙሉ የተኩስ አቁም ተግባራዊ እንዲደረግ ተስማምተዋል። ከተኩስ አቁሙ ሌላ የዩክሪይን ወታደሮች እና በሩስያ የሚደገፉ አማፂያን ምስራቅ ዩክሬንን ሙሉ በሙሉ እንዲለቁ እና ምርኮኛ ወታደሮች እንዲለዋወጡ ስምምነት ላይ ተደርሶአል። ሩስያና ዩክሪይን በ2015 ዓም ከምስራቅ ዩክሬይን ከባድ የጦር መሳርያዎችን ለማዉጣት እና የተኩስ አቁም ለማድረግ ስምምነት ላይ ደርሰዉ እንደነበር ይታወቃል። ትናንት ፓሪስ ዉስጥ በተደረገዉ ጉባኤ ላይ የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል፤ የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኤማኑኤል ማክሮ፤ የሩስያዉ ፕሩሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን እንዲሁም አዲሱ የዩክሬይን ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ሴሌንስኪ ተካፋይ ነበሩ። ከጉባዔዉ በኋላ የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጉባዔዉ ስኬታማ እንደሆን ተናግረዋል።
«የዛሬዉ ስብሰባችን ከባድ የሆኑ ጥያቄዎችን ለመፍታት ጥሩ ፍላጎት የታየበት ነዉ። ይህ ጥሩ ፍላጎት ደግሞ ሁሉንም የፖለቲካ ጥያቄዎችና ችግሮች የሚፈታ ነዉ። እርግጥ ነዉ በዚህ ጉባዔዉ የሩሲያዉ ፕሬዚዳንት ፑቲን እና የዩክሬይኑ ፕሬዚዳንት ሳሊኒስኪ ለመጀመርያ ጊዜ ነዉ የተገናኙት። በዉይይታችን የአዉሮጳ ፖለቲካ ጥያቄዎችንም አንስተናል። በአዉሮጳም ብዙ ልንሰራ ይጠበቅብናል። የፓሪሱ ጉባዔያችን እጅግ ለሁሉም ተካፋዮች ጥሩ ነበር። »    
ሩስያን እና ዩክሪይን የተቃቃሩበት የምስራቅ ዩክሪን ዉዝግብን ለመፍታት በጎርጎረሳዉያኑ 2014 የተቋቋመዉ «የኖርማንዲ ፎርማት » የተባለዉ ይህ ጉባዔ ፤ ለመጨረሻ ጊዜ የዛሬ ሦስት ዓመት በርሊን ላይ ተካሂዶ እንደነበር የሚታወስ ነዉ።      

 

አዜብ ታደሰ 

ነጋሽ መሐመድ