1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሶማሊያ ሰሞናዊ ሁኔታ

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 7 2002

አብዛኛዉ የርዕሠ-ከተማይቱ ነዋሪ ሕይወቱን ለማትረፍ ሸሽቷል።የሠላም ተስፋ ግን ሞቃዲሾም፥ ነዋሪዋ ሸሽቶ የሠፈረበት ሥፍራም ሶማሊያ ምድር የትም የለም።ሌላ አመት-ሌላ ፅልመት

https://p.dw.com/p/Mwxh
ሞቃዲሾ ገፅታ-አንድምስል AP

የሶማሊያ አክራሪ ደፈጣ ተዋጊ ቡድናት አል-ሸባብና ተባባሪዎቹ ባዘዙት መሠረት ከርዕሠ-ከተማ ከሞቃዲሾ የሚያሠራጩ የግል ራዲዮ ጣቢያዎች ሙዚቃ ማጨወት አቆሙ።የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ አሜሪካ ዉስጥ የሚገኝ የአል-ሸባብና የተባባሪዎቹ ሐብትና ንብረት እንዲታገድ አዘዋል።ባለፈዉ ሰኞ-እና ማክሰኞ ሞቃዲሾ ዉስጥ ይደረግ የነበረዉ ዉጊያ ትናንት እና ዛሬ ጋብ ብሏል።በራዲዮ ጣቢያዎቹ ላይ የተጣለዉን እገዳ፥የዩናይትድ ስቴትስን እርምጃ ዉጤት እና የሞቃዲሾዉን ዉጊያ በተመለከተ ነጋሽ መሐመድ በሶማሊያ የዶቸ ቬለ ተባባሪ ዘጋቢ ሙስጠፋ ሐጂ ኑርን አነጋግሮ የሚከተለዉን ዘገባ አጠናቅሯል።

የአል-ሸባብና የተባባሪዎቹ አክራሪ ሐይላት ቀደመዉ በተቆጣጠሯቸዉ በደቡብ እና፥በማዕከላዊ ሶማሊያ-አካባቢያዊ ራዲዮ ጣቢያዎችና ጋዜጠኞች ላይ ያደረጉትን ሲያደርጉ የመቅዶሾዎቹ ብጤዎቻቸዉ መቼን-እንጂ የባልደረቦቻቸዉ እጣ እንደሚደርሳቸዉ በርግጥ አላጡትም ነበር።ሙስጠፋ ሐጂ ኑርም ጋዜጠኛ ነዉ።ያዉቀዋል።
«አል-ሸባብ ሙሉ በሙሉ በሚቆጣጠረዉ በደቡባዊ ሶማሊያ የሚገኙ አካባቢያዊ ራዲዮ ጣቢያዎችን ቀደም ሲል ዘግተዋቸዋል።እስካሁን ድረስ ከተፅዕኖ ጋርም ቢሆን ይሠሩ የነበሩት ሞቃዲሾ የሚገኙት ራዲዮ ጣቢያዎች ነበሩ።»

የሞቃዲሾ ጋዜጠኛ-ራዲዮ ጣቢያዎች ከተፅዕኖ ጋር መቼን እየጠየቁ፥ የሶማሊያ፥ የኢትዮጵያ፥ የኪስዋሒሊ፥ የድፍን አፍሪቃዉ፥የአዉሮጳ አሜሪካዉንም ሙዚቃ ያንቆረቁርት ነበር።ባለፈዉ ሳምንት ማብቂያ ግን አሳሳቢዉ ጥያቄ አስፈሪ-መልስ አገኘ።አሽባብ ሐይማኖት ጋር አብሮ የማይሔድ ያለዉን ሙዚቃ ራዲዮ ጣቢያዎቹ እንዳያጫዉቱ አዘዘ።የታዘዙትን ካለደረጉ-የሚደርስባቸዉን የሚያዉቁት ጋዜጠኞች ሙዚቃዉን ፀጥ።

«(ማስጠንቀቂያዉ) የሶማሊያን ነፃ መገናኛ ዘዴ በተለይም የአካባቢያዊ ራዲዮ ጣቢያዎችን ክፉኛ ነዉ-የጎዳዉ።ሁሉም እየተሰማዉ ነዉ።ራዲዮ ጣቢያዎቹ ምንም አይነት ሙዚቃ አያጫዉቱም።ይሕ እስላማዊ ፅንፈኞች የሐገሪቱን ነፃ መገናኛ ዘዴዎች ለመደፍለቅ ከሚወስዷቸዉ እርምጃዎች አንዱ ነዉ።»

Somalia Mogadischu Islamisten Flüchtlinge
ሞቃዲሾ ገፅታ-ሁለትምስል picture-alliance/dpa

ርዕሠ-ከተማ ሞቃዲሾ-አስራ አራት የግል ወይም ነፃ ራዲዮ ጣቢያዎች አሉ።ሁሉም ቢያንስ ሙዚቃንንና ሥለሙዚቃ አቆሞ። ቤተ-መንግሥት አጠገብ የምትገኘዉ የሽግግር መንግሥቱ ራዲዮ ጣቢያ ግን አሁንም ጭል፥ ጭል ማለትዋን ቀጥላለች።በምዕራባዉያን የሚደገፈዉ የሽግግር መንግሥት የራዲዮ ጣቢያዎቹን ቀርቶ የራሱንም ሕልዉና ማስከበሩ በሚያጠራጥርበት መሐል-ነዉ የዩናይትድ ስቴትሱ ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ አሜሪካ የሚገኝ የአል-ሽባብና የአስራ-አንድ ደጋፊዎቹ ሐብት ንብረት እንዲታገድ ያዘዙት።

እገዳዉ ግን ጋዜጠኛ ሙስጠፋ ሐጂ እንደሚያምነዉ የሶማሊያን ሁኔታ ለመቀየር የሚተክረዉ የለም።ካለም ኢምንት ነዉ።

«እንደሚመስለኝ የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናት ባወጡት ዝር ዝር በጠቀሷቸዉ ግለሰቦች ላይ የተወሰደዉ እርምጃ እዚሕ (ሶማሊያ) ባለዉ ሁኔታ ላይ የሚያሳድረዉ ተፅዕኖ በጣም ትንሽ ነዉ።ምክንያቱም የዩናይትድ ስቴትስ (ባለሥልጣናት) ከአል-ቃኢዳ ወይም አሸባሪ ከሚሏቸዉ ቡድናት ጋር ግንኙነት አላቸዉ የሚሏቸዉን ወገኖች ንብረት ሲያግዱ ያሁኑ የመጀመሪያዉ አይደለም።ከዚሕ ቀደም አቡ መንሱርና አቡ ዙቤርን ጨምሮ የአል-ሸባብን ትላልቅ ባለሥልጣናትና ደጋፊዎችን ንብረት አግደዋል።(እርምጃዉ) ሶማሊያ ዉስጥ ምንም አላመጣም።እና የተጠቀሱት ብዙዎቹ ሰዎች በዩናይትድ ስቴትስ እገዳ የሚደርስባቸዉ ነገር የለም።ምክንያቱም ሐብታም አይደሉም።ነጋዴዎች አይደሉም።ሚሊየነሮች አይደሉም።»
ሞቃዲሾ-ያዉ እንደኖረችበት በመድፍ-አዳፍኔ አረር ታርራለች።በተለይ ከትናንት በስቲያ፣-ይቀጥላል ሙስጠፋ።

«ከትናንት በስቲያ ለሞቃዲሾ ከበጣም መጥፎቹ ቀናት አንዱ ነበር።የእስላማዊ ሐይሎችና በአፍሪቃ ሕብረት ወታደሮች የሚታገዘዉ የሶማሊያ መንግሥት ጦር በመድፍና አዳፍኔ ሲዋጉ ነበር።እንደ ሁል ጊዜዉ የዉጊያዉ ዋነኛ ተጎጂ ሰላማዊ ሰዎች ናቸዉ።በሰሞኑ ግጭትም ከሃያ የሚበልጡ ሰዎች ተገድለዋል።ከስልሳ በላይ ቆስለዋል።ሥለዚሕ አሁንም ከርዕሠ-ከተማይቱ ለቀዉ ላልወጡት ጥቂት ቤተሰቦች ምንም ተስፋ የለም።»

Somalia Mogadischu Flüchtlinge Flash-Galerie
እና ስደትምስል AP

አብዛኛዉ የርዕሠ-ከተማይቱ ነዋሪ ሕይወቱን ለማትረፍ ሸሽቷል።የሠላም ተስፋ ግን ሞቃዲሾም፥ ነዋሪዋ ሸሽቶ የሠፈረበት ሥፍራም ሶማሊያ ምድር የትም የለም።ሌላ አመት-ሌላ ፅልመት።ሶማሊያ አስራ ዘጠኝ አመት አለች።

ነጋሽ መሐመድ
አርያም ተክሌ