1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትና የኢትዮጵያ የሥነ-ጽሑፍ ሐብት

ሐሙስ፣ ጥቅምት 4 2014

አፍሪቃዉያን በተለያየ ግዜያት የሥነ-ጽሑፍ ኖቤልን አሸንፈዋል። ይህ የአፍሪቃን ብዙ ዓመታት የሥነ-ጽሑፍ ታሪክን ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገባና ሌሎች የአፍሪቃ እንቅስቃሴዎችም በዓለም ትኩረት እንዲያገኙ ይረዳል። የኢትዮጵያ የሥነ-ጽሑፍ ሃብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ እንዴት ማስገባት ይቻል ይሆን?  

https://p.dw.com/p/41fKI
Abdulrazak Gurnah | Gewinner Literaturnobelpreis 2021
ምስል Chapter of Canterbury Cathedral/Reuters

የኢትዮጵያን የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ እንዴት ማምጣት ይቻል ይሆን?

«አፍሪቃዉያን በተለያየ ግዜያት የሥነ-ጽሑፍ ኖቤልን አሸንፈዋል። ዘንድሮም አንድ አፍሪቃዊ ተሸላሚ ተገኝቶአል። ይህ የብዙ ዓመታት የሥነ-ጽሑፍ ታሪክ ያላትን አህጉር አፍሪቃን የሥነ ጽሑፍ ሃብቷ ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ እንዲገባ እና  አፍሪቃ ከስነ-ጥበቡ ዘርፍ በተጨማሪ በሌሎችም እንቅስቃሴዎችም በዓለም ያላትን ትኩረት እንዲጎላ ያደርጋል።»  

በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ፤  ታንዛንያዊው የ72 ዓመቱ ደራሲ፤ አብዱልረዛቅ ጉርናህ የዘንድሮዉን የዓለም የሥነ-ጽሑፍ የኖቤል ሽልማት ማሸነፋቸዉን ተከትሎ የሰጡን አስተያየት ነበር። በየዓመቱ እንደሚደረገዉ ሁሉ፤ ባለፈዉ ሳምንት ሃሙስ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ቀትር ላይ፤ በስቶክሆልም የሚገኘዉ የስዊድኑ ንጉሣዊ የሳይንስ አካዳሚ ሕንጻ ዉስጥ የሚገኘዉ ከባድ የሚመስል ትልቅ በር፤  ስዊድናዊዉ ታዋቂ ደራሲ ማትስ ማለም ከፍተዉ የሚያነቡትን ጽሑፍ ይዘዉ፤ የድምፅ ማጉያ እና መቅረጫ ወዳለበት ቆም ብለዉ፤ ተከታዩን ለዓለም አወጁ።

Äthiopien Kinderbücher in Hawassa
ምስል Shewangizaw Wegayehu/DW

«የ 2021  » የሥነ-ጽሑፍ የኖቤል ሽልማት ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ አሸንፈዋል። በዛንዚባር የወተወለዱት እና በአሁኑ ወቅት ኑሮአቸዉን እንጊሊዝ ያደረጉት ደራሲ ለሽልማት የበቁት የቅኝ ግዛት በባህልና፤ በአህጉር መካከል በስደተኛዉ እጣ ፈንታ ላይ ያሳደረዉን ጉልህ ተጽዕኖ የሚጋፈጡ ሥነ-ጽሑፎችን በማበርከታቸዉ ነዉ።»

ታንዛንያዊዉ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ ምናልባት የሆነ ሰዉ ቀልድ ቀልዶ የሚያታልላቸዉ ስለመሰላቸዉ፤ ነገሩ ቀልድ ነዉ ብለዉ አልተታለልኩም ቢጤ ለማለት ለመልስ ተዘጋጅተዉ እየተጠባበቁ ነበር። በቴሌቭዥን ላይ ቀርበዉ ከስዊድኑ የንጉሳዊ ሳይንስ አካዳሚ የአብዱልራዛቅ ጉርናህን አሸናፊነት ለዓለም ያወጁት ስዊድናዊዉ፤ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ  ጋር ስልክ ደዉለዉ እንኳን ደስ ያሎ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን አሸንፈዋል ብለዉ፤ ሲልዋቸዉ ነዉ ጥቂት እንደማመን ቢጤ የዳዳቸዉ። ከዝያም በተለያዩ የዜና ምንጮች በዜና መልክ መቅረቡን ሲሰሙ፤ እዉነት ለመናገር ይህ ጉዳይ በተለያዩ ጣብያዎች በይፋ መነገሩን እስክሰማ ድረስ ማመን ተስኖች ነበር ብለዋል።

 በሞዕራብ አፍሪቃዊትዋ ቤኒን ታዋቂ የሆነዉ ደራሲ ፍሎሪን ኩዋዞቲ ዜናዉ የአፍሪቃን የኪነ-ጥበብ ዓለም የሚያነቃቃ ነዉ። «ይህ ለመላው አፍሪቃ ኪነ-ጥበባዊ ዓለም ታላቅ ዜና ነው። ሌሎች የአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ ባሞያዎች የእሱን ፈለግ እንደሚከተሉ ተስፋ አደርጋለሁ። ከዚህ ቀደም የናይጀርያዉ ደራሲ፤ ቮለ ሲይንካ ይህን የስነጽሑፍ ኖኔል ሽልማት ሲሸለም ሰማን ዓመት እስኪሞላዉ በጠበቁ ይቆጨናል። የታንዛንያዊዉ ደራሲ ገና የ 20 እና 30 ዓመት እድሜ ክልል ሳለ ጀምሮ በስደት ዓለም ነዉ የሚኖረዉ። ታንዛንያዊ እንደሆነም ነዉ የሚናገረዉ።  በርካታ ጽሑፍንም አቅርቦአል። ሽልማቱን እስኪያገኝ ግን ብዙ ጊዜን ወስዶአል። የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማት ከሰሃራ በታች ካሉ አፍሪቃ ሃገራት መካከል ለሦስተኛ ደራሲ ብዙ ዓመታት ሳንጠብቅ ያገኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።» 

Schweden Stockholm | Bücher von Literaturnobelpreisträger Abdulrazak Gurnah
ምስል Jonathan Nackstrand/AFP/Getty Images

የቶጎዉ ተወላጅ እና በቶጎ በፈረንሳይኛ ሥነ-ጽሑፋቸዉ የሚታወቁት ኮሲ ኢፎይ የዛንዚባሩ ተወላጅ የዘንድዎዉን ሥነ-ጽሑፍ ማሸነፋቸዉ፤ ለአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ እዉነተኛ ማበረታቻ ነዉ ብለዋል። «ይህ ለአፍሪቃ አንባቢዎች መልካም ዜና ነው። ምክንያቱም አፍሪቃውያን አንባቢዎች የአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፎች ለምን በኢንጊሊዘኛ አይተረጎሙም ብለው እራሳቸውን ስለሚጠይቁ ነዉ። እንዳየነዉ ብዙ ጊዜ አይተረጎምም።  ይህ ጉዳይ በእንግሊዝኛ የሌሉ ፈረንሣይ ተናጋሪ ደራሲያን ስራዎችን ይመለከታል። ግን ደግሞ ከሁሉ በላይ በአፍሪቃ ቋንቋዎች የሚጽፉ ብዙ የአፍሪቃዉያን ድርሰቶች አልተተረጎሙም። ይህንን ሽልማት አንድ አፍሪቃዊ ደራሲ ማግኘቱ ለአፍሪቃ ሥነ-ጽሑፍ እውነተኛ ማበረታቻ ነዉ ብዬ አምናለሁ» 

በጎርጎረሳዉያኑ  በ1948 ዓ.ም በታንዛንያዋ ዛንዚባር የተወለዱት ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ በ1960ዎቹ ዓመታት በስደት ወደ ብሪታንያ ከሄዱ በኋላ የከፍተኛ ትምህርታቸዉን እዝያዉ በብሪታንያ አጠናቀዉ ፤ እስከአሁኑ ጊዜ ድረስ  በኬንት ዩንቨርስቲ የእንጊሊዘኛ እና የድሕረ-ቅኝ ግዛት ዘመን ታሪክ አስተማሪ ሆነዉ በማገልገል ላይ ናቸዉ። ወጣቱ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ ወደ ብሪታንያ የተሰደዱት ከዛንዚባር አመጽ እና አብዮት ብሎም ነጻነት በኋላ፤ 21 ዓመት ሲሞላቸዉ ነበር። አብዱልራዛቅ ጉርናህ ቅን ግዛትን ጠቅሰዉ ሥነ-ጽሑፍን የጀመሩት በጣም በወጣትነት እድምያቸዉ እንደሆነ ይነገራሉ።

በሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ተሸላሚዉ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ የቀድሞውን የትውልድ አገራቸዉን ታንዛንያን ደጋግመዉ የሚጠቅሱበት እና የጀርመን እና የእንግሊዝን የቅኝ ግዛት አገዛዝ የሚያወሳ፤ አሥር ልብ ወለዶችን እና በርካታ አጫጭር ታሪኮችን አሳትመዋል። ደራሲ አብዱልራዛቅ የአፍ መፍቻ ቋንቋዋቸዉ የስዋሂሊ ቋንቋ ቢሆንም ፣ ያሳተምዋቸዉ መጽሐፍቶች ሁሉ ግን በእንግሊዝኛ ናቸዉ።

በአፍሪቃ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን ያገኙ አፍሪቃዉያን ከዘንድሮዉ ተሸላሚ ጋር በቁጥር ስድስት ናቸዉ።  ናይጀርያዊዉ ደራሲ ዎሌ ሶይንካ በጎርጎረሳዉያኑ 1986 ዓ.ም ሽልማቱን ወስዶአል። በጎርጎረሳዉያኑ 1988 ዓመት፤ ግብጻዊዉ ናጉብ ማፎዝ ተሸላሚ ነበር። በጎርጎረሳዉያኑ 1991 ነጭዋ ደቡብ አፍሪቃዊት ፀሐፊ በመባል የምትታወቀዉ ናዲን ጎርድሜር የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ሽልማትን ተቀብላለች። 2003  ዓመት ደቡብ አፍሪቃ የተወለደዉ ነጩ አፍሪቃዊ ጆን ማክስዌል ኮቲዝ የሥነ-ጽሑፍ ኖቤል ተሸላሜ ነበር። በ 2008 ደግሚሞ የሞሪታንያ እና የፈረንሳይ ዜንግነት ያለዉ ደራሴ በሥነ-ጽሑፎቹ ኖቤልን አግኝቶአል። ዘንድሮ ያዉ በዛንዚባር የተወለዱት አብዱልራዛቅ ጉርናህ ተሸላሚ ናቸዉ። በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ፤ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ፤ ሽልማቱ ዳግም ወደ አፍሪቃ መምጣቱ ትልቅ ትርጉም እንዳለዉ ተናግረዋል።

Äthiopien Gelan Schulbuch Druckerei
ምስል Seyoum Getu/DW

ኢትዮጵያ በጣም ግዙፍ የሆነ የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ያላት ሃገር ናት። እና ይህን የሥነ-ጽሑፍ ሐብት ወደ ዓለም አቀፉ መድረክ ለማምጣት ምን አይነት ጥረት እየተደረገ መሆኑንም በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ዉስጥ መጽሐፍን የማንበብ ባህል እየተበረታታ እና እየተጠናከረ መሆኑን በአዲስ አበባ የሆሄ የሥነ- ፅሑፍ ሽልማት አዘጋጅ አቶ ኤፍሬም ብርኃኑ ተናግረዋል። ነገር ግን መጽሐፍን ለማሳተም የህትመት ዋጋ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ የዘርፉን እንቅስቃሴ እንዳይጎዳዉ የሚል አስተያየትም አለ። በዚህም በህትመት አኳያ መንግሥት እርዳታ እንዲያደርግ ጥያቄ ቀርቦአል።     

በስዊድናዊዉ የኬምስትሪ ልሂቅና አዲስ ነገር ፈጣሪ በአልፍሪድ ኖቤል ስም የተሰየመዉና፤ በሞተበት በጥቅምት ወር የስዊድኑ የንጉሳዊ ሳይንስ አካዳሚ ሽልማት መስጠት የጀመረዉ ከጎርጎረሳዉያኑ 1901 ዓመት ጀምሮ እንደሆነ ጽሑፎች ያሳያሉ። በብሪታንያ ነዋሪ የሆኑት የዘንድሮዉ የሥነ-ጽሑፍ  ኖቤል አሸናፊ ደራሲ አብዱልራዛቅ ጉርናህ፤ በያዝነዉ የጎርጎረሳዉያን ዓመት 2021 ዓመት መጨረሻ ላይ ከንጉሳዊዉ የሳይንስ አካዳሚ፤ 10 ሚሊዮን የስዊድን ክሮን ወይም ወደ አንድ ሚሊዮን ዶላር ይቀበላሉ።

Abdulrazak Gurnah | Gewinner Literaturnobelpreis 2021 | Buchcover
ምስል AFP via Getty Images

ከዛንዚባር የመጡት አብዱልራዛቅ ጉርናህ የዘንድሮዉን የሥነ-ጽሑፍ ሽልማት ማግኘታቸዉን የሰሙት በካሜሩን ታዋቂዉ ደራሲ ኤጉኔ አቦዴ ለሽልማቱ አፍሪቃዉያን ልንደሰ ልንኮራ ይገባል ብለዋል። "ለዚህ ድንቅ ሽልማት እና ክብር በመብቃታቸዉ አብዱልረዛቅ ጉርናንን እንኳን ደስ አሎት እላለሁ! አፍሪቃ ስትሸለም ማየት ሁሌም ትልቅ ክብር ነው። በአፍሪቃ ከሰሜን እስከ ደቡብ ፣ ከምስራቅ እስከ ምዕራብ ያለን ሁሉ ዜጎች ሁሉ በሽልማቱ ደስተኞች መሆን አለብን!" 

የኢትዮጵያን የሥነ-ጽሑፍ ኃብት በዓለሙ መድረክ እንዲነበብ ምን እናድርግ ሃሳብ አሎ? አስተያየቶን ይስጡን። ቃለ ምልልስ የሰጡንን በዶቼ ቬለ ስም እናመሰግናለን።

ሙሉዉን ዝግጅቱን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን ተጭነዉ እንድያደምጡ እንጋብዛለን! 

 

አዜብ ታደሰ

ኂሩት መለሰ