1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሳዑዲ ተመላሾች ምሬት

ሰኞ፣ ግንቦት 28 2009

ሳዑዲን ለቀን ወደ ሀገራችን አንመለስም የሚሉት እና የሳዑዲን እርምጃ ለመጋፈጥ የቆረጡት በርካቶች የለም ወደሀገራችን እንግባ ብለው ቀኑ ከገፋ በኋላም ቢሆን የመጓጓዣ ሰነድ ለመውሰድም ሆነ የዘረ-መል ምርመራ ውጤታቸውን ባለመቀበላቸው የተማረሩ ኢትዮጵያዊን ቅዳሜ ማለዳ የሪያዱን የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር አጨናንቀውት ነበር፡

https://p.dw.com/p/2e8Q1
Äthiopische Rückkehrer aus Saudi-Arabien
ምስል DW/S.Shibru

Beschwerden äthiopischer Rückkehrer in Riyadh - MP3-Stereo

በርካታ ከሳዑዲ ተመላሽ ኢትዮጵያዊያን በጉዞ ሰነድ አሰጣጥም ሆነ የዘረ መል ወይንም ዲኤን ኤ ውጤት መዘግየት ሳቢያ እየተንገላቱ መሆኑን በምሬት ይናገራሉ፡፡ የሳዑዲ መንግስት የሰጠው የ90 ቀን የምህረት ጊዜ ሊጠናቀቅ 23 ቀናት ብቻ ቀርተውታል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት  12 አባላት ያሉት ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች የሚገኙበት የልዑካን ቡድን ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ልኳል፡፡ የልዑካን ቡድኑን የሚመሩት አምባሳደር ጊፍቲ አባሲያ እንደሚሉት ከሰሞኑ መልካም ለውጦች ተገኝተዋል፡፡ የመጣው ይምጣ እንጂ ሳዑዲን ለቀን ወደ ሀገራችን አንመለስም የሚሉት እና መጪውን የሳዑዲ መንግስት እርምጃ ለመጋፈጥ የቆረጡት በርካቶች ቀርተው የለም ወደሀገራችን እንግባ ብለው ቀኑ ከገፋ በኋላም ቢሆን የመጓጓዣ ሰነድ ለመውሰድም ሆነ የዘረ-መል ምርመራ ውጤታቸውን ባለመቀበላቸው የተማረሩ ኢትዮጵያዊን ቅዳሜ ማለዳ የሪያዱን የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ማህበር አካባቢውንም ሆነ አዳራሹን አጨናንቀውት ነበር፡፡ አብዛኞቹም በኢትዮጵያ ኤምባሲም ሆነ በሳዑዲ መንግስት አሰራር መማረራቸውን ይገልጻሉ፡፡ወይዘሮ ሳዓዳ የሁለት ልጆች እናት ናት የ3 እና የአንድ ዓመት ናቸው ፡፡ ባለቤቷ ቀድሞ ሀገር እንደገባ ትናገራለች፡፡

«የምህረት አዋጁ እንደተጀመረ የልጆቼን ዲኤን ኤ ወይንም ዘረ መል ለምርመራ ሰጥቼ ይሄው እስካሁን ከ1 ወር በላይ ሆነ በየቀኑ እቀጠራለሁ፣እመላለሳለሁ ውጤት የለውም፡፡

Äthiopische Rückkehrer aus Saudi-Arabien
ምስል DW/S.Shibru

ቶሎ አልቆልኝ የምሄድ መስሎኝ ኪራይ ቤቴን ለቅቄ ሰው ቤት ነው ያለሁት ቶሎ አልቆልኝ የምሄድ መስሎኝ ስራዬንም ለቀኩኝ፡፡ ከሁለቱም ሳልሆን ልጆቼን በችጋር እየፈጀሁ ነው፡፡»

የኢትዮጵያ መንግስት በኤምባሲው በኩል የሚካሄደውን የመውጫ ሰነድ የመስጠት ሂደቱን እንዲያቀላጥፉ በሚል በአምባሳደር ጊፍቲ አባሲያ የሚመራ 12 የመንግስት የስራ ኃላፊዎች የተካተቱበት የልዑካን ቡድን ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ልኳል፡፡ ስድስቱ በሪያድ ስድስቱ በጂዳ ድጋፍ እየሰጡ ናቸው፡፡ የልዑካን ቡድኑን የሚመሩት አምባሳደር ጊፍቲ አባሲያ እንደሚናገሩት የችግሩን ስፋትና መጠን ከተረዱ በኋላ በመፍትሔዎቹ ዙሪያ ቀን ከሌት እየሰሩ ናቸው፡፡ አምባሳደር ጊፍቲ እንዳረጋገጡት ከትላንት በስቲያ እንደተጀመረውም የዘረ መል ምርመራ ውጤት ሰጥተው የዘገየባቸው ዜጎች ኤምባሲው ዋስትናውን ወስዶ የልጆቻቸውን ኢትዮጵያዊነት ማረጋገጫ እየሰጠ ከሳዑዲ የሚወጡበት መንገድ ተጀምሯል፡፡ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በተደረገ ስምምነትም ከነገ ጀምሮ ትላልቅ ኤሮፕላኖች በመመደብ እና ተደጋጋሚ በረራዎችን በማድረግ ዜጎችን የማጓጓዝ ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ይፋ ሆኗል፡፡ አድሃኖም የጎንደር ዩኒቨርስቲ ጤና መኮንን ምሩቅ ነው፡፡ በቀይ ባህር በኩል ወደ ሳዑዲ ከተሰደዱት ኢትዮጵያዊያን አንዱ ነው፡፡ባለፉት ሶስት ዓመታት በሳዑዲ ዓረቢያ በጉልበት ሰራተኛነት ቆይቷል፡፡ ለስደቱም ሆነ ለእንግልቱ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጣቱን ይቀስራል፡፡ያም ሆነ ይህ የሳዑዲ መንግስት የሰጠው የዘጠና ቀን የምህረት ጊዜ ቁልቁል ተንደርድሮ 23 ቀን ብቻ ቀርተውታል፡፡ ባለፉት 67 የምህረት ቀናት ወደ ሀገር የገቡት ዜጎች ቁጥር ከቀሩት ጋር ሲነጻጸር አሁንም እጅግ ኢምንት ናቸው፡፡

ስለሺ ሽብሩ

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ