1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምክር ቤት አባላት ትችትና ኢቢሲ

ረቡዕ፣ ግንቦት 2 2009

የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፓሬሽን የህዝብ ድምፅ መሆን አልቻለም ተባለ። ኮርፓሬሽኑ የቆመለትን ዓላማ ከማሳካትና የመልካም አስተዳደር ችግርን የሚያሳዩ ዘገባወች ከማቅረብ ይልቅ ማስታወቂያወች ላይ በማተኮር ወደ ንግድ ተቋምነት አዘንብሏል የሚል ወቀሳ ሰሞኑን በምክር ቤት አባላት  እንደቀረበበት የሀገር ዉስጥ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

https://p.dw.com/p/2chIa
Äthiopien | Parlament
ምስል DW/Y. G. Egziabher

parliament members criticized EBC - MP3-Stereo


የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት የአሁኑ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮፖሬሽን «ኢቢሲ» እንደ ህዝብ የመገናኛ ብዙሃን ተቋምነቱ የህዝብ ችግር ላይ ከማተኮርና  የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ከመንቀስ ይልቅ  የተሳኩ ተግባራት ላይ ብቻ ያተኩራል ተብሏል።
ባለፈዉ ሀሙስ ሚያዚያ 26 ቀን 2009 አ/ም የኮርፖሬሽኑ ሀላፊወችና የቦርድ አባላት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ጋር ባደረጉት ዉይይት የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፓሬሽን የቆመለትን «የህዳሴና የብዝሃነት ድምፅ»ዓላማ የሚያሳኩና  ዘገባወችን ማቅረቡን ወደጎን ትቶ ማስታወቂያ በማብዛት ወደ ንግድ ተቋምነት አዘንብሏል መባሉን የምክር ቤት አባላቱን ጠቅሰዉ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።
ኮርፓሬሽኑ የህዝቡን ነባራዊ ሁኔታወች የሚያሳዩ ዘገባወችን በማቅረብ ረገድም እጥረት አለበት ተብሏል።  የግለሰቦችና የመንግስት ባለስልጣናት ተፅኖ ስር በመዉደቁም  ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዳልተወጣ በምክር ቤት አባላቱ መነሳቱ ተገልጿል።
ዶቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ በኖሮዌ ሀገር በዓለም አቀፍ ጋዜጠኝነት  የሁለተኛ ዲግሪያቸዉን በመከታተል ላይ ያሉት አቶ ምንይችል  መሰረት  በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃንና ጋዜጠኝነት ላይ ጥናት አድርገዋል። እሳቸዉ እንደገለጹት፤ የህዝብ የመገናኛ ብዙኃን ከህዝብ በሚገኝ ገንዘብና በመንግስት ድጎማ የሚተዳደሩ በመሆናቸዉ ከመንግስት ጋር የሚያገናኛቸዉ ነገር ሰፊ ነዉ። ያ ማለት  ግን መንግስት ጣልቃ ይገባል ማለት እንዳልሆነ ጠቁመዉ፤ ጣልቃ የሚገባም ከሆነ የዳበሩ የዘገባ ይዘቶች በተቋማቱ እንዲኖር ለማድረግና የህዝብን ጥቅም ከማስከበር አንጻር መሆን እንዳለበት አብራርተዋል። በመርህ ደረጃ የህዝብ መገናኛ ብዙኃን ዓላማም ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ማገልገል ነዉ ሲሉ አስረድተዋል።

Gambia Street in Addis Abeba, Äthiopien
ምስል picture alliance/dpa

«የዚህ የፐብሊክ ሰርቪስ ብሮድካስቲንግ  በሚባለዉ የሚዲያ አስተሳሰብ ዋና ዓላማዉ በሶሻል ዲሞክራቲክ አስተሳሰብ ዉስጥ የሚገኝ ነዉና ማንኛዉንም ማህበረሰብ  የሚያገለግል ሚዲያ መክፈት ነዉ ።ይህም ሲባል በዕድሜ ፣በጾታ ፣በዘር ሁሉንም የማህበረሰብ አካልየሚወክልና  የእያንዳንዱን ማህበረሰብ አካል  ፍላጎት የሚያሟላ  የሚዲያ አቅርቦት የመስጠት ዓላማ ያለዉ የሚዲያ አሰራር ነዉ።»
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፓሬሽን «ኢቢሲ» ከዚህ የብዙኃን መገናኛ ዘዴወች መርህ አንጻር ሲመዘን እጥረት እንዳለበት ባለሙያዉ አመልክተዉ ምንም እንኳ ተቋሙ በህግ የተቀመጡ ማዕቀፎችና ደንቦች ቢኖሩትም በተጨባጭ ግን  መመዘኛዉን የሚያሟላ ሆኖ ባለሙያዉ አላገኙትም።

በኢትዮጵያ አብዛኛወቹ የመገናኛ ብዙኃን  መንግስትን የመተቸት ሁኔታ  ደካማ ነዉ ያሉት የኮሚኒኬሽን ባለሙያዉ ፤የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተዉ ኮርፓሬሽኑን መተቸታቸዉ የኢትዮጵያን የጋዜጠኝነት ሁኔታ ሊያሻሽል የሚችል አወንታዊ ርምጃ ነዉ ብለዋል።
የምክር ቤት አባላቱን ወቀሳ  የኮርፓሬሽኑ አመራሮች መቀበላቸዉ በዘገባወቹ የተገለጸ ቢሆንም ጉዳዩን በተመለከተ እነሱን ለማነጋገር ያደረግነዉ ጥረት አልተሳካም። 

ፀሐይ ጫኔ

አዜብ ታደሰ