1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሳህል አካባቢ ሀገራት እና ፀረ ሽብር ጦራቸው

ረቡዕ፣ ሰኔ 28 2009

አምስት የሳህል አካባቢ ሀገራት አንድ ድንበር ተሻጋሪ ፀረ ሽብር ጦር ለማቋቋም ወሰኑ። አውሮጳ ሀሳቡን ደግፋዋለች። ይሁንና፣ ጠበብት እንደሚሉት፣ ማሊ፣ ሞሪታንያ፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ኒዠር እና ቻድ  በሚገኙበት የሳህል አካባቢ የሚታዩትው ውዝግቦች ሁሉ በወታደራዊ ኃይል ብቻ መፍትሄ አያገኙም።

https://p.dw.com/p/2fzuX
Mali Bamako Armee
ምስል picture-alliance/dpa/M. Kappeler

G5-Sahel-Gruppe: Mehr als nur Militär - MP3-Stereo

ሰሜናዊ ማሊ ባካባቢው ለሚታየው ቀውስ ማዕከል መሆኗ ይነገራል። ሙስሊም ጽንፈኞች በጎርጎሪዮሳዊው 2012 ዓም አካባቢውን ለአስር ወራት ተቆጣጥረውት ነበር።  የማሊ መንግሥት በፈረንሳይ እና አፍሪቃውያን ጦር ኃይላት ድጋፍ ካገኘ በኋላ ነበር አካባቢውን መልሶ መቆጣጠር የቻለው። ከዚያን ጊዜ ወዲህ  በምህጻሩ «ሚኑስማ» የተባለው 11,000 ወታደሮች እና 1,500 ፖሊሶች ያጠቃለለው የተመ ሰላም አስከባሪ ተልዕኮ ባካባቢው ተሰማርቷል፤ የአውሮጳ ህብረትም ለማሊ ጦር የስልጠና ርዳታ ይሰጣል። ከዚህ በተጨማሪም 3,000 ወታደሮች የያዘው እና በፈረንሳይ የሚመራው  ግብረ ኃይል «ቡርካኔ» ቡድን ካለፉት ሶስት ዓመታት ወዲህ በአምስቱ የሳህል አካባቢ ሀገራት፣ ሞሪታንያ፣ ማሊ፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ኒዠር እና ቻድ በሚንቀሳቀሱ ዓማፅያን አንጻር ትግል ያካሂዳል።
ይሁን እንጂ፣ አካባቢው አሁንም አልተረጋጋም፣ በአንጻሩ፣ የተመድ ከጥቂት ጊዜ በፊት ያወጣው ዘገባ እንደሚያሳየው፣ የኃይሉ ተግባር በሰሜናዊ ማሊ ተስፋፍቷል፣ ከማሊም አልፎ  አዘውትሮ ወደ ጎረቤት ሀገራት ተዛምቷል።.
ባለፈው የሳምንት መጨረሻ በማሊ መዲና ባማኮ ከፈረንሳይ ፕሬዚደንት ኤማኑዌል ማክሮ ጋር ጉባዔ ያካሄዱት የአምስቱ የሳህል አካባቢ ሀገራት መሪዎችይህን የኃይል ተግባር በማስቆሙ ተግባር ላይ የሚረዳ 5,000 ወታደሮች የሚያሰልፍ አንድ የአፍሪቃውያን አጥቂ ቡድን ለማቋቋም ወስነዋል። 
የአውሮጳ ህብረት ለዚሁ አጥቂ ቡድን 50 ሚልዮን ዩሮ  ፣ «ጂ 5»  እያንዳንዳቸው አስር ሚልዮን ፣ ፕሬዚደንት ማክሮ ደግሞ ስምንት ሚልዮን ለመስጠት ቃል ገብተዋል፣ ይህ ግን አንድ አራተኛውን ብቻ ነው የሚሸፍነው በመሆኑ፣ ቀሪውን በተመድ ለማስሽፈን ፈረንሳይ ያደረገችው ሙከራ ከሽፏል። እርግጥ የተመድ እቅዱን ቢያሞግስም፣ ርዳታ ለመስጠት ቃል ከመግባት ተቆጥቧል። ምክንያቱም በፕሬዚደንት ትራምፕ የምትመራ ዩኤስ አሜሪካ ውድ የምትላቸውን የተመድ ሰላም ተልዕኮዎች የሚመለከቱ ውሳኔዎችን አትደግፍም።
እስከ መጪው መስከረም ወር ድረስ ስራውን  መጀመር አለበት የሚባለው ይኸው የሳህል አካባቢ ሀገራት ቡድን ፣ እንደ በለንደን የሚገኘው «ቻተም ሀውስ » የተባለው የፖለቲካ ተቋም ተንታኝ ፖል ሜሊ አስተሳሰብ፣ ትልቅ ሚና ይኖረዋል።
« ጽንፈኞች የሀገራት ድንበሮችን እየተሻገሩ በርካታ ጥቃት ይፈጽማሉ። ይህ በመሆኑም፣ አሁን ይቋቋማል የሚባለው ድንበር ተሻግሮ ጥቃት የማካሄድ ስልጣን የሚኖረው ቡድን ባካባቢው የፀጥታ ጥበቃ ላይ ለሚታየው ችግር መፍትሄ ለማስገኘት ቁልፍ ሚና ይጫወታል። »
ሆኖም ፣ ባካባቢው መረጋጋት ለማውረድ ፣ ፒተር ማሊ የተወሳሰቡ የሚሏቸውን  ችግሮች፣ ለምሳሌ፣  ባካባቢው የሚታየውን ድህነት እና መንግሥታቱ ደካማ የሆኑበትን ድርጊት መታገል አስፈላጊ ይሆናል።
በድርቅ እና በበረሀማነት መስፋፋት ሰበብ ከማሊ ሕዝብ መካካ,ል አንድ አምስተኛው ረሀብ አስግቶታል። አክራሪ ሙስሊሞች እና የተደራጀው ሕገ ወጡ  የጦር መሳሪያ፣ አደንዛዥ ዕፅ እና የሰው ዝውውር ሁኔታውን አባብሶታል።
« ጠንካራ የልማት እንቅስቃሴ የማይኖርበት ሁኔታ ፣ የፖለቲካ መረጋጋት ሊኖር የሚችልበትን አጋጣሚ፣ እንዲሁም፣ ሰዎች ወደ ሽብርተኝነት እንዳይሳቡ እና ታጣቂ ቡድኖችን የሚቀላቀሉበትን ስጋት ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት መና ያስቀራል።  »  
ይህ እንዳይሆን የችግሮቹን መንስዔዎች ማስወገድ የሚያስችል ስልት ማውጣት ወሳኝ መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞች ያምናሉ።

Gipfeltreffen in Bamako Mali
ምስል Reuters/L. Gnago
Karte Infografik G5 Sahelzone

አርኒ ኩዎፓሜኪ/አርያም ተክሌ

ሂሩት መለሰ