1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ጉብኝት በኢትዮጵያ 

Merga Yonas Bula
ሰኞ፣ ሚያዝያ 15 2010

የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ዘይድ ራአድ አል ሁሴን በኢትዮጵያ ያለዉን የሰብዓዊ መብት አያያዝን በተመለከተ የአራት ቀን ጉብኝታቸዉን ትናንት ጀምረዋል።

https://p.dw.com/p/2wWeJ
Diplomat Zeid Ra'ad al-Hussein
ምስል Reuters/P. Albouy

Human Rights chief visit to Ethiopia - MP3-Stereo

በዛሬው ዕለትም ከኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት በቀረበላቸዉ ግብዣ መሰረት ኮሚሽነሩ በክልሉ ያለዉ የሰብዓዊ መብት ጉዳዩች ላይ እስካሁን የተሰጠዉን መፍትሄ በተመለከተ መወያየታቸዉን ቃል አቀባያቸው ራቪና ሻምዳሳን ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል።

ኮሚሽነሩ በነገው ዕለትም በአፍሪቃ ሕብረት ተገኝተዉ በከፍተኛ ደረጃ የተዘጋጀ ውይይት እንደሚያደርጉ፤ በአዲስ አበበ ዩኒቨርሲቲም ሰብዓዊ መብትን በተመለከተ ለተማሪዎች ማብራሪያ እንደሚሰጡ ሻምዳሳን ተናግረዋል። ረቡዕ ዕለት ደግሞ ከሲቪል ማሕበራት መሪዎች፤ እንዲሁም ከጠቅላይ ሚኒስትሩና ከከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር እንድሁም በቅርቡ ከእስር ከተፈቱ ታዋቅ ግለሰቦች ጋር እንደሚገናኙም ቃል አቀባይዋ አክለው አመልክተዋል።

በቅርብ ከእስር የተፈቱትና የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግረስ /ኦፌኮ/ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ጉዲና በበኩላቸው ከኮሚሽነር ዘይድ ጋር እንደሚገናኙ መረጃ ቢደርሳቸዉም መቼና የት እንደሆነ ምንም ዝርዝር እንዳልደረሳቸዉ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። ግን ከኮሚሺነሩ ጋር ከተገናኙ ሊወያዩባቸው ያቀዷቸው ነጥቦች እንዳሏቸዉ አክለዉ ገልፀዋል።

Äthiopien  Dr Mererra & Medrek
የኦፌኮ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ጉዲና ምስል DW/Yohannes G. Egziabher

እንደ አዉሮጳያኑ አቆጣጠር በ2016 በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች ዉስጥ የመንግሥት የፀጥታ አካላት ከመጠን ያለፈ ኃይል ተጠቅመው በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ የወሰዱት ርምጃ በገለልተኛ አካል መጣራት እንደሚገባው ኮሚሽነሩ ማሳሰባቸዉ ይታወሳል። ይሁን እንጂ እስካሁን በተጨባጭ የታየ ነገር የለም። ኮሚሽነሩ አቅርበው የነበረውን የሰብዓዊ መብት አያያዝ ምርመራ ጉዳይ በዚህ ጉብኝታቸዉም እንደሚያነሱ ቃል አቀባይዋ ራቪና ሻምዳሳን ለዶይቼ ቬሌ አስረድተዋል።

ራቪና፤ «ከፍተኛ ኮምሽነሩ በተለያዩ አገራት ጉብኝት ሲያደርጉ እንደሚያነሱት ሁሉ አሁንም በሰብዓዊ መብት ላይ ያለዉን ስጋት ለባለስልጣናት ያነሳሉ። ከሲቪል ማህበራት ጋር እየተነጋገረን ነዉ። እነሱም ያለዉን ጉዳይ ተረድተዋል። እኛም የራሳችን ትንተና አለን። ኮሚሽነሩ በመጨረሻ ጉብኝታቸዉም ሁሌ የሚያደረጉት ንግግር አለ። ንግግሩም ከመንግሥት ባለስልጣናት ጋር ያነሳነዉን፣ መልሳቸዉንና ለወደፊት ከነሱ የምንጠብቀዉን ጉዳዮች ያጠቃልላል። በጉብኝቱ ማጠቃለያም አንተ እንዳነሳኸዉ በብዙ የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ላይ እንወያያለን።»

Ravina Shamdasani , Sprecherin UNHCR
ራቪና ሻምዳሳንምስል UNHCR Presse Büro

የሰባዓዊ መብት ጥሰት በገለልተኛ አካል ይጣራ የሚለዉ ለብዙ ዓመታት ዶክተር መረራም ሲጠይቁ የነበረ መሆኑን ተናግረዉ ግን ደግሞ ለመንግሥት እስካሁን እንዳልተዋጠለት አክለውበታል።

በዚህ ጉዳይ ላይ በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ባካሄድነው ዉይይት አብዛኞቹ የዶይቼ ቬሌ ተከታታዮች ከኮሚሽነሩ ጉብኝት ብዙ ተስፋ እንደሌላቸዉ በዋትስኣፕ ላይ የላኳቸው የፅሁፍ አስተያየቶች ያመለክታሉ። ለምሳሌ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በገለልተኛ አካል ይጣራ የሚለዉ ላይ መንግሥት ፍቃደኛ ያልሆነበት ምክንያት «ብዙ ዜጎችን በማን አለብኝነት ስለጨፈጨፉ ፣ መቸም ቢሆን እሽ አይሉም» የሚል አስተያየት ጽፈዋል። ሁለት ግለሰቦች ደግሞ የሚከተለዉን አስተያየት አስፍረዋል፤ «ኮሚሽነሩ መምጣታቸው ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ህዝብ ብሶቱን የት ነው ማሠማት የሚችለው? ኮሚሽነሩ በከፍተኛ ባለስልጣናት ታጅቦ ነው ቤተ መንግሥት የሚጋበዘው» ስለዚህ «የሚጠበቀው የምኒልክን ቤተመንግሥት እንደተለመደው ጎብኝቶ መውጣት ነው»።

ሙሉ ዘገባዉን ለማዳመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሰ