የሶማሊያ ሰብአዊ ቀውስ
ሰኞ፣ ሐምሌ 16 2004በጦርነት በተመሰቃቀለችው ሶማሊያ ዘንድሮ ረሃብ አያሰጋም ። ይሁንና አሁንም ቢሆን ከ 2.5 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቿኳይ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው የተባበሩት መንግሥት ድርጅት አስታውቋል ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ እርዳታዎች አስተባባሪ ቢሮ በምህፃሩ OCHA ሃላፊ ማርክ ቦውደን ለዶቼቬለ የአማርኛው ክፍል በሰጡት ቃለ መጠይቅ በሶማሊያ በቂ ዝናብ ባለመጣሉ አሁንም ሰብዓዊው ቀውስ ቀጥሏል ። ያነጋገረቻቸው ሂሩት መለሰ ተከታዩን ዘገባ አጠናቅራለች ።ባለፈው ዓመት ሶማሊያን የመታት አስከፊ ድርቅና የርስ በርሱ ጦርነት ያስከተለው ረሃብ በ10 ሺዎች የሚቆጠር ህዝብ ህይወት አጥፍቷል ። ይህ አስከፊ ረሃብ በዚህ ዓመት አጋማሽ ግድም ማብቃቱ ታውጇል ። ይሁንና አሁን በሶማሊያ ሁኔታዎች እንደገና ወደ አሳሳቢ ደረጃ እንዳይሸጋገሩ ያሰጋል ። ባለፈው ሳምንት ሶማሊያን የጎበኙት የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ እርዳታዎች አስተባባሪ ቢሮ ሃላፊ ማርክ ቦውደን ለዶቼቬለ የአማርኛው ክፍል በሰጡት ቃለ ምልልስ እንዳሉት አሁንም ለሶማሊያ አስቸኳይ እርዳታ ያስፈልጋታል።« በሶማሊያ አሁንም ሰብዓዊ ቀውስ አለ ። ሶማሊያ ካለፈው ዓመቱ አሰከፊ ረሃብ አገግማለች ሆኖም የዘንድሮው ዝናብ ከተጠበቀው ያነሰ ነው ። በዚህ ሳቢያም ዝናብ ካጠረባቸው አንዳንድ አካባቢዎች ሰዎች እየለቀቁ መሆናቸውን አይቻለሁ ። በተጨማሪም ውጊያውንና ግጭቱን እየፈሩ በመሸሽ ላይ ናቸው ። ስለዚህ አሁንም እጅግ አፋጣኝ እርዳታ የሚያስፈልገው ህዝብ አለ ።»ከሁሉም ችግሩ የሚያሳስበው በደቡብ ሶማሊያ ነው ። የአፍሪቃ ህብረትና የኢትዮጵያ ሠራዊት ከአሸባብ ጋር የሚዋጉበት ይህ አካባቢ የዝንብ እጥረት አጋጥሟታል ። በዚህ ምክንያትም ቦውደን እንዳሉት በመጪዎቹ 6 ወራት የተረጂው ቁጥር ከፍ ሊል ይችላል ። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች አሁንም አስቸኳይ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል ።«በ 6 ወራት ውስጥ ረሃቡን ለመቋቋም ችለናል ። በዚህ ዓመት ከጥር ወር በኋላ ረሃብ አልነበረም ። ይህ ማለት የምግብ ቀውስ አልነበረም ማለት አይደለም ። 2.5 ሚሊዮን ሰዎች አሁንም አስቸኳይ እርዳት የሚያስፈልጋቸው ናቸው ። እነዚህም የምግብ እጥረትና የሞት መጠን ከፍተኛ በሆነባቸው አካባቢዎች የሚገኙ ናቸው ። »ባለፈው ዓመት ሶማሊያ ረሃብ እንደሚያሰጋት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ቅድመ ማስጠንቀቂዎችን ሰጥተው ነበር ። ይሁንና ለጋሾች ይህን ማሰጠንቀቂያ ችላ በማለታቸው ለህዝቡ መድረስ የተቻለው ረሃቡ ከተከሰተ በኋላ ነው ። አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች እንደሚሉት ማስጠንቀቂያው ትኩረት ተስጥቶት ቢሆን ኖሮ የሶማሊያውን ረሃብ አስቀድሞ መቋቋም በተቻለ ነበር ። ታዲያ ለጋሾች ከዚህ ተሞክሮምን ትምህርት ወስደው ይሆን ?« እንደሚመስለኝ ለጋሾች ከዚህ ትምህርት ወስደዋል ባለፈው ዓመት አጋማሽ ላይ ለቀረበላቸው ጥሪ በጥሩ ሁኔታ ምላሽ ሰጥተዋል ። ካለፈው ዓመት አጋማሽ አንስቶ እስከዚህ ዓመት አጋማሽ ድረስ እርዳታውን መቀጠል ችለናል ። ወደ 500 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልገናል ።ለጋሾች ሁኔታው ከባድ መሆኑን ተገንዝበው በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ የጀመሩትን ሥራ ከጫፍ ያደርሳሉ ብዮ ተስፋ አደርጋለሁ »ለሶማሊያ ህዝብ ታስቦ የሚላከው እርዳታ በቀጥታ ለተረጂው እንዳይደርስ ልዩ ልዩ መሰናክሎች ያጋጥማሉ ። ለዚህ አስተዋፅኦ ያደርጋሉ ከሚባሉት ውስጥ ሙስና አንዱ ነው ። ይህና የመሳሰሉትን ችግሮች ለማስወገድ የእርዳታ ድርጅቶች የሚከተሉት አሰራር ምን ይመስላል « የእርዳታ ድርጅቶች ምግብ ለተረጂዎች የሚያደርሱባቸው የተለያዩ መንገዶች ቀይሰዋል ። እንደሚመስለኝ የዓለም የምግብ ድርጅት በብዜ የሃገሪቱ ክፍል መድረስ አይችልም ። የምግብ ቀውሱን ውጊያው እንዳባባሰው ሁሉ ሙስናም አስተዋፅኦ ያደርጋል ። ሰብዓዊ ድርጅቶች እርዳታ በሌላ ወገን በኩል ሳይሆን ለተረጂዎች በቀጥታ እንዲደርሷቸው የሚያደርጉባቸው መንገዶች አሏቸው ። »አስቸኳይ እርዳታ ከሚያስፈልጋቸው 2.5 ሚሊዮን ሰዎች በተጨማሪ 1.9 ሚሊዮን ሶማሌዎች ህይወታቸውን ለማቆየትና በመንደራቸውና በቤታቸው ተወስነው እንዲቆዩ የሚያስችላቸው እርዳታ ይሻሉ ።
ሂሩት መለሰ
ነጋሽ መሐመድ